- በውጭ ያለችው ቤተክርስቲያን የፍትሕ እጦት ብዙ መዘዝ እንዳያስከትል ያስፈራል።
- ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ''እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመበት ለመንጋው ሁሉ (ሁሉ የሚለው ተሰምሮበት) እና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ! ያለው ሁልጊዜ መታወስ ያለበት ቅዱስ ቃል ነው።''
ጆሮ ያለው ይስማ! መንገድ ላይ የሚጮህ ''እብድ '' አይደለም ህጻናት ሲጫወቱ እርስ በርስ የተነጋገሩትን ''ይህች ንግግር ለእኔ ነች ወዮልኝ!'' ብለው እያነቡ ወደ ገዳም የሄዱ አባቶች ያሏት ቤተክርስቲያን በተራ እልህ እና የአንድ ቡድን ስሜት ይዞ በመሄድ ቤተክርስቲያንን መጉዳት በእግዚአብሔር ዘንድ እንደሚያስጠይቅ ለማስረዳት ጥቅስ መደርደር አያስፈልግም።
ከሊቀ ካሕን ክርስቶስ የሚበልጥ ጳጳስ የለም። ካህኑ ዔሊ ከ40 ዓመታት በላይ ታቦተ ጽዮንን ማገልገሉ በኋላ ባሳየው ቸልተኛነትና ቡድናዊ ስሜት ከመቀጣት አላዳነውም። ምዕመናን መፍትሄ የሚሰጣቸው ቤተክህነት እና ሊቀ ጳጳስ ይፈልጋሉ። ችግሮች የሚፈቱት በባዕዳን ፍርድቤት የቤተክርስቲያንን አጀንዳ ይዞ በመዞር አይደለም።የምዕመናንን ገንዘብ በየባዕዳኑ ፍርድቤት እየበተኑ ኃላፊነት ባልተሰማ መንገድ ምዕመናን ሲበተኑ ቆሞ በማየት ሊሆን አይችልም።ስለእዚህ ጉዳይ የማይገደው ማንም ክርስቲያን የተባለ ሊኖር አይገባም።
ዝቅ ብሎ ምዕመኑ ጋር ቀርቦ ችግሩን መፍታት፣ሸክሙን መሸከም የተሰጠ አደራ ነው። እግዚአብሔር ከማደርያው ሆኖ የሚፈጸሙትን የግፍ እና የአድሏዊ አሰራሮች ይመለከታል። ተመልክቶ ግን ድንገት በቃ ብሎ ይነሳል። ይህንን መጠን ያለፈ መንጋውን በፍቅር ሳይሆን በኃይል ለምግዛት የመሞከር አካሄድን አለመናገር በራሱ በእግዚአብሔር ዘንድ ያስጠይቃል።መጽሐፍ ያስተማረው ጳጳሳት መንጋውን በኃይል ሳይሆን በፍቅር እንዲመሩ ነው።
በውጭ እና በሀገር ውስጥ ያለው የሲኖዶስ መከፈል በኋላ ቀድሞ የነበሩ የአጥብያዎች የእርስ በርስ ችግሮች ውስጥ ስንት ችግሮች በውጭ ባሉ ጳጳሳት ተፈታ? ስንቶቹ አሁንም ድረስ ፍርድ ቤት ለፍርድ ቤት ሲሄዱ ጳጳሳት አንተም ተው! አንተም ተው! ብለው ሲሆን አልቅሰው እና ምዕመኑ መሃል ቀርበው ፈቱ? ስንቶቹ ጋር በአንዱ ቡድን ውስጥ እየገቡ ችግሮቹ ተባባሱ? በእዚህ ላይ እስኪ ቤተክህነት ጥናት ያጥና እና እነኝህን ችግሮች ይፍታ! ችግሩ ጣርያ ደርሶ ሀገር ሲታመስ ከመሮጥ ዛሬ ላይ ቀድሞ መፍትሄ መስጠት ያስፈልጋል። የቤተክርስቲያን ጉዳይ የጳጳሳት ጉዳይ ብቻ፣ወይንም የዲያቆናት ጉዳይ ብቻ አይደለም። ምዕመናን የራሳቸው ድርሻ አላቸው።መንጋውን በኃይል እንዲገዛ የተፈቀደለት እረኛ እንደሌለ መጽሐፍ ነግሮናል።በፍቅር፣ዝቅ ብሎ ምዕመናን እና ካህናቱ መሃል ቁጭ ብሎ የመነጋገር እና የመፍታት ለእዚህም የሚመጣ ማናቸውንም ፈተና ለመቋቋም የእያንዳንዱ እረኛ ግዴታ ነው።ቁራም ይጮሃል፣እብድም ይናገራል።ይህች ንግግር ለእኔ ነች ብሎ የሚሰማ ይስማት።የማይሰማ ንቆ ይተዋት። ይህ የሰማይ ደጅ ጉዳይ ነው።በሰማይ ደጅ ጉዳይ ነው።ምዕመኑ የሰማይ ደጁን ጉዳይ ጳጳሳት ዝቅ ብለው ወርደው እንዲፈቱ አሁንም ይለመናሉ።እግዚአብሔር ሳይነሳ ሰውም ሳያመር ትናንት የነበሩበትን አስታውሶ እንደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዝቅ ብለው ችግሮችን እንዲፈቱ ይለመናሉ።
===============/////፟=============


