ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, September 14, 2012

ከወታደራዊ ''ደርግ'' ወደ ሽምቅ ተዋጊ ''ደርግ '' ተሸጋገርን እንዴ?

  • ነገራችን ሁሉ '' የወታደራዊ ደርግ ውጣ የ ሽምቅ ተዋጊ ደርግ ግባ'' እንዳይሆን ሁለት ሶስት ጊዜ ማሰብ ይገባናል፣
  • አፍቃሪ ኢህአዴግም ሆኑ አባላቱ ያማይባቸው አንድ የጋራ የሆነ ባህሪ  አለ፣
  • ኢህአዴግ አሁንም 1983 ዓም ላይ ያለ ለመሆኑ ስራዎቹ እያሳበቁበት ነው፣
  • አሁን በምንኖርበት ዓለም ውስጥ ሕዝብ የሚመራው ፍላጎቱ እና ሃሳቡ በሳይንሳዊ መንገድ በተደገፈ መረጃ እና የጥናት ውጤት እንጂ በዘፈቀደ የተወሰኑ ሰዎች ተሰብስበው እንደፍላጎታቸው በወሰኑት ሊሆን አይገባውም፣
  • በኢትዮጵያ በስልጣን ሽምያም ሆነ በተለያዩ ምክንያቶች ከ ጥንት ጀምሮ ነገስታት እርስ በርስ ተዋግተዋል። አንዳቸውም ግን ከወገናቸው ጋር ላደረጉት ውግያ 'ግዳይ' እንደጣለ ማስታወሻ ሀውልት ያቆሙ የሉም።

የደርግ ትርጉም

ደርግ የሚለውን ቃል ትርጉም ውክፕድያ የተሰኘው እንሳይክሎፕድያ እንዲህ ይገልፀዋል:-

 ''The Derg or Dergue (Ge'ez: ደርግ), which means "committee" or "council" in Ge'ez, is the short name of the Coordinating Committee of the Armed Forces, Police, and Territorial Army that ruled Ethiopia between 1974 to 1987, taking power following the ousting of Haile Selassie I'' 1

'' ደርግ ወይንም ደርጉ ማለት በ ግእዝ  ኮሚቴ ወይንም ምክርቤት ማለት ሲሆን በ አጭሩ  ይህ ስም  የ ጦር  ኃይሎች የ ፖሊስ ሰራዊት እና የ ምድር ጦር አስተባባሪ ኮሚቴ እ አ አቆጣጠር ከ 1974 እስከ 1987 የ ቀዳማዊ ሃይለስላሴን መንግስት ተክቶ በኃይል ኢትዮጵያን የገዛ።'' ይለዋል።

ቀዳማዊ  አፄ ሃይለስላሴ በፈቃዳቸው ስልጣን ለቀቁ ማለት አንችልም?

ሰኔ 21/1966 ዓም  የተመሰረተው ደርግ መስከረም2፣ 1967 ዓም ቀዳማዊ አፄ ሃይለስላሴን ገድሎ  በ ይፋ ስልጣን መያዙን አወጀ። ይህ ብቻ አይደለም ህዳር 13/1967  ለ ደርጉ የ ዘመቻ እና ጥበቃ መምርያ መኮንን በተፃፈ ደብዳቤ ጀነራል አማን አምዶምን እና በ ተለምዶ የ'' ስልሳዎቹ እልቂት'' ተብሎ የሚታወሰውን ሚኒስትሮቹን እና ባለሙያ ምሁራንን ሁሉ በ አንዲት ጀንበር የፈጀበትን  ፍርድ ፈረደ።


 በ እዚህም የደርግ ፍርደ ገምድልነት '' ያለ ምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም! '' የሚለው መፈክር ሕልም መሆኑ ለየለት። እንደወቅቱ የታሪክ ተናጋሪዎች ከሆነ አፄ ሃይለስላሰም ሆኑ ከፍተኛ ባለስልጣኖቻቸው የ ጦር ኃይሉን ከመሰረቱ ጀምሮ ኮትኩተው ያሳደጉት ስለሆነ የከፋ ነገር ይፈፅማል ብለው አይጠብቁም ነበር። ብርጋዲር ጀነራል ደስታ ገመዳ ስለ ደርግ  አነሳስ እና  የ አፄ ሃይለስላሴን አመለካከት ሲገልፁ:-
'' እነ  ጀነራል አበበ ገመዳ የ ሰራዊቱን ሁኔታ አይተው  ጃንሆይን ' ልምታ?(ያመፁትን መኮንኖች )' አሉ። ጃንሆይ አይሆንም እንዳትነኩዋቸው አሉ።ምክንያቱም ጃንሆይ  ደም እንዲፈስ አይፈልጉም። ሚኒስትሮቹን ሁሉ ሂዳችሁ እጅ ስጡ ነው ያሉት።'' 2  ሲሉ ተናግረዋል ።

 ይህ ብቻ አይደለም በሰኔ  21/1966 የደርግ መመስረት ጋር ተያይዞ ኮለኔል ደበላ ደንሳ ለንጉሡ  ከደርግ መኮንኖች ጋር በ ቤተመንግሥታቸው ተገኝተው ባነበቡላቸው የደርግ ውሳኔ ላይ  ''የ ጦር ኃይሎች የ ፖሊስ ሰራዊት አስተባባሪ ደርግ ለ ግርማውነትዎ ጤንነት በሰፊው የሚያስብ ስለሆነ ለ ደህንነትዎ የተዘጋጀ ቦታ ስላለ  ወደዝያ እንዲሄዱልን  በትህትና እንለምናለን'' የሚል መልክት ነበር ።  ንጉሡም  የመለሱት  እንዲህ ነበር።
''በጠቅላላው የተናገራችሁትን ሰምተናል።የ ኢትዮጵያ ንጉሰ  ነገስት ስንሆን ስም ብቻ አይደለም።ህዝብንም ሀገርንም በሰላም ጊዜ የሚሰራበትን ጥፋትም ሲመጣ የሚመከትበትን በማሰናዳት መሆኑን ይህ በ ጦር ሰራዊታችን ውስጥ የታወቅ ሳይሆን ይቀራል ብለን አንጠረጥርም። ቢሆንም በየጊዜው የሚለዋወጠው ነገር ለሀገር የሚጠቅም ነገር እስካለበት የሀገርን ጥቅም በሌላ ለመለወጥ አይቻልምና ይህን ያነበባችሁትን ሰምተናል በእዚሁ ማቆም ነው።'' ብለዋል። 3
ቀዳማዊ አፄ ኃይለሰላሴ ደርግ ከ ቤተመንግሥታቸው ወደ አራተኛ ክፍለጦር በ ቫልስ ቫገን  መኪና ሲወስዳቸው።


በ እንዲህ አይነት ስልጣን የተቆናጠጠው ደርግ 'ስልጣኑን ለ ሕዝብ እመልሳለሁ' የሚል ቃል የገባ ቢሆንም በ ጎን ግን በ ሺህ የሚቆጠሩ''ሕዝባዊ መንግስት አሁኑኑ'' ያሉ ወጣቶችን  ደም ማፍሰስ  የ እለት ከ እለት ስራው ሆነ። ለቅሶ እና ዋይታ በ የስፍራው ተሰማ። ለ ሃገሩ እንግዳ ለ ህዝቡ ባዳ የሆነ የ ራሽያው ሶሽያሊዝም የሀገሪቱ መመርያ ነው ተባለ። ሰው ክብር የሚያገኘው በገደለው እና አላዋቂ በመሆኑ ብቻ ሆነ። እኔ ይህን ዘመን ክፉ ደግ ሳላውቅ በማለፉ ብቻ አምላኬን አመሰግነዋለሁ። ወላጆቻችን ሲጨነቁ  እኛ አና በ አኔ  እድሜ ያለን ሁሉ ምናልባት 'ሌባና ፖሊስ' እየተጫወትን ወይንም 'ድብብቆሽ' እንጫወት ይሆናል። አንዳንድ ጊዜ የ ቤተሰቦቻችንን ፊት  መከፋት እያየን ለጥቂት ጊዜ በ ዝምታ ተውጠን መልሰን ወደ ጫወታችን ሄደን ይሆናል። ለ እኔ ወቅቱ የሚታወሰኝ ነገር ስለሌለ እና በጣም ልጅ ስለነበርኩ ትውስታ ብዬ የምለው የለኝም። ሆኖም ግን አንድ ሰው ስለ ግሪክ ታሪክ ለማውራት በ ግሪክ ዘመን  መኖር አይጠበቅበትም። ያነበበው፣ በማስረጃ የተደገፉ ታሪካዊ ሁነቶችን አጤኖ ብዙ ሊገነዘብ የ እራሱንም ፍርድ መፍረድ ይችላል።

ደርግ ስልጣን እንደክረሜላ እየጣመው መጣ። በ 1972 የ ኢትዮጵያ ሰራተኞች ፓርቲ አደራጅ ኮምሽን (ኢሰፓአኮ)፣ ቀጥሎ በ 1977 ኢትዮጵያ ሰራተኞች ፓርቲ (ኢሰፓ)  በመጨረሻም የ ኢትዮጵያ ህዝባዊት ዲሞክራሳዊት ሪፑብሊክ (ኢ ህ ዲ ሪ) ሆኛለሁ አለ። ደርግ አይደለሁም አለ።ይህ ሁሉ ሲሆን ግን ከ ክፍለ ሀገር አስተዳዳሪ እስከ ከፍተኛ ሊቀ መናብርት ድረስ በ ማረግ ያሉ የ ሰራዊቱ መኮንኖች ግን ሶሻሊዝም የገባቸው ተብለው ስልጣን ላይ ነበሩ።እንድያውም ኮለኔል መንግስቱ በ አንድ ወቅት''ደርግ ደርግ የምትሉት እውን አሁን ደርግ አለን?'' ብለው በ 17 ዓመት ታሪካችን ለመጀመርያ ጊዜ  ከት ብለን እንድንስቅ አረጉን። ይህ የወታደራዊ ደርግ ታሪክ ነው። አሁን ባለንበት ጊዜ የሚያሰጋኝ ''የወታደራዊው ደርግ'' ሳይሆን '' የ ሽምቅ ተዋጊ ደርግ'' የሚል ስያሜ የምሰጠው የሰሞኑ ስጋቴ ነው።
ኮለኔል መንግስቱ እና ፊደል ካስትሮ


ከወታደራዊ ደርግ ወደ ሽምቅ ተዋጊ ደርግ ተሸጋገርን እንዴ ?

ሰሞኑን የ 2004 ዓም  ተሰናብተን የ 2005 ዓም ተቀብለናል።'' የጎመን ምንቸት ውጣ የገንፎ ምቸት ግባ' ባልንበት  ነገራችን  ሁሉ  '' የወታደራዊ ደርግ ውጣ የ ሽምቅ ተዋጊ ደርግ  ግባ'' እንዳይሆን  ሁለት ሶስት ጊዜ ማሰብ ይገባናል። ሀገራችን ለ ከፋ የታሪክ ጠባሳ የዳረጋት  እና ብዙ የማደግ እድሏን የገታባት ወታደራዊው ደርግ ዛሬም በ አሳዛኝ መልኩ ብናስበውም  ከላይ እንደተጠቀሰው አፄ  ሃይለስላሴ ''ሀገርንም በሰላም ጊዜ የሚሰራበትን ጥፋትም ሲመጣ የሚመከትበትን በማሰናዳት መሆኑን ይህ በ ጦር ሰራዊታችን ውስጥ የታወቅ ሳይሆን ይቀራል ብለን አንጠረጥርም'' እንዳሉት። የሀገር አንድነትን በተመለከተ በ ብሔራዊ አንድነት ላይ እና በ ርዮተ ዓለም ላይ በነበረ አመለካከት ላይ በተመሰረተ ልዩነት እንጂ በ ዘር፣በ ክልል መከፋፈል የማያምን መሆኑ በራሱ የሚያስመሰግነው ነው-ደርግን ። በ እዚህ ፅሁፌ መግብያ ላይ የ ደርግ ትርጉምን ስንመለከት የ ደርግ ባህርያት የግለሰብ ፈላጭ ቆራጭነት ቢታይበትም በደርጉ ምክርቤት እየቀረቡ የወሰኑ የነበሩት ነገሮች አስደንጋጭ  እንደነበር ለመግለፅ ሞክርያለሁ።

አቶ መለስ ዜናዊ ከ እዚህ ዓለም በ ሞት ከመለየታቸውም ሆነ ከተለዩ በኋላ የስልጣን ውዝግቡ በ ኢህአዲግ ውስጥ ቀጥሏል።ይህ ብቻ አይደለም ማን ሀገሪቱን እየመራ ለማወቅ መብት የሌለን ህዝቦች ብቻ ሳንሆን። ጠቅላይ ሚንስትሩ እንዴት እንደታመሙ፣መቼ አንደታመሙ፣የት እንደታከሙ፣ስታከሙ ምን አንዳሉ፣ማን አንዳስታመማቸው፣አስከሬናቸው ከየት ሀገር ከየት ሆስፒታል ወደ አዲስ አበባ አንደገባ (ኢቲቪ የ አቶ መአስን አስከሬን የያዘው  አይሮፕላን አዲስ አበባ  ማረፉን አንጂ ከየት እንደገባ እስካሁን የተናገረ አይመስለኝም) ሁሉ ያልተነገርን ለመነገርም ያልተከበርን ሆነናል። ከአንዳንድ ዜናዎች እንደምንሰማው ሀገሪቱ ለ ይስሙለ ጠቅላይ ሚኒስትር ወደፊት ኢህአዲግ የሚሾምላት ቢሆንም አመራሩ ግን ሰባት ኮሚቴ ባሉት የ ፓርቲው አባላት እንደሚያዝ ሳይታለም የተፈታ ሆኗል።ይህ ኮሚቴ ስራውን በይፋ ለመጀመሩም ማስረጃ የሚሆነው። ጠቅላይ ሚኒስትር እንምረጥ በሚል አንድ ጊዜ ምክርበቱን ሌላ ጊዜ ፓርቲው ተደጋጋሚ ስብሰባ አድርገው አለመሳካቱ በይፋ ከታወቀ በሁዋላ እና ፓርቲው እራሱ በ መስከረም የመጀምርያ ሳምንት ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር  ማን እንደሚሆን እናሳውቃለን ብሎ በማሳወቅ 'ጠቅላይ ሚኒስትር አለን ይሆን እንዴ ?' እያልንየተጠራጠርንን ወገኖች ሁሉ በ ግልፅ 'የላችሁም በመስከረም የመጀምርያ ሳምንት ላይ አሳውቃለሁ' ያለን ኢህአዲግ በ ጠቅላይ ሚኒስትር ብቻ እንዲሰሩ የታዘዙትን ስራዎችለምሳሌ ለ 37 መኮንኖችከፍተኛ የ ወታደራዊ ማረግ በመስጠቱ  የሽምቅ ተዋጊ ደርግ ስራውን ጀመረ እንዴ?  እንድል አድርጎኛል።

የኢትዮጵያ ጥያቄ በ ሽምቅ ተዋጊ ደርግ አይመለስም

ኢህአዴግ ሃያ አንድ አመታት የ ኢትዮጵያን ሕዝብ በደንብ ለመረዳት ከ በቂ በላይ የሆነ ጊዜ ከ አምላክ ተችሮታል።ከሀገሬ ከመውጣቴ (ከዛሬ ሁለት ዓመት በፊት) በሥራ አጋጣሚዎች የማገኛቸው አፍቃሪ ኢህአዴግም ሆኑ አባላቱ ያማይባቸው አንድ የጋራ የሆነ ባህሪ  አለ። ይሄውም ችግሮች መኖራቸውን ያውቃሉ። ግን በጊዜ የሚረሱ ይመስሏቸዋል።መፍትሄዎቻቸው ለዛሬ ህዝብን አታሎም ይሁን አስረስቶ ዛሬን ማለፍ ከተቻለ ነገ ችግር የለውም ብለው ያስባሉ። ዛሬ ያልተፈታ ችግር ነገ ተራራ ሆኖ የማይወጡት ዳገት ይሆናል ብሎ የሚያወራ ሁሉ እንደነሱ አገላለፅ ይህ ሰው ሌላ ሳይሆን  ''ጨለምተኛ'' አስተሳሰብ የያዘው ነው ይላሉ። ነገሮችን ሁል ጊዜ የሚመለከቱት ከደርግ ጊዜ ጋር በማነፃፀር ሲሆን ዲሞክራሲን በተመለከተ ህዝቡ ገና ብቁ አይደለም ፣ለ እዚህደረጃአልደረሰም፣የሚለውንፕሮፓጋንዳ መሰልነገር እንደ 'ነጠላ ዜማ' መልቀቅ አዲሱ ፋሽን ብቻሳይሆን ዝቅተኛ ገቢ  ባለው ሕብረተሰብ ዘንድ እና ለመረጃ ብዙምቅርብ ባልሆነው ሕዝብ መሃል ለማሳመን ጥረት የተደረገበትም ሙከራ መኖሩን አስታውሳለሁ።

መሰረታዊው የኢህአዴግ ችግር ግን ዘመኑን አለመዋጀት ችግር ነው

 ዛሬም 1983 ላይ ሆነን ካሰብን በጣም ተሳስተናል። በ ዓለም ላይ የሚገኙ የ ወታደራዊ ደርግም ሆኑ የ ሽምቅ ተዋጊ ደርጎች መሰረታዊ ስህተት የ ትውልዱ አስተሳሰብ መምጠቁን ሳይረዱ ባሉበት ጎርፍ ይዞ ወዳልፈለጉበት እና ወደ አልተመኙት ቦታ ይዞአቸው መሄዱ ነው። የ የትኛውም መግስት ትልቅነት የሚለካው ዘመኑን መዋጀት በመቻሉ እና በ  አዲሱ ትውልድ አስተሳሰብ ተገብቶ ማሰብ በመጀመር አና ባለመጀምሩ መሃል ባለው ልዩነት ነው።

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ኦባማን መመረጥ የማይፈልጉ በ ገንዘብም ሆነ ባማናቸውም ኃይል እና ጉልበት ያላቸው አሜሪካውያንን ይዛ ነበር አሜሪካ ኦባማን የመረጠችው። እነኝህ ኃይሎች ሕግ እና ስርዓት ብቻ ሳይሆን ያገዳቸው አንድ እውነታ ነበረ። የ አዲሱ ትውልድ ፍላጎት። እዲሱ ትውልድ ኦባማን ፈለገ በቃ። ሁሉ ነገር በ አዲሱ ትውልድ እና በ ህዝቡ ፍላጎት ብሎም ነገ መሰራት ያለባቸው ስራዎች ዘመኑን የዋጁ መሆን አለባቸው እና ኦባማ ሰተት ብለው ሲገቡ ያልፈለጉአቸውም አብረው ዘመሩላቸው።ኢህአዲግ ሃያ አንድ ዓመት በ አዲስ አበባ ስቀመጥ  ከ አዲሱ ትውልድ በ ክልል መወለድ ሳይሆን በ ርዮተ ዓለም ደረጃ አሳምኖ ያመጣው  አንድ ሰው ካለው እስኪ ለ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ይቅርና  ለ አዲስ አበባ  ከንትባነት ያምጣ እና  ያሳየን።ይሄው ሃያ አንድ ዓመት ሙሉ  የድሮ ታጋዮች ብቻ ናቸው ሲቀያየሩ የሚታዩት።ከ አዲሱ ትውልድ አስተሳሰብ እና ከ ህዝቡ ጋር መች ተዋሐደ? ይህ የሚያሳየን የ ኢህአዲግ ፖሊሲዎች ሕዝቡን ይልቁንም አዲሱን ትውልድ ያገለለ መሆኑን ነው። በ አነስተኛና ጥቃቅን መደራጀት እና ፖሊስን መደገፍ ይለያያሉና።
ኢህአዴግ አሁንም 1983 ዓም ላይ ያለ ለመሆኑ  ስራዎቹ እያሳበቁበት ነው። ብዙ ማስረጃውችን ማንሳት ይቻላል።

ለምሳሌ አዲስ አበባ የገባበትን በዓል ግንቦት ሃያን  ሲያከብር አራትኪሎ ቁጭ ብሎ ልክ ከ ባዕድ ወታደር ጋር ተዋግቶ እንዳሸነፈ ሁሉ ቀን ሙሉ 'ግዳዩን' ሲያወራልን ይውላል።  በ እርስበርስ ጦርነት ዘመዶቻቸው የሞቱባቸው ግን ከስሩ ቁጭ ብለው የሞቱትን ያስባሉ። በኢትዮጵያ በስልጣን ሽምያም ሆነ በተለያዩ ምክንያቶች ከ ጥንት ጀምሮ  ነገስታት እርስ በርስ ተዋግተዋል። አንዳቸውም ግን ከወገናቸው ጋር ላደረጉት ውግያ 'ግዳይ' እንደጣለ ማስታወሻ ሀውልት ያቆሙ የሉም።እዚህ ላይ ሃውልታቱ የ ጊዜውን ታሪክ ጠባሳነት  የሚያሳዩ ብቻ ተደርገው የተሰሩ ቢሆን ባልከፋ። ታሪክ የተጀመረው ከ እዚህ ነው የሚል አንደምታ ያለው ሥራ እና የ እርስ በርስ ጦርነትን እንደ ትልቅ ገድል ማቅረቡ ከፋ እንጂ።ይህ ብቻ አይደለም ባለፉት 20 አመታት ውስጥ ዓለም እንደነበረች አይደለችም። በዘመነ ኢህአዲግ ቴክኖሎጂ ለ ዓለም ካበረከታቸው እና ሕዝባችንም እየተጠቀመበት ያለው የ ኢንተርኔት እና የ ሳተላይት ዲሽ ቴቪ አገልግሎት የ ሕዝቡን የመረጃ የማግኘት እና በሌላው ዓለም ምን እየተደረገ እንዳለ ለማወቅ ትልቅ እድል መክፈት ብቻ ሳይሆን ከ ክልላዊ አስተሳሰብ ወደ ሃገራዊ ብሎም ወደ ዓለም አቀፍ አስተሳሰብ መሸጋገሩን  እንዲሁም ለ እራሱ ብቻ ሳይሆን ለሌላ ሀገር ነዋሪዎችም ሕይወት እያሰበ እንዲመጣ ማድረጉን እንገነዘባለን። ኢህአዲግ ግን አሁንም 1983 ላይ ነው። ሁለት ክስተቶች ለ ኢህአዴግ የ ኢትዮጵያን ሕዝብ ለመረዳት ትልቅ ዕድል ፈጥረውለት ነበር።አንዱ የ 1997 ዓም ምርጫ  ሲሆን ሌላው የ ሰሞኑ የ አቶ መለስ ስርዓተ-ቀብር ናቸው።
አሁን በምንኖርበት ዓለም ውስጥ ሕዝብ የሚመራው ፍላጎቱ እና ሃሳቡ በሳይንሳዊ መንገድ በተደገፈ መረጃ እና የጥናት ውጤት እንጂ በዘፈቀደ የተወሰኑ ሰዎች ተሰብስበው እንደፍላጎታቸው በወሰኑት ሊሆን አይገባውም።በ 1997 ዓም የተደረገውን ምርጫ እንደ ጥናታዊ (research ) መጠይቅ እናስበው። መጠይቁ ከተበተነላቸው ሰዎች ስንቶቹ በምን አይነት ሃሳባቸውን ሰጡ? ለምን ኢህአዴግን አልደገፉም? ትልቁ ጉድለት  ምንድን ነው? የትኛው ፖሊስ አያስኬድም? የቱ ጥሩ ነው? ብሎ የማሰብያ ጊዜ የሚሰጥ ትልቅ የጥናት ውጤት ነበር። ግን አልሆነም  ኢህአዲግ በተወሰኑ መድረኮች ይህን መሰል የዳሰሳ  ሥራ የሰራ ቢመስልም ድምዳሜው ግን ካድሬ ተኮር የሆነ እና መንገድ እና አነስተኛና ጥቅቅንን በደንብ እናስፋፋ ህዝቡ ያን ጊዜ  ይወደናል የሚል የተናጥል ድምዳሜ ላይ ተደርሶት አረፈው።

ሁለተኛው የአቶ መለስ የሰሞኑ የቀብር ስርዓት እና የህዝቡ ተሳትፎ ነው። ከላይ ለማውሳት እንደሞከርኩት ህዝቡ በ ሃያ ዓመት ውስጥ በተፈጠሩት የ ቴክኖሎጂ እድሎች ከ ሃገራዊ ጉዳዮች ሃሳብ አልፎ ዓለም አቀፍ አካልነቱ ገብቶታል።አቶ መለስን የምያወሳቸው  ''እጅ እንቆርጣለን፣መንገዱን ጨርቅ ያርግላችሁ'' በሚሉት ንግግራቸው አይደለም።ኢትዮጵያን በመወከል በዓለም  አቀፍ ስብሰባዎች በመገኘታቸው እንጂ። አቶ መለስን ከ አድዋ አና ኤርትራ  መወለዳቸውን ህዝቡ የረሳው በ 1983 ''ይች ሀገር '' እያሉ ኢትዮጵያን መጥራት ሲጀምሩ ነው። በቃ! የ ኢትዮጵያ መሪ ናቸው ብሎ ነገር አለሙን  ትቶ ስለ ዓለም ማሰብ ጀመረ። ኢህአዲጎች:ግን:አቶ መለስ መሞቱን ሲነገረው የ:ህዝቡ ምላሽ  ምን ይሆን? እያሉ ሲያስቡ ዓለም አቀፉ ሕዝብ ስለ አፍሪካ፣ ስለ አየር ንብረት ጥበቃ ፣ ወዘተ አቶ መለስን እያነሳ ''ሞታቸው ያሳዝናል'' አለ።  ይህ ብቻ አይደለም ከ አሁን በሁዋላ ኢህአዲግ ወደ እኔ ዓለም አቀፍ አስተሳሰብ ይመጣል ብሎ ተስፋ አደረገ-ህዝቡ። ኢህአዴግም ፍንጭ አሳየ። የ ''ፍትህ'' ጋዜጣ አዘጋጅ ተመስገንን ብንን ብሎ እንዳሰረው ብንን ብሎ ''ወደቤትህ ሂድ'' ብሎ ፈታው። ሌሎች በ ሺህ የሚቆጠሩ እስረኞችን ፈታ።'' ዘንድሮ በግ እና ዶሮ ባልበላም ዘመኑ ጥሩ ሳይሆን አይቀርም'' አለ ህዝቡ። እርቅ ናፈቀው።በ አቶ መለስ ዘመን የጠፉ ነገሮች ሁሉ አሁን እናያቸዋለን ብሎ ጠበቀ።ትንሽ:እንደቆየን (በሰአታት:ልዩነት)'ለ:ሰላሳ ሰባት መኮንኖችየ ብርጋዴር ጀነራልነት እና:የ ጅነራልነት ማአረግ ኢህአዴግ ሰጠ  ተባለ።:በየትኛው:የ:ሕግ አግባብ?ይህ ተወሰነ?አቶ መለስ ያስወሰኑት ነው እንዳይባል አቶ መለስ ከታመሙ  ከሶስትወርበላይ ሆኗል።የ እዚህጊዜ ቢያንስ እንደ እኔ ግንዛቤአጥር ማጥበቅ መያዙካለፈው ታሪካችንገባኝ።ከሁሉም ደግሞ የሳምንት ጊዜጠብቆ ጠቅላይ ሚኒስትሩን መርጦ ወደስራ ለመሄድ የተቸኮለው ''እውን  አሁን ደርግ አለን?''  ብለው ኮለኔ ል መንግስቱ ሃይለማርያም በ 1980ዎቹ መጀመርያ  አካባቢ እንዳሳቁን '' እውን ከ ወታደራዊ ደርግ ወደ ሽምቅ ተዋጊ ደርግ ተሻገርንን?'' የሚል ጥያቄ ጫረብኝ -ውስጤ ። እነሆ አሁንም ልብ እንገዛ ዘንድ ሕዝብ እና እግዚአብሔር ምስክር ሆነው ይመለከቱናል።
አበቃሁ።

ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ 
ማጣቀሻ 



 

2 comments:

Mekonnen Aderaw said...

“... አፍቃሪ ኢህአዴግም ሆኑ አባላቱ የማይባቸው አንድ የጋራ የሆነ ባህሪ አለ። ይሄውም ችግሮች መኖራቸውን ያውቃሉ። ግን በጊዜ የሚረሱ ይመስሏቸዋል።መፍትሄዎቻቸው ለዛሬ ህዝብን አታሎም ይሁን አስረስቶ ዛሬን ማለፍ ከተቻለ ነገ ችግር የለውም ብለው ያስባሉ። መሰረታዊው የኢህአዴግ ችግር ግን ዘመኑን አለመ ዋጀት ችግር ነው።”

Anonymous said...

yemigerm tintena new. negeru hulu endalkew new yemimeslew zare Hailemaryamn ye parti sebsabi argewtal. Ethiopia sew yelelat liareguat new enesu powerun be remot liashkerekru yshalu. Almost YESHIMIQ DERG LIGEZAN NEW.

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።