ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, November 21, 2023

አቡነ ኤርምያስ ከተናገሩት ውስጥ እውነት ያልሆነ አንድ ቃል ማግኘት አልቻልኩም።

አቡነ ኤርምያስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ
  • ''በማንም ተጽዕኖ ውስጥ ወድቄ በማንም ተናገር ተብዬ የተናገርኩት የለም.።ወደፊትም እናገራለሁ ብዬ አላስብም።መንፈስቅዱስ ይጠብቀኝ። '' አቡነ ኤርምያስ የሰሜን ወሎ ሀገረስብከት ሊቀ ጳጳስ

=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

የሰሜን ወሎ ሀገረስብከት ሊቀጳጳስ አቡነ ኤርምያስ ሰሞኑን ከላስታ ላሊበላ ህዝብና ካሕናት ጋር በተደረገ ስብሰባ ላይ የተናገሩትን መነሻ በማድረግ ሁሉም ለምን የእኔን ሀሳብ አላንጸባረቁም? በሚል የተለያዩ ስሞታም፣ወቀሳም አለፍ ሲልም ዘለፋ ሲዘነዘር እየሰማን ነው። በሌላ አንጻርም አቡነ ኤርምያስ የተናገሩት እውነት መሆኑን የተናገሩም፣የመሰከሩም አሉ።በአቡነ ኤርምያስ ከተናገሩት አንዳንዶችን የከነከናቸው ነገር ግን በቀጥታ ጉዳዩን ሳያነሱ ዙርያ ጥምጥም የሚሄዱባቸው ሦስቱን ነጥቦች ብቻ እንመልከት።ወደ ሦስቱ ነጥቦች ከመሄዴ በፊት ለሁሉም ግንዛቤ እንዲሆን ሁለት ነጥቦች ላንሳ።

የመጀመርያው ነጥብ፣የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች የስነ መንግስት ጉዳይ የማይገባቸው እንዲያው ካለ እውቀት እንደተናገሩ አስመስለው የሚያቀርቡ በጣም እንደተሳሳቱ ማስረዳቱ ጥሩ ነው።የአባቶች ብቃት ከዓለማዊው ትምሕርት ባለፈ መንፈስቅዱስ ባወቀ የሚረዱትን የመረዳት አቅምም መኖሩን ማሰብ ተገቢ ነው።

ሁለተኛው ነጥብ፣የስነ መንግስትን ጉዳይ መግፋት የቤተክርስቲያን ጉዳይ አይደለም።ይህም ሆኖ በነባራዊው ዓለም ላይ የምትኖር ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ዘመንም የመንግስት ጉዳይ አንስተው ክርስቶስን ለመፈተን ''ከፈሪሳውያንና ከሔሮድስ ወገን ሰዎችን ላኩ'' በማለት  መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ያለው ቃል ይነግረናል። ንባቡ እና የአባቶቻችን ትርጓሚ እንደሚከተለው ነው።

የማርቆስ ወንጌል 12፣14 - 17  ''መጥተውም። መምህር ሆይ፥ የሰውን ፊት ሳትመለከት በእውነት የእግዚአብሔር መንገድ ታስተምራለህና እውነተኛ እንደ ሆንህ ለማንምም እንዳታደላ እናውቃለን፤ ለቄሣር ግብር መስጠት ተፈቅዶአልን ወይስ አልተፈቀደም? እንስጥን ወይስ አንስጥ? አሉት። እርሱ ግን ግብዝነታቸውን አውቆ። ለምን ትፈትኑኛላችሁ? አየው ዘንድ አንድ ዲናር አምጡልኝ አላቸው። እነርሱም አመጡለት። ይህች መልክ ጽሕፈቲቱስ የማን ናት? አላቸው፤ እነርሱም። የቄሣር ናት አሉት።ኢየሱስም መልሶ። የቄሣርን ለቄሣር የእግዚአብሔርንም ለእግዚአብሔር አስረክቡ አላቸው። በእርሱም ተደነቁ።''

በአባቶቻችን ትርጓሜ ጌታችንን ለመፈተን የመጡት ግብር መስጠት ተፈቅዷል ካለን ይሄ ምድራዊ ነው እንጂ ሰማያዊ አይደለም ስለምድራዊ ግብር ያወራል ሊሉት፣ ግብር አትስጡ ቢላቸው ደግሞ ለመንግስት ሄደው ግብር አትክፈሉ የሚል ተነስቷል ብለው ሊከሱት እንደሆነ አውቋልና ዲናሯን አምጡ ብሎ ዲናሩ ላይ ያለችውን ጽሕፈት አሳይቶ የቄሳርን ለቄሳር፣የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሄር ስጡ ብሎ በመመለሱ የሚከሱበት አጡ በማለት የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን አብራርታ ታስተምራለች።

ቤተክርስቲያንን ከፖለቲካ ዕይታቸው አንጻር ለመለወስ እና ጥፋት ነቁጥ ለመንቀስ የሚደክሙ በየትኛውም የጎሳ ስብስብ ውስጥ ቢሆኑ ከላይ ከተጠቀሱት ከፈሪሳውያንና ከሔሮድስ ወገን አስተሳሰብ የተለዩ አይደሉም። አቡነ ኤርምያስ የአባትነታቸውን የተናገሩትን እውነት ለአንዳንዶች የራስ ምታት ቢሆንባቸውም ዕውነትነቱ ላይ ግን የሚያመጣው አንዳች ለውጥ የለም።

አቡነ ኤርምያስ ከተናገሩት ውስጥ እውነት ያልሆነ እስኪ አንዲት ቃል አውጡ? 

''አራት ኪሎ ቢገባስ''

አንዳንዶች የአቡነ ኤርምያስን እውነት አልዋጥ ካላቸው ውስጥ በቀጥታ አያናገሩትም እንጂ ከላይ በተጠቀሰው መድረክ ላይ ከተናገሩት  ቀደም ብለው ችግሮች እንዳይፈጠሩ ለእርቅ የሄዱበት መንገድ እንደነበርና በኋላ አንድም ካህን ቢመጣ በጥይት እንለዋለን ድረስ የሚሉ ቃላት በአማራ ክልል በሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች በኩል መሰማቱን በመጠኑ ጠቁመው፣ በታጣቂዎቹ አካሄድ ላይ ግን እንደማይስማሙ አባታዊ ምክራቸውን ሲለግሱ እንዲህ ብለዋል ''በወንድሞቼ አካሄድ አልስማማም። ደግሞስ አራት ኪሎ ቢገባስ'' ካሉ በኋላ ዘላቂ  መፍትሄ እንደማይሰጥ ይህ ደግሞ ሌላው እስኪዘጋጅ እንጂ ዘላቂ ሀገራዊ ሰላም እንደማያመጣ መክረዋል። ከእዚህ ዕውነት ውስጥ ምን ውሸት መንቀስ ይቻላል? በ21ኛው ክ/ዘመን ስልጣን በጠበንጃ በመነጣጠቅ መፍትሄ እንደማይመጣ ከእዚህ ይልቅ ሌሎች የሰላማዊ የትግል መንገድ መከተል አስፈላጊነት ላይ ምን ስህተት ይወጣለታል?

''ላሊበላ ለምን ከተሙ?''

አቡነ ኤርምያስ ያነሱት ሌላው ነጥብ ላሊበላ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናቱ ብቻ ሳይሆኑ ከተማዋ በራሷ ከተማ ሳትሆን የተቀደሰ ቦታ ነች።መገዳደል ያስቀስፋል በሚል የገለጹበት እውነት ነው። በእዚህም ላሊበላ መክተም ለምን? የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ እና ከገዳሙ አውጥቶ መግደል ምን ዓይነት ህሊና እንደሆነ የገለጹበት መንገድ ምን ነቁጥ ይገኝበታል?

''ውጪ ሆነው ሬሳ እየሸጡ የሚኖሩ''

ይሄ ውሸት ነው? የዩቱበር ሸቀጥ ለመሸቀጥ ያልሞተ ሞተ፣የወደቀውን ተሰበረ፣ እያለ በውጭ ሀገር ሶፋ ላይ ተቀምጦ የራሱን ልጆች ወደ ትምህርት ቤት እየላከ በአማራ ክልል ከሦስት ሚልዮን በላይ የሚሆኑ ልጆች እስከ ኅዳር ወር መጀመርያ ድረስ በጸጥታ ችግር አለመመዝገባቸው ትንሽ ቅሬታ ያልፈጠረበት፣ነገር ግን ''በለው!'' እያሉ ሲፎክሩ የሚውሉ እያየን አይደለንም እንዴ? እነኝህ አስከሬን ካልታየ ዩቱባቸው ይሸጣል? ይህንን እውነት ለምን እንክዳለን? የህወሓት አድናቂዎች በትግራይ ምስኪን ህዝብ ሞት ከውጭ ሆነው ሲያበረታቱ የነበሩ ዛሬ ሞቶን እና መርዶውን ለምስኪን የትግራይ እናቶች አስታቅፈው እነርሱ ዛሬ የት ናቸው? በአማራ ክልልስ እየሆነ ያለው በወሬ የሬሳ ሽያጭ መነገድ የተለየ ነገር አለ? 

''በጦርነት ሰላም አይመጣም፣ ወንድም ወንድሙን አጥቅቶ፣ፋኖ መከላከያን አጥቅቶ ወሰን ሊያስከብር አይደለም፣ ጉዳዩ ይህ እንደ ሀገር ያሰጋል።''

እዚህ ላይ የሚነቀስ ምን ውሸት አለ? እውነቱን ከሚናገሩት ጥቂቶች በቀር፣ ሁሉም ''ካድሬ ይሉኛል'' ብሎ አፉን ይዞ ነው እንጂ ምንም ይሁን ምን መከላከያውን የበላ ህዝብ የሚበላው ጠላት ዕለቱን መጥቶ እንደሚበትነው፣ እርስ በርሱም ወደ የማያባራ ጦርነት እንደሚገባ ከሶርያ ባንማር፣ከሊብያ፣ከሊብያ ባንማር ከየመን፣ ከእነኝህ ሁሉ መማር ቢያቅተን እንዴት ከቅርብ ጎረቤታችን ሱዳን መማር አቃተን። አቡነ ኤርምያስ ሀገር እንዲህ መሄድ የለበትም ሲሉ አለመስማት ብቻ ሳይሆን ለስድብ አፍን ማሾል ምን ዓይነት መረገም ነው?

አቡነ ኤርምያስ በእዚሁ መድረክ ላይ መንግስትንም በተገቢ ቃላት ወቅሰዋል።በአማራ ክልል የሚገኙ ታጣቂዎችን ጉዳይም ለመንግስት በሚገባ አካሄዱን እንዲፈትሽ ሲያሳስቡ ከተናገሩት ውስጥ የሚከተሉት ይገኙበታል 
  • የተቆጡ ወገኖች አሉ።ሁላችንም እኔንም ጨምሮ ተቆጥተናል።
  • እነኝህ ወገኖች ከመከላከያ ጋር አብረው የተዋደቁ ናቸው።
  • መንግስት ዝቅ ብሎ ለእነኝህ ወገኖች የሚመጥን መድረክ መንግስት አዘጋጅቶ መፍትሄ ማምጣት አለበት።
  • ክርስቶስ ዝቅ ብሎ መጥቶ አዳምን አድኖ የነበረበትን መንገድ ምሳሌ ጠቅሰዋል።
  • መከላከያ ከገባ በኋላ ተፈጽሟል የተባለውን ዘረፋ መከላከያ አጣርቶ ይህንን ያደረጉትን እንዲቀጣ አሳስበዋል።
  • ''የመረረው ድሃ ይገባል ከውሃ'' እንዲሉ መንግስት ባለበት ሀገር ዛሬ ከዋና ከተማዋ ተነስቶ ሰው እንዴት ለመሄድ የሚፈራበት ሁኔታ ይፈጸማል?
እና ሌሎችም ምክረሃሳቦችን አቅርበዋል።

ለማጠቃለል፣ከአቡነ ኤርምያስ ምክረሃሳብ ውስጥ የሚገኝ አንድ ውሸት ካለ እስኪ አውጡ? ስለሌለ የምታወጡት አንድም ውሸት የለም። በእዚህ የውይይት መድረክ ላይ ከተሳታፊዎች ደጋግሞ ከተነሳው ቅሬታ ውስጥ አንዱ እና ህዝቡን ያስቆጣው ጉዳይ ግን ነበር። የከባድ መሳርያ ድምጽ በእዚያ መጠን ለምን እንዲተኮስ ተደረገ የሚለው ገዢው ሃሳብ ነው። ይህንን ጉዳይ መከላከያ በከፍተኛ ትኩረት ሊመለከተው የሚገባ ነው።አሁንም ወደ ህዝቡ ወርዶ የሚሰጠው ማብራርያ ካለ ጉዳዩን ማብራራት አለበት።ይህ ጉዳይ የአብዛኛው ተሳታፊን እና ካሕናቱን አስተያየት የሸፈነ ነበር። አቡነ ኤርምያስ ዘግይተው በሰጡት ማብራርያ ደግሞ ''በማንም ተጽዕኖ ውስጥ ወድቄ በማንም ተናገር ተብዬ የተናገርኩት የለም.።ወደፊትም እናገራለሁ ብዬ አላስብም።መንፈስቅዱስ ይጠብቀኝ። '' በማለት ተናግረዋል።ሀገርን ያለ አንድ መስካሪ ባዶ አይተዋትም። 

የአቡነ ኤርምያስን እና የተሳታፊዎችን አስተያየት የያዘው ቪድዮ



 

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...