ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, April 13, 2018

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ እያደረጉት ያለው ጉዞ ቅድምያ የሚሰጠው የነበረ ትክክለኛ ጉዞ ነው (የጉዳያችን ማስታወሻ)

ጉዳያችን / Gudayachn
ሚያዝያ 6/2010 ዓም (አፕሪል 14/2018)

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ቅድምያ ወደ ሱማሌ፣በመቀጠል ወደ አምቦ፣መቀሌ እና በመጪው ጊዜ ደግሞ ወደ ባህር ዳር እና ጎንደር መሄዳቸው ትክክል ነው? አይደለም ? ቅድምያ ወደ ካብኔ ምስረታ መሄድ የለባቸውም ነበር? የሚሉ አስተያየቶች እዚህም እዝያም ይሰማሉ።ይህ ግን ከትክክለኛ የስልት እሳቤ አንፃር መመልከት ያልቻሉ ሰዎች አተያይ ነው።ስለሆነም  ቅድምያ ለጉዞ መስጠታቸው ትክክል ነው።ለእዚህም ማስረጃ የሚሆነው ከጉዞዎቹ ምን ተገኙ የሚለውን ለመለካት ስንችል ነው።ውጤቱ የሚለካው ደግሞ በቀላሉ በሚለካ የፖለለቲካ ውጤት ሳይሆን አጠቃላይ ሀገሪቱ ከነበረችበት ወቅታዊ ሁኔታ አንፃር ማመሳከር ሁሉ ይፈልጋል።በእዚህም መሰረት ዶ/ር ዓብይ ከጉዟቸው የሚከተሉትን የማይተኩ ውጤቶች አግኝተዋል። እነርሱም : -

1/ ከጉዞ በፊት ወደ ስልጣን እንደመጡ በሕወሓት በኩል የኢትዮጵያ ሱማሌ ክልልን ከኢትዮጵያ ፖለቲካ የመነጠል እና የህወሓት ጥገኛ ብቻ የማድረግ ሙከራ ከሽፏል።በእዚህም ሳብያ የኢትዮጵያ ሱማሌ ባለስልጣናት የዋለለ አካሄድ ይኖራል ቢባል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግን ሕዝብ ልብ ውስጥ እንዲገቡ ማድረግ ተችሏል።ለእዚህም ከጅጅጋ አየር ማረፍያ ጀምሮ የተሰለፈው ሕዝብ በነቂስ መውጣቱ ለአለቆቹ ማስተላለፍ የፈለገው መልክት ነበር። 

2/ በአምቦ ባደረጉት ጉብኝት እና ንግግር ደግሞ የኦሮሞ ማኅበረሰብ በምን ያህል ቁጥር አብሯቸው እንደቆመ ለህወሓት አሳይተውበታል።ይህ ብቻ አይደለም ለቄሮ ታገሱን ለውጥ እናመጣለን በሚል ንግግር ያለፈውን ትግል አወድሰው መጪውን አብረው እንደሚሄዱ የፖለቲካ ኃይሉን አጠናክረው ተመልሰዋል።

3/ ዛሬ በመቀሌ ያደረጉት ጉብኝት ደግሞ እራሱን የቻለ ስልት የያዘ ይመስላል።አንዳንዶች ለምን ሰማዕታት ሃውልት የአበባ ጉንጉን አስቀመጡ? የሰማእታት ሃውልት መሰራት ያለበት ከደርግ ወገንም ለሞቱት ጭምር ነው መሆን ያለበት የሚሉ ሃሳቦች አንስተዋል። ትክክል ናቸው። ይህንን ሃሳብ ትክክል ቢሆንም ወደ ተግባር ለማምጣት ግን ዶ/ር ዓብይ በበቂ ሁኔታ የፖለቲካ ስልጣኑን መረከብ አለባቸው።መቀሌ ላይ ያደረጉት ንግግር በዋናነት በትግርኛ በመናገር እና የትግራይን ጥንታዊነት በማንሳት ህዝቡ በጠላትነት እንደህዝብ እንዳልተፈረጀ ለትግራይ ሕዝብ ለመንገር አጋጣሚውን ተጠቅመውበታል። ይህም ጉዳዩ ከመሪዎቹ ጋር ሳይሆን ሕዝብ እንደ ሕዝብ እንዳይደነበር ነግረውበታል።ይህ ደግሞ መልካም አጋጣሚ ነው።

ባጠቃላይ ዶ/ር አብይ እነኝህን ጉዞዎች ማድረጋቸው እና በቀጣይ ቀናት ወደ ባህር ዳር እና ጎንደር ማምራታቸው አስፈላጊ ነበር። እነኝህን ጉዞዎች ካቢኔ ከመመስረት በፊት ማስቀደማቸው በእራሱ ትክክለኛ ስልት ነው። በጉዟቸው ሁሉ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ስልጣን በፓርላማው ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያውያን ዘንድ መረጋገጡን እና  ተስፋ እንዳጫረ ሁሉ ለህወሓት በግልጥ ነግረውታል።በእዚህም ህወሓት እርሳቸውን የሚጋፋ ከሆነ በጉብኝታቸው ወቅት ለድጋፍ ከወጣው ሕዝብ ጋር ሁሉ መጋጨት እንደሆነ በግልፅ የፖለቲካ ማሳያ መንገድ ለህወሓት የነገሩበት የጥበብ መንገድ ነው።ከእዚህ ሁሉ ግብኝት እና የፖለቲካ ኃይል ማሰለፍ በኃላ ወደ ካቢኔ ምስረታ የመሄዱ ሂደት ከተፅኖ  ፈጣሪነት አቅም ጋር ስለሚሆን የዶ/ር ዓብይ አቅም ቀድሞ ከነበረው ጎልብቶ እንዲገኝ አድርጎታል።በሌላ በኩል በጉዞዎቹ ላይ የተገኘው የህዝብ ድጋፍ የተመለከቱ የውጭ ኃይሎች ሁሉ ዶ/ር አብይ ያሰለፉት የህዝብ ብዛት እንዲመለከቱ ያደረገ ብቻ ሳይሆን ሂደቱ በህወሓት ቢደናቀፍ ምክንያታዊ ያልሆነ ነገር ግን የስልጣን ጥማት ብቻ መሆኑን ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ክስተት ሆኗል።ስለሆነም የዶ/ር ዓብይ ጉዞ ትክክለኛ እና ውጤታማ ነበር።ለመጪው ለውጥም ትልቅ የፖለቲካ ጉልበት የሚሰጣቸው ይሆናል።

ድምፃዊ ማዲንጎ አፈወርቅ - ጎዳናው (ዜማ)

ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments: