ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, June 22, 2017

ስምንት ሚልዮን ሕዝብ በረሃብ የሞት አፋፍ ላይ ባለበት ሁኔታ የጅቡቲ ወደብ በፀጥታ ምክንያት አገልግሎቱ የመታጎል አደጋ ተጋርጦበታል (ጉዳያችን ዜና)

ፍጥጫ - አቶ ኢሳያስ እና ኢስማኤል ኦመር ጉሌህ 

አቶ ጆን ግራም (Mr. John Graham) የሕፃናት አድን ድርጅት የኢትዮጵያ ዳይሬክተር በተጨነቀ ስሜት ውስጥ ሆነው ለፕሬስ ቲቪ ይህንን የተናገሩት የትናንትናዋ ጀንበር ሳትጠልቅ ነበር።ጆን ግራም እንዲህ ነበር ያሉት -

    " የሕይወት አድን የምግብ እርዳታው ሊቆም ይችላል። በአንድ ወር ውስጥ ያለው የምግብ ክምችት ያልቃል።ከዝያ ምን እንደሚሆን አሁን መገመት አንችልም " (ፕሬስ ቲቪ፣ ሰኔ 15፣2009ዓም )
"We're looking at the food pipeline actually breaking, so the food is running out in about a month's time," John Graham, country director for Save the Children, said, adding, “After that, we don't know what's going to happen." 
እንደ ቴሌቭዥን ጣቢያው የዛሬ ሰኔ 15፣2009 ዓም ዘገባ በሱማሌ ክልል ድርቁ በተባባሰበት አካባቢ በትንሹ ወደ ግማሽ ሚልዮን የሚጠጋ ሕዝብ ቀየውን ትቶ ተሰዷል።የፕሬስ ቴሌቭዥን የኢትዮጵያ አደጋ መከላከል እና ዝግጁነት ኮሚሽን ኃላፊ አቶ ምትኩ ካሳን ጠቅሶ እንደዘገበው ዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ የለገሰው እርዳታ አነስተኛ መሆኑን ማማረራቸውን ይገልፃል።

በተባበሩት መንግስት የዓለም ምግብ ድርጅት (FAO) ገለጣ መሰረት ረሃብ ዋነኛ መሰረቱ ድርቅ ብቻ ሳይሆን የመንግሥታት መልካም ያልሆነ አስተዳደር ውጤት መሆኑን በማያሻማ መንገድ ይገልጣል። ከእዚህ በተጨማሪ ረሃብ የሚከተለው የፀጥታ መደፍረስ መሆኑን ይሄው የዓለም የምግብ ድርጅት ሲገልጥ  "በየትኛውም የዓለማችን ክፍል  ረሃብ የፀጥታ ስጋት ነው "  "Hunger anywhere threatens peace everywhere" (FAO Summit, June, 2002) ይላል። 

በኢትዮጵያ አሁን የተንሰራፋው አድሏዊ ስርዓት እና በዕውቀት ላይ ያልተመሰረተ ነገር ግን በሙስና እና ብልሹ አሰራር የተተበተበው የሕወሓት አገዛዝ ከሩብ ክ/ዘመን በኃላም የኢትዮጵያን የእርሻ ምርት አንዲት ስንዝር ሳያራምድ ይልቁንም የኢትዮጵያን ለም መሬት ለአረብ ቱጃር በመቸብቸብ ዛሬም የስምንት ሚልዮን ሕዝብ ርሃብተኛ የያዘች ሀገር ሆና ኢትዮጵያ በዓለም አደባባይ እርዳታው ዘገየ የምትል ሀገር ሆናለች።ይህ እንግዲህ አዲሱ የፈረንጆች 21ኛው ክፍለ ዘመን (ሚሊንየም) ከገባ ከ17 ዓመታት በኃላም መሆኑ ነው ህመሙ።


ከሁሉም የሚዘገንነው ጉዳይ ደግሞ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እና ራድዮ ድርቁን ከሚገመተው በላይ ደብቀውታል።ሕዝብ ተረባርቦ ወገኖቹን እንዳያድን መረጃው መደበቁ አሁንም በገሃድ እየታየ ነው።የበልግ ዝናብ በብዙ ቦታዎች ላይ በበቂ አለመገኘቱ እና በጎጃም የተነሳውን የአንበጣ መንጋ ትልቅ ስጋት ሆኖ እየታየ በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ለመከላከል አሁንም  ምንም አለማድረጉ የህዝቡን ችግር አባብሶታል።የህዝብን መራብ መደበቅ በእራሱ ከሰብአዊ መብት ጥሰት በላይ በዓለም አቀፍ ሕግም የሚያስጠይቅ መሆን እንዳለበት በርካታ አካላት ሲያሳስቡ መቆየታቸው ይታወቃል።በላቲን አሜሪካ እና ሩቅ ምስራቅ አገሮች መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ረሃብ የደበቁ መንግስታቶቻቸውን ለፍርድ ቤት እያቀረቡ ማስፈረዳቸው የሚታወቅ  ነው። 

በዓለም ምግብ ድርጅት ማብራርያ መሰረት የርሃብ ምክንያቶች በርካታ መሆናቸውን እና በዋናነት ግን ስድስት መሆናቸውን ይገልፃል። በቅድምያ ፅሁፉ በመግቢያነት የሚይስቀምጠው ነጥብ ''ዓለም ለ7 ቢልዮን የዓለማችን ሕዝብ በቂ ምርት ያመርታል'' በማለት ይጀምርና ስድስቱን በአንድ ሀገር ላይ ርሃብ የሚከሰትባቸውን ምክንያቶችን ይዘረዝራል። እነርሱም : - ድህነት (Poverty trap)፣በእርሻ ላይ በቂ መዋለ ንዋይ አለመመደብ ( Lack of investment in agriculture)፣ የአየር ንብረት ለውጥ 
( Climate and Weather)፣ ጦርነት እና የህዝብ ከስፍራው መፈናቀል (War and displacement)፣ ያልተረጋጋ የምግብ ገበያ ( Unstable Market)፣ የተረፈ ምግብ ብክነት ( Food Wastage)።

የኢትዮጵያን የአሁኑን የርሃብ ችግር የሚያባብሰው አንዱ ጉዳይ በአንድ ወር ውስጥ የመካከለኛው ምስራቅ ግለት ከጨመረ እና በጅቡቲ እና በኤርትራ መካከል ግጭት ከተነሳ የኢትዮጵያ ብቸኛ ወደብ ጅቡቲ ወደ ኢትዮጵያ የእርዳታ እህል ብቻ ሳይሆን ነዳጅ ጨምሮ ምንም አይነት ሸቀጥ ላይገባ ይችላል።በሱዳን በኩል ይገባ የነበረው የነዳጅ ምርት በአሁኑ ጊዜ አካባቢው በአማፅያን ኃይሎች በመያዙ ሕወሓት የሱዳን መኪናዎችንም ጭምር መከላከል እንዳልቻለ ይታወቃል።በመጪው ሁለት የክረምት ወራት ደግሞ አማፅያኑ የበለጠ ቦታዎችን ለመያዝ አመቺ ሁኔታ ከወንዝ መሙላት እና ሳሮች ተራሮችን ከመሸፈናቸው አንፃር የሕወሓት ሰራዊት በአብዛኛው ይዞታዎቹን እንደሚያጣ መገመት ይችላል።ምክንያቱም በመካናይዝድ ጦር የተሻለ አቅም የሚኖረው ሕወሓት በክረምት ወራት መንቀሳቀስ ስለማይችል ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ ኤርትራ ሰሜናዊ ጅቡቲ የሚገኘውን ራስ ዱሜራ ተራራማ ቦታ ኳታር 400 የሚሆኑ ወታደሮቿን ማንሳቷን ተከትሎ መቆጣጠሯ የወቅቱ ሌላው አዲስ ክስተት ነው።ኳታር ስፍራውን የለቀቀችበት እለት ማለትም እኤአ ሰኔ 12 እና 13/2017 ዓም  ሲሆን ኤርትራ ስፍራውን የያዘችውም በተመሳሳይ ሁለት ቀናት መሆኑን የጅቡቲ መንግስት ገልጧል።ይህንኑም  ተከትሎ ቀጣዩ ግጭት ኢትዮጵያ የጅቡቲን ወደብ የመጠቀም አቅሟን በእጅጉ ሊፈታተን የሚችል ሁኔታ እንደሚሆን ተገምቷል።ይህ ማለት ኢትዮጵያ ለአፋጣኝ የምግብ ዕርዳታ ብቻ ሳይሆን የጦር መሳርያ ለማስገባትም የጅቡቲ ወደብ ማለት ብዙ ማለት መሆኑ የታወቀ ነው።

በሕውሃት አስተዳደር ወቅት ኢትዮጵያን ከአካባቢው ሀገሮች በስልታዊ የተፈላጊነቷን ደረጃ ዝቅ እንድትል ካደረጋት አንዱ እና ዋናው ጉዳይ የአቶ መለስ ዜናዊ አስተዳደር ኢትዮጵያ ካለ ወደብ መኖር እንደምትችል በመግለፅ ጉዳዩን ማድበስበሳቸው መሆኑ ይታወሳል። በእርግጥ እዚህ ላይ የሚነሳው ጉዳይ ኢትዮጵያ ወደ ጦርነት መግባት ነበረባት ወይ? የሚል ጥያቄ እንደሚነሳ ይታወቃል። ሆኖም ግን የአቶ መለስ ሕወሓት የወደብ ጉዳይን ወደተራዘመ የመደራደርያ አጀንዳነት ማቅረብ ሲችሉ እና አንዳንድ የአሜሪካ ባለስልጣናትም ኢትዮጵያ የወደብ ባለቤት የመሆኗ ዓለም አቀፍ ሕግ እንደሚፈቅድላት ይሄውም 90 ሚልዮን ሕዝብ በ20 ኪሜ ርቀት ካለወደብ ሊቀመጥ አይችልም የሚለው መከራከርያ ጎልቶ የወጣ ግዙፍ ሃሳብ ነበር።የወደብ ጉዳይ የሕወሓት የኢትዮጵያን ሕዝብ ማማለያ ካርድ ከሆነ ሰንብቷል።ሕወሓት ውጥረት ውስጥ በሚሆንበት ወቅት የወደብ ጉዳይን እንደ ሰሞኑ ጀኔራል ፃድቃን "ኢትዮጵያ ወደብ ያስፈልጋታል" የሚል አረፍተ ነገር የመሰለ የወቅታዊ ካርድ መዘዛ አንዱ አካል ነው።



የጅቡቲ ወደብ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሳድ ኦማር ጉለህ 
M. SAAD OMAR GUELPH

ባጠቃላይ ሕወሓት የመዳከሙ ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን የበለጠ አደጋ ላይ የጣለ ቡድን ለመሆኑ አንዱ መገለጫ ሆኖ እየቀረበ ያለው ብቸኛ የኢትዮጵያ ገቢ እና ወጪ መስመር የሆነው የጅቡቲን ወደብ መከላከል የማይችል መሆኑን አስመስክሯል።የጅቡቲ ወደብ በአንድ መለስተኛ ሮኬት ተኩስ ጠቅላላ ወደቡ የመድን ሽፋን ዋስትና ሊያጣ እንደሚችል እና የዱባይ ኩባንያ በኮንትራት የሚያስተዳድረው የጅቡቲ ወደብ በማንኛውም ጊዜ በፀጥታ ችግር ሳቢያ አገልግሎቱ ሊቆም እንደሚችል አመላካች ነው። የሃያ ስድስት አመታት የሕወሓት አመራር ኢትዮጵያውያ ወደብ አልባ ብቻ ሳይሆን ከጎረቤት ሀገር ጅቡቲም የምትጠቀምበትን ወደብ መከላከል የማትችል ሀገር ደረጃ አድርሷታል። ይህ የሕወሓት የስልጣን ጥማት እና እጅግ የጠበበ የጎሳ ፖለቲካ ይህንንም ተከትሎ የፍትህ እና ዲሞክራሲ ጥያቄ የሚጠይቁ ኢትዮጵያውያንን የመግደል፣ማሰር እና ማሰደድ ተግባር  ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ያማዳከም ደረጃው ከሚገመተው በላይ ነው።ለእዚህም ነው ኢትዮጵያን ለማዳን ሕወሓት ስልጣኑን መልቀቁ እና የሽግግር መንግስት መመስረት ብቸኛ ወቅታዊ ሃገራዊ ጥሪ ሆኖ የሚቀርበው።

ጉዳያችን GUDAYACHN

www.gudayachn.com


ማጣቀሻዎች 

- ፕሬስ ቲቪ http://217.218.67.231/Detail/2017/06/22/526188/Ethiopi-UN-Warder-Save-the-Children

- የዓለም ምግብ ድርጅት (ዜሮ ሀንገር)   http://www1.wfp.org/zero-hunger 

- የዓለም ምግብ ድርጅት 2002 ጉባኤ   http://www.fao.org/worldfoodsummit/msd/Y6808e.htm
-


No comments: