ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, July 11, 2019

የህወሓት የሐምሌ 3ቱ ፀብ ጫሪ መግለጫ የድርጅቱ የመጨረሻው የሕቅታ ድምፁ ነው።

 ጉዳያችን / Gudayachn
ሐምሌ 5/2011 ዓም (ጁላይ 12/2019 ዓም)

ሐምሌ 3 እና 4/2011 ዓም በኢህአዴግ ውስጥ ካሉ አባል ድርጅቶች ውስጥ የትግራይ ሕዝብ ነፃነት ድርጅት (ህወሓት) እና የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ሁለት ተነቃቃፊ መግለጫዎች አውጥተዋል።ቀድሞ የወጣው እና የመተንኮስ ሚና የተጫወተው ሐምሌ 3 ቀን የወጣው የህወሓት መግለጫ ሲሆን የአዴፓ ፓርቲ መግለጫ ግን የህወሓት መግለጫን ተከትሎ የወጣ እና ባብዛኛው የህወሓት ያለፈ ሥራ እና መግለጫ ጭምር የሚነቅፍ መግለጫ ነው።

የህወሓት መግለጫ '' ለኢትዮጵያ ህዝቦች ይቅርታ እንዲጠይቅ፡ ካልሆነ ግን ህወሓት ከአዴፓ ጋር መስራት እንደማይችል'' ይገልጣል። ይህ አገላለጥ በራሱ ከሚገባው በላይ የተለጠጠ እና ህወሓት ይቅርታ ተጠያቂ ፣ አዴፓ ደግሞ ይቅርታ ጠያቂ ይሁን የሚል ''ጠብ ያለሽ በዳቦ'' አይነት አገላለጥ ነው።''ህወሓት አብሮ መስራት የማይችል'' የሚለው አባባል በራሱ ነጥለን ብናወጣው ላለፈው አንድ ዓመት ህወሓት አብሮ እየሰራ ነበር ወይንም በኢህአዴግ የማዕከላዊ ስብሰባ ላይ ብቻ እየተሳተፈ ነው የሰነበተው የሚል ጥያቄ ያስነሳል።

የህወሓት መግለጫ ተራ ቁጥር 5 ላይ ''ህወሓት እንደ አንድ ህገ-መንግስታዊ እና ፌደራላዊ ሀይል፡ ሀገራችን ከወቅታዊ እና ቀጣይ አደጋዎች ለማዳን ተመሳሳይ ዓላማ ካላቸው ህገ-መንግስታዊ እና ፌደራላዊ ሀይሎች ጋ ሰፊ መድረክ ፈጥሮ ለመታገል እና በፍጥነት ወደ ተግባር ለመሸጋገር የህወሓት ማ/ኮ ወስኗል'' ይላል።ይህ አባባል ህወሓት በይፋ ከኢህአዴግ ምክር ቤት የወጣ ያህል ያስቆጥረዋል። በሌላ በኩል ተመሳሳይ ዓላማ ካላቸው ጋር መድረክ ፈጥሮ በፍጥነት ወደ ተግባር ለመሸጋገር መወሰኑን የሚያትተው ዓረፍተ ነገር የሚያመላክተው ነገር ቢኖር ህወሓት ዛሬም ክልሎችን በማባበል ሀገሪቱን የመከፋፈል ተግባር ላይ ለመሰማራት ማቀዱን ያመላክታል።


የአዴፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ በሌላ በኩል ሐምሌ 4/2011 ዓም ባወጣው መግለጫ የህወሓትን መግለጫ ''ከትልቅ ሃዘናችን ባልተላቀቅንበት ሕሊናዊ ሁኔታ ውስጥ ሆነን የወጣው የትህነግ/ህወሓት መግለጫ አሳፋሪ የሴራ ፖለቲካ'' በማለት ገልጦታል።በመቀጠልም መግለጫው ትህነግ /ህወሓት በ1968 ዓም ማኒፌስቶው የአማራን ሕዝብ በጠላትነት የፈረጀ መሆኑን አለመርሳቱን አስታውሶ፣ ዛሬም ህወሓት በአደባባይ ተሸንፎ ሕዝባዊ እርቃኑን መጋለጡን ረስቶ የተቀበረውን የትምክህት ትርክቱን ዳግም ይዞ ብቅ ብሏል በማለት አብጠልጥሎታል።


የህወሓት እና የአዴፓ መግለጫ እንዲህ ዓይነት በባላንጣ ቃላት ተሞልቶ መውጣቱ እንዳለ ሆኖ የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) ጨፌ ምክርቤት በመጪው ሳምንት መጀመርያ ላይ ይሰበሰባል።በስብሰባው ማጠቃለያም መግለጫ እንደሚያወጣ ይጠበቃል።በመግለጫው ላይም የለውጥ ሂደቱን ያደናቅፋል ብሎ የሚያስበውን ማናቸውንም ኃይል ህወሓት ጨምሮ መውቀሱ የሚጠበቅ ነው። ቁምነገሩ ግን የኢህአዴግ ድርጅቶች መግለጫ ጋጋታ ለኢትዮጵያ ምን ይፈይዳል? የሚለው ነው።


ኢትዮጵያ ከአሁን በኃላ ልትሸከም የምትችለው የመግለጫ ንትርክም ሆነ የጦርነት አውድማ የለም 


ኃላፊነት የማይሰማቸው፣የስልጣን ጥማቸውን በሴራ ፖለቲካ ብቻ ማሳካት የሚፈልጉ እና የጎሳ ፖለቲካ የሚያቀነቅኑ ኃይሎች በኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ላይ መናኘት ከጀመሩ ይሄው 29 ዓመታት ሆነ።ያለፉት ሁለት ቀናት የህወሓት እና የአዴፓ መግለጫዎች ጥሩ መገለጫዎች ናቸው።መግለጫዎቹ እጅግ ኃላፊነት የጎደላቸው ብቻ ሳይሆኑ በህወሓት ፀብ ጫሪነት ተጀምሮ በአዴፓ የመልስ ምት ምሽቱ ተፈፅሟል።በመጪው ሳምንት ደግሞ የኦዴፓ መግለጫ ሲጨመር ሌላ የቃላት ንትርክ ይከተላል።ይህ የሚያሳየው ኢህአዴግ እንደ ድርጅት እየተሰነታጠቀ መሆኑን ነው።መሰንጠቁ ደግሞ እራሱን ብቻ ይዞ ወደ ሞት የሚወስድ ሳይሆን ኢትዮጵያውያንን በጎሳ ለማጋጨት ዓላማ ያለው ይመስላል።ይህ ግጭት ደግሞ አድማሱ በክልሎች አካባቢ ብቻ ተወስኖ የሚቀር ሳይሆን በመላ ሀገሪቱ የሚቀሰቅስ አደገኛ የጎሳ ግጭት እንደሚፈጥር ይታወቃል።ስለሆነም ከኃላፊነት የጎደለው ተግባር ሁሉም ሊርቅ ይገባዋል።ህወሓት ይህንን የፀብ ጫሪ መግለጫ ሐምሌ 3 ቀን ለመልቀቅ የፈለገበት ምክንያት ግልጥ ነው።ይሄውም በውስጡ የተነሳው ቀውስ እና ክልሉን ለማስተዳደር ከገጠመው የአቅም ማነስ ምክንያት ከሕዝቡ የሚነሳውን ተቃውሞ ለማፈን አዲስ የግጭት አጀንዳ በመፍጠር ሕዝቡን የመወጠር ደካማ ስልት የያዘ ይመስላል።ይህ ደግሞ መልሶ ገመዱን ያሳጥረው እንደሆነ እንጂ የትም የሚያደርስ ስልት አይደለም።ኢትዮጵያ ከአሁን በኃላ ልትሸከም የምትችለው የመግለጫ ንትርክም ሆነ የጦርነት አውድማ የለም።ሕዝብ ሊቃወመው የሚገባ አብይ የወቅቱ ፖለቲካ ቢኖር ይህ የኢህአዴግ ድርጅቶች የሚያነሱት የእርስ በርስ ንትርክን ነው። 


ለማጠቃለል የኢህአዴግ ህልውና የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ እንደደረሰ አመላካች ነው።አሁን ኢህአዴግ ድምፁን ሳያሰማ የመክሰሚያው ጊዜ አሁን ነው።ኢህአዴግ ከከሰመ በኃላ ከሃያ ሰባት ዓመታት በላይ ''አጋር'' የሚለውን ስም ተሸክመው በኢትዮጵያ የፖለቲካ ሕይወት ውስጥ የተገለሉትን ድርጅቶች ለምሳሌ የአፋር እና የሱማሌ ድርጅቶች ጭምሮ አዲስ ውሁድ የፖለቲካ ድርጅት ሆኖ ኢህአዴግ መውጣት  አለበት።አንዳንዶች ኢህአዴግ በራሱ መደምሰስ አለበት የሚሉ አሉ። ይህ ግን ከኢትዮጵያ የተለያየ የፖለቲካ አጣብቂኝ ውስጥ ለምትገኝ ሀገር ያለውን ማፍረስ አይጠቅማትም።ማፍረስ ወደ ባሰ የእርስ በርስ ግጭት ያመራል።መክሰም ግን በፀጥታ ድምፅ ውስጥ ያለ አንዳች የከፋ መንገራገጭ የሚከሰት የለውጥ ሂደት ነው።በመክሰሙ ሂደት ላይ የማይስማማ የኢህአዴግ አባል ሊኖር ይችላል።ለምሳሌ ህወሓት ላይስማማ ይችላል።ህወሓት ባይስማማ የሚጎዳው እና በአጭር ሂደት ውስጥ የማያፈናፍን ደረጃ ላይ የሚያደርሰው እራሱን ህወሓትን ነው።ህወሓት እስካሁን በነበረው የኢህአዴግ ምክር ቤት ሚናው ቢያንስ በስብሰባ ሂደት እንደማንም ድርጅት እየተከራከረ ስሳተፍ መቆየቱ ይታወቃል።አሁን ህወሓት የሚያጣው ይህንኑ ዕድሉን ነው።በቀጣዩ ቀናትም ከመግለጫ ባለፈ ህወሓት የሚሄድበት ሂደት የሚታይ ነው።ህወሓት ይህንን መግለጫ ሲያወጣ ለተከታታይ ጊዜ በትግራይ ውስጥ ከፍተኛ የማጥላላት ሥራ በማዕከላዊ መንግስት ላይ ሲያካሂድ ሰንብቷል።ከፕሮፓጋንዳ ቀጥሎ የተለቀቀው መግለጫ ጠንካራ ምላሽ ከአማራ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ያገኘ ቢሆንም የህወሓት የሐምሌ 3ቱ  ፀብ ጫሪ መግለጫ የድርጅቱ የመጨረሻው የሕቅታ ድምፁ ነው።ሕቅታ ሰው ከመሞቱ በፊት የሚያሰማው የመጨረሻ አጭር  ወደውስጥ የሚሰማ ትንታ መሰል ድምፅ ነው።



ቴዲ አፍሮ (ቪድዮ)


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።