ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, February 8, 2017

የመሰረታዊ ውሃ አቅርቦት ቀውስ በኢትዮጵያ (ጉዳያችን አጭር ዘገባ)

ጉዳያችን/ Gudayachn
የካቲት 2/2009 ዓም (ፈብርዋሪ 9/2017)
=========================

  • 42.5 ሚልዮን ሕዝብ ከፍተኛ የመሰረታዊ የውሃ እጥረት ላይ ነው።
  • በእዚህ ሳቢያ 71 ሚልዮን ሕዝብ መሰረታዊ ንፅህና ለመጠበቅ ተቸግሯል።
  • 71% የሚሆነው ሕዝብ ከ3.10 ዶላር በታች የሚያገኝ ሕዝብ ነው።
  • የቢራ ፋብሪካ ከመደርደር ይልቅ የውሃ ፕሮጀክት መስራት ይገባ ነበር።
  • ውሃ ጠማኝ በምከፍለው የቀረጥ ገንዘብ መንግስት ውሃ ያቅርብ ማለት ኢትዮጵያ ውስጥ ፖለቲካ ተብሎ ሊያሳስር ይችላል።

በኢትዮጵያ ከዋና ከተማ አዲስ አበባ  እስከ አዲግራት፣ ከደሴ እስከ ሻሸመኔ የሚጠጣ ውሃ ብቻ ሳይሆን ለገላ መታጠብያ ውሃ ብርቅ እየሆነ ነው።አዲስ አበባ በተለያዩ ቦታዎች ላይ አንድ ጀርካል ውሃ ከእነተሸካሚው እስከ 20 ብር በሻሸመኔ ደግሞ እስከ 15 ብር እንደሚያወጣ እራሱ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥንም በይፋ ያወጀው ዜና ነው።

ለውሃ እጥረቱ ዋነኛ ምክንያት ዝርክርክ፣እቅድ የለሽ እና ቅድምያ የሚሰጡ ፕሮጀክቶችን ቅድምያ የማይሰጥ  የመንግስት ፖሊሲ ሳብያ ነው።በቀደሙት መንግሥታት ወቅት የውሃ አቅርቦት ፕሮጀክት የሚሰራው ከከተሞች እድገት ጋር እየተሰላ ሲሆን በህወሓት ዘመን ግን የከተሞች እድገት ቁጥርን ታሳቢ አድርገው የሚያቅዱ የከተማ ምክርቤት ባለሙያም ሆነ እራሱ ሕወሓት የሚመድባቸው ባለሥልጣናቶች ሁሉ ከእዚህ አይነቱ አስተሳሰብ መራቃቸውን አመላካች ነው።

በኢትዮጵያ የውሃ አቅርቦት ላይ ኢትዮጵያ በውሃ ቀውስ ላይ ነች በማለት ዜናውን የሚያትተው water.org   የተሰኘው ድረ ገፅ 45.5 ሚልዮን ሕዝብ ከፍተኛ የውሃ እጥረት ላይ መሆኑን ገልፆ፣ በእዚሁ ሳብያ 71 ሚልዮን ሕዝብ መሰረታዊ ንፅህና ለመጠበቅ አለመቻሉን በተጨማሪም የውሃ እጥረቱ ህዝቡ በገንዘብ አቅምም የማይችለው መሆኑን ሲገልፅ 71% የሚሆነው ሕዝብ ከ3.10 ዶላር በታች የሚያገኝ ሕዝብ መሆኑ በእራሱ ፈታኝ መሆኑን ይገልጣል።

ባጠቃላይ የመሰረታዊ ነገሮች አቅርቦት ውስጥ ዋናው የሆነው የውሃ ነገር በእራሱ ውሃ እየሆነ ነው።ለእዚህ ሙሉ በሙሉ ኃላፊነቱን የሚወስደው ስልጣን ላይ የሚገኘው የሕውሓት መንግስት ዕቅድ አለማወቅ፣ቅድምይ በጀት አመዳዳብ ስህተት እና የሰለጠነ የሰው ኃይል ፍልሰት ሁሉ ተጠቃሾች ናቸው።በአንፃሩ ደግሞ የስርዓቱ የጥቅም ተጋሪዎች የሆኑ እንደ አሸን የፈሉት የታሸገ ውሃ አምራቾች ይህንን የውሃ እጥረት እንደ ሰርግ እና ምላሽ ነው የሚመለከቱት።ይህንን ደግሞ ስርዓቱ ላይ በስልጣን ላይ ያሉት ግለሰቦች የእነኝህ የታሸገ ውሃ አምራች ድርጅቶች ባለቤቶች ናቸው። ለእነርሱ ትርፍ ሲባል ሕዝብ የሚጠጣው ውሃ ላይ በቂ ትኩረት አይሰጠውም። ለውሃ እጥረት ምክንያቱም ምን እንደሆነ የተጠየቀው የሕወሓት መንግስት እስካሁን የረባ መልስ ሲሰጥ አልተደመጠም። አንድ ወቅት አቶ ሃይለማርያም የውሃ እጥረት ሕዝብ መብዛቱን እንደ ምክንያት ሲያቀርቡ መንግስት ቀድሞ ማቀድ ይገባው እንደነበር እና የቢራ ፋብሪካ ከመደርደር ይልቅ የውሃ ፕሮጀክት መስራት ይገባው እንደነበር ተናግረው አያውቁም።የውሃ ፍሳሽ ቢሮም ስለ ችግሩ ሲጠየቅ የሚሰጠው ምክንያት መብራት አለመኖር እና አዲስ አበባም የተቆፈረው ጉድጉአድ እየጎደለ ነው የሚል ነው።ኢትዮጵያ በአፍሪካ ከኮንጎ ቀጥሎ የውሃ ማማ ተብላ የምትጠራ ሀገር ነች።ነዳጅ ከጅቡቲ በቧንቧ እስባለሁ ያለ መንግስት እንዴት ለአዲስ አበባ ጉድጉአድ በመቆፈር ችግሩን ለመፍታት እየሞከርኩ ነው ብሎ ይናገራል? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው። 

ከእዚህ በታች የምትሰሙት ዜና ከስድስት ወራት በፊት የወጣ የፋና ዘገባ ሲሆን በዘገባው በርካታ ምክንያቶች ለመስጠት ቢሞከርም ዋናው ምክንያት ከላይ የተጠቀሰው ቀድሞ የሚያቅድ መንግስት አለመኖር እና የሀገሪቱን ገንዘብ ቅድምያ ለሚሰጡ ጉዳዮች ላይ ያለመመደብ እንዲሁም የተማረ የሰው ኃይል እጥረት ከመብራት እጥረት ጋር ተዳምሮ መሆኑን መረዳት ይቻላል። ይህ ዜና ከተወራ  ከወራት ወዲህም  አሁንም  ችግሩ በበለጠ ተባብሶ ይገኛል።የፈረቃ አገልግሎቱ የተጀመረው ያለፈው ዓመት እንደነበር ከእዚህ በታች ያለው ዜና ይነግረናል።አሁን ያለው ችግር ግን እራሱ ፈረቃው በተባለው ቀን አለመምጣቱ ነው።ውሃ ጠማኝ በምከፍለው የቀረጥ ገንዘብ መንግስት ውሃ ያቅርብ ማለት ኢትዮጵያ ውስጥ ፖለቲካ ተብሎ ሊያሳስር ይችላል።




ጉዳያችን GUDAYACHN

 www.gudayachn.com