ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, February 16, 2018

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ከህወሓት ውጭ ሌሎች የኢህአዴግ ድርጅቶች አልተስማሙበትም።ህወሓት በለየለት የዕብደት ሥራ ውስጥ ገብቷል። (ጉዳያችን አጭር ዘገባ)

 ጉዳያችን / Gudayachn
  የካቲት 10/2010 ዓም (ፈብሯሪ 16/2018 ዓም) 

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመታወጁ ጉዳይ የህወሓት እና የህወሓት ፍላጎት ብቻ እንደሆነ መረጃዎች ከአዲስ አበባ ያሳያሉ።ባለፈው ዓመት በነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መነሳት ላይ በከፍተኛ ደረጃ የአዋጁን መነሳት ሲቃወሙ የነበሩት የህወሓት ጎራ የሚገኙ ከፍተኛ ባለ ሀብቶች፣የወታደራዊ እና ጥቂት የኤሊቱ ወገን እንደነበር እና ጉዳዩ ዓለም አቀፍ ጫና እና የውጭ ምንዛሪ ላይ ተፅኖ በመፍጠሩ መነሳቱ ይታወቃል።ሆኖም ግን አሜሪካ፣አውሮፓ እና ቦሌ ቅምጥል ህንፃዎች ውስጥ ተቀምጠው የሚሞተው ሕዝብ የማይገዳቸው "አዋጅ ነው ለእዚህ ሕዝብ መድሃኒቱ" በሚል ስላቅ የአሁኑ አዋጅም እንዲታወጅ አዋጁ ከመነገሩ አርባ ስምንት ሰዓታት በፊት በትግራይ ኦን ላይን ድረ ገፅ እና በፌስ ቡክ ሰራዊታቸው አማካይነት ማሰራጨት ጀምረው ነበር። ዛሬ የካቲት 9/2010 ዓም የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ ለጋዜጠኞች ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ መግለጫ እንደሚሰጥ ገልጦ ጋዜጠኞችን እስከ ምሽት ድረስ አስቀምጦ አዋጁ መውጣት እና አለመውጣት ላይ ሲከራከሩ ያመሸው ህወሓት መሩ ስብሰባ ያለውጤት በመቆየቱ ጋዜጠኞች እንዲመለሱ መልዕክት ከተነገረ በኃላ ምሽት ላይ በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እና ራድዮ አዋጁ እንደወጣ ተነገረ።የሆነው ይሄው ነው።በእዚህ ላይ ኦህዴድም ሆነ ብአዴን ያሉት ነገር እየቆየ የሚታይ ጉዳይ ነው የሚሆነው።ጉዳዩ ግን የሚያመለክተው አሁንም የኢትዮጵያ ችግር እያጠነጠነ ያለው በህወሓት አጉል ጀብደኝነት እና ትዕቢት ዙርያ መሆኑን መረዳት ይቻላል።

ህወሓት ኢትዮጵያን ከቀውስ ወደ ቀውስ እየወሰዳት ነው።የእዚህ አይነት አዋጅ ትናንት ከስልጣን ለቅቅያለሁ አንዳንድ ስራዎች እንዳይቆሙ እስካስረክብ ብቻ ኃላፊነት እወጣለሁ ያለ ጠቅላይ ሚኒስትር ያለው እና ከኃላፊነት የወረዱበት ካቢኔ የእዚህ አይነት አዋጅ ያውም ምክር ቤቱ ባልተወያየበት ደረጃ ማውጣት ይችላል ወይ? ይህ ጥያቄ ለጦር ሰራዊቱ ፊደል ቆጥረናል ለሚሉ ይቅረብልኝ።

 የዛሬ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ውሎ ብቻ የሚያሳየው ህወሓት  የትግራይ ኦን ላይን የመሰሉ ድረ ገፆችን  እና ጥቂት በስልጣን እና ሙስና ያበዱ ግለሰቦችን ይዞ የለየለት የእብደት ሥራ ውስጥ እንደገባ  እየታየ ነው።ሌላው ቀርቶ ከአሁን በኃላ በህወሓት አፈቀላጤ የሆኑ ድረ ገፆች እና ማኅበራዊ ሚድያ ላይ የሚተላለፉት መልክቶች የእራሱ የህወሓት ሙሉ ስምምነት ላይ ያልተደረሰባቸው ይልቁንም ጥቂት ደፋር ነን ባዮች በፈጠሩት የአናርኪ ቡድን የሚንቀሳቀስ መሆኑን ማወቅ ይቻላል።ይህ ማለት ካለው ህወሓት ውስጥ እራሱ ሌላ ጀብደኛ ነኝ ባይ ትንሽ ህወሓት እንደፈጠረ አመላካች ነው።በሌላ በኩል አቶ ገዱ ከስልጣን ወርደዋል የሚለውን ዜና እራሱ ሐሰት መሆኑን አሁንም ከሀገር ቤት የሚመጡ ዜናዎች ይጠቁማሉ።ይህንኑ ዜና ዛሬ ሲያሰራጩ የዋሉት ግን አሁንም የህወሓት አፈቀላጤ ማኅበራዊ ሚድያዎች ናቸው።  የአቶ ገዱን እና አቶ ደመቀ ከስልጣን ተነሱ የሚለው ዜና ውሸት መሆኑን የክልሉ ቃል አቀባይ አቶ ንጉሡ ጥላሁን በፌስ ቡክ ገፃቸው ''ዶሮ ብታልም ጥሬዋን'' በሚል ርዕስ በሰጡት ምላሽ ዜናው ሐሰት መሆኑን ሲያብራሩ 
'' በሰበር ዜና ለሚያሰሙን ህልመኞች መሪውን የሚመርጠው ድርጅቱ እና የአማራ ህዝብ ስለሆነ መመኘት ይቻላል ፤ እዉነት ግን ወዲህ አለች ” እንላለን።ህዝባችንም ይህንን አይነት ዘመቻ የተለመደ ስለሆነ የድርጅቱን ውሳኔዎች ውይይታችን በሚቀጥሉት ቅርብ ቀናት እስኪጠናቀቅ እና ትክክለኛው መረጃ በድርጅቱ በኩል እስኪሰጥ ድረስ ለሚለቀቁ እንዲህ ዓይነት የህልም ዜናዎች ጆሮ እንዳይሰጥ እንጠቁማለን።
“ዶሮ ብታልም ጥሬዋን”  ብለዋል። (የአቶ ንጉሡ ምላሽ ይህ ፅሁፍ በሌሎች ድረ ገፆች ከወጣ በኃላ የተጨመረ ስለሆነ የጉዳያችን ዜና በወጣባቸው ሌሎች ገፆች ላይ ባታገግኙት ከድረ ገፆቹ ስህተት አለመሆኑን ለማሳሰብ እንወዳለን)።

ባጠቃላይ ህወሓት አሁንም ኃላፊነት የተሰማው ተግባር እየፈፀመ አይደለም።ይህ ደግሞ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር እጅግ የሚጎዳት ነው።አሁን ሁለተኛው ምዕራፍ የነፃነት ትግል እንደተጀመረ አመላካች ሁኔታዎች አሉ። የመጀመርያውን ምዕራፍ ሕዝብ አይኑን እንዲገልጥ ለነፃነቱ እንዲናገር እንዲደፍር ጥቂቶች እነ እስክንድር ነጋ፣በቀለ ገርባ፣ እና ሌሎች በፈንጅ ላይ የመራመድ ያህል ተረማምደው የህዝብ ልቦና አንቅተዋል።አሁን ሁለተኛው ምዕራፍ ላይ በአንደኛው ምዕራፍ ላይ ዝም ያልን በሙያችን እና ባለን አቅም ሁሉ ለኢትዮጵያ አንድነት፣ፍቅር፣እና ሰላማዊ ሽግግር እንነሳ።ኢትዮጵያን እንደ ሀገር መልሰን እናቁማት።ህወሓት ከጋረጠባት አደጋ እንታደጋት።

ኢትዮጵያ ሀገሬ 



ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።