ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, September 11, 2020

ከዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ማኅበራት አንድነት ጉባኤ በኢትዮጵያ፣ በክርስቲያኖች ላይ ስለሚደርስ ተደጋጋሚ ጭፍጨፋ እና ኢፍትሃዊነት ላይ የተሰጠ መግለጫ


መግለጫው በአሁኑ ሰዓትም ክርስትያኖች በአሸባሪዎች ዛቻ እየደረሰባቸውና ቀጣዩንና መጪውን ጊዜ በመፍራት ላይ ስለሚገኙና አሸባሪዎች ለበለጠ ጥፋት እየተዘጋጁ ስለሆነ ለሚመለከታቸው አካላት ማሳሰቢያ ሰጥቷል።

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡ 

ዓለም አቀፍ የምእመናንና ማህበራት ጉባኤ በክርስትያኖች ላይ የደረሰውን ዘግናኝ ጭፍጨፋና ያስከተለውን ጉዳት ሲያጣራና ሲከታተል ቆይቷል። በጭፍጨፋው ምክንያት የተበተኑትን ወደቀያቸው ለመመለስ፤ የተጎዱትን ለመካስና አጥፊዎችን ለፍርድ ለማቅረብ የሚደረጉትን ጥረቶች ሲያግዝና ሲከታተልም ነበር። ነገር ግን እነዚህ ጥረቶች በሚገባው ፍጥነት ውጤት አለማምጣታቸው ብቻ ሳይሆን አሁንም ክርስትያኖች በአሸባሪዎች ዛቻ እየደረሰባቸው ስለሆነና አንዳንድ ሰዎች የደረሰውን የአሸባሪዎች ጭፍጨፋ በግልጽ ሲደግፉና የደረሰውን ዘግናኝ ጉዳት በተለያዩ ሚድያዎችና መንገዶች ሲያስተባብሉ ስለታዘበ ጉባኤው ይህን መግለጫ ለመስጠት ተገዷል። 

በመላው ዓለም ለመጀመርያ ጊዜ ክርስትና በሰላም እንበለ _ደም በፍቅር ተሰብኮ ሀገራዊ ኃይማኖት የሆነው በአፍሪካ ምድር በሀገረ ኢትዮጵያ ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በብዙ መከራ ውስጥ ጸንታ ዘመናትን ተሻግራ ሀገር ሁናና ሀገር መስርታ የሌሎችን እምነትን አክብራና አስከብራ የሰው ልጅ በነጻነት በፍቅርና በመተሳሰብ እንዲኖር ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያደገችም ነው። 

ቤተክርስቲያኗ የተመሰረተችው በመስቀል ፍቅር፣ በክርስቶስ ደም ስለሆነ የሰው ልጅ በፍቅርና በሰላም ተከባብሮ እና ተሳስቦ እንዲኖር ምንጊዜም ታስተምራለች፤ የሰው ልጅ ሁሉ በእኩልነት እንዲኖርና ፍትህ እንዲሰፍን ትሰራለች። ይህንን የፍቅር ጥሪ በመቃወም እና ተከባብሮ እና ተሳስቦ የመኖር እሴትን በመጠየፍ ሰውን በአሰቃቂ ሁኔታ የሚገድሉ፤ ሴቶችን በኃይል የሚደፍሩ፤ ህጻናትን የሚገድሉ አብያተ ቤተክርስቲያናትን የሚያቃጥሉ ሰው ወጥቶ ወርዶ ያፈራውን ንብረት የሚዘርፉ የሚያወድሙ፤ በኃይል የግላቸውን እምነት ሌሎች ላይ በኃይል የሚጭኑ፣ ዓለም አቀፍ ትስስርና ትብብር ያላቸው አሸባሪዎች በአሁኑ ሰዓት በተለያዩ ሀገራት በተለያየ ስሞች ይገኛሉ። ከእነዚህ መካከል ጎልተው የሚታወቁትን ለመጥቀስ ያህል አልቃይዳ፤ አይሲስ፤ አልሸባብ፤ ቦኮ ሀራም፤ ፉላኒ ኢስላሚክ ቡድንና ሌሎችም ይገኙበታል። 

እነዚህ ዓለም አቀፍ አሸባሪዎች በኢትዮጵያ ስማችውንና የሽብር ዘዴአቸውን ቀይረው በቅርብ ዓመታት ውስጥ ብዙ ክርስቲያኖችን በገጀራ ቀልተው፤ በቆንጨራ ቆራርጠው፤ በጦር ወግተው በጩቤ ዘክዝከው፤ በሜንጫ ተልትለው፤ በዱላ ቀጥቅጠው እና በደንጊያ ወግረው ገድለዋል። አስከሬናቸው በጎዳና ጎትተዋል። አስከሬናቸው በአራዊት እንዲበላ አድርገዋል ። ሽማግሌዎችን አርደዋል። ነፍሰጡሮችን አሰቃይተው ገድለዋል። ህጻናትን በወላጆቻቸው ፊት አርደዋል። ሴቶችን፥ በልጆቻቸው፣ በአባቶቻቸው እና በባሎቻቸው ፊት ደፍረዋል። ክርስትያኖች ለዘመናት የደከሙበት ቤት ንብረታቸውን፣ ዘርፈዋል። ቀሪውን ጋዝ እያርከፈከፉ አቃጥለዋል። ክርስትያኖችን በኃይል አስገድደው አስልመዋል። ቤተ ክርስቲያናትን አቃጥለዋል። ክርስትያኖች ከቤታቸውና ከቀዬአቸው ተፈናቅለው በመቃብር ቤቶች በልዩ ልዩ መንግሥታዊ ተቋማት እንዲሁም፣ በግለሰቦች ቤቶች ተጠልለዋል። ለአስከፊም ማኅበራዊ እና ሥነ ልቡናዊ ቀውሶች ተዳርገዋል። አሸባሪዎቹ ክርስትያኖችን የማጽዳት ዘመቻ ብለው በጀመሩት ጭፍጨፋ በኦሮምያ ክልል “ከክርስትያኖች የጠዳ ምድር” በማለት የለዩአቸው አካባቢያዎች አሉ። እነኝህ በክርስትያኖች የደረሱት የዘር ማጥፋት ወንጀሎች በጠንካራ መረጃና ማስረጃ በደንብ የተያዙ ስለሆነ አስፈለጊ ሲሆን ጉዳዩ ለሚመለከተው አካል ማቅረብ እንችላለን። 

አሸባሪዎቹ ባለፉት ጥቂት ጊዜያት የፈጸሟቸውን የዘር ማጥፋት ወንጀሎችን ለአብነት ያህል በማሳያነት ለመጥቀስ፤ 

● ከሰኔ 22 ቀን ምሽት ጀምሮ እስከ ሰኔ 24 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ ባሉት ሦስት ተከታታይ ቀናት በኦሮምያ ክልል በተፈጸመ ጥቃት፥ 67 ምእመናን በግፍ እና በአሠቃቂ ኹኔታ ተገድለዋል፤ 38 ምእመናን ቋሚ(ከባድ)፣ 29 ምእመናን ደግሞ ቀላል የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ ኮኮሳ ሆጊሶ መድሃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሙሉ ለሙሉ ተቃጥሏል።ከ 530 በላይ የክርስቲያኖች መኖርያ ቤቶች ከ200 በላይ ሆቴሎችና ከ6 በላይ ፋብሪካዎች ተቃጥለዋል;፤ ከ500 በላይ መኖርያ ቤቶችና ከ35 በላይ ሆቴሎች ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል። በገጠር አካባቢ በማሣ ላይ ያሉ ሰብሎችም ወድመዋል። ባለሃብት የነበሩ ክርስትያኖች በአንድ ጀንበር ተመጽዋች ሆነዋል። ከ7000 በላይ ክርስትያኖች ከመኖሪያቸው ተፈናቅለው በመቃብርና በተለያዩ ቦታዎች ተሰባስበው የመላው ዓለምን ድጋፍ እየጠበቁ ይገኛል። እነዚህ ክርስትያኖች በተለያየ ደረጃ ለሚገለጽ ሥነ ልቦናዊ እና ሥነ አእምሯዊ ቀውስም ተዳርገዋል። የብዙዎች ቤተሰብ አባላት ተበትነዋል። አሸባሪዎቹ ሙሉ በሙሉ የቤተሰብ አባላትን፤ ሽማግዎችን፣ ህጻናት ሴቶችን ጭምር አርደዋል። ለምሳሌ በኦሮሚያ ክልል ዝዋይ አዳሚ ቱሉ በእነዚህ አሸባሪዎች አንድ ሙሉ ቤተሰብ (አባት፤ እናትና ሶስት ልጆች) እጅግ አሰቃቂ በሆነ መልኩ አርደዋቸዋል። በአርሲ ነገሌ ደግሞ ከመግደልም አልፈው ሬሳው እንኳን በክብር እንዳይቀበር ዘቅዝቀው የሰቀሉት አለ፡፡ 

● በጥቅምት 2012 ዓ;ም በኦሮምያ ክልል 31 አብያተ ክርስትያናት ተቃጥለዋል፤ 97 ክርስትያኖች በግፍ ተገድለዋል፤ ከ40 በላይ በውል የታወቁ የመንዲሳ (ምስራቅ ሐረርጌ)) ነዋሪዎች፣ ቤት ንብረታቸው ከተቃጠለ በኋላ ዓይናቸው እያየ ልጆቻቸው እንዳይታረዱ ሲሉ ተገደው ሰልመዋል። ከ17 በላይ የምእመናን ንብረት የሆኑ ሆቴሎች ተቃጥለዋል። ከ80 በላይ የክርስትያኖች መኖርያ ቤቶች ሙሉ በሙሉ ወድመዋል። የክርስትያኖች ንብረት የሆኑ መኪኖችና ባጃጆች ተቃጥለዋል። 

● በመጋቢት ወር 2011 እና በመስከረም 2012 በአማራ ክልል በኦሮምያ ዞን በአጣየ ብቻ 57 ክርስትያኖች በግፍ ተገድለዋል፤ 68 ክርስትያኖች ከባድ እና ቀላል የመቁሰል አደጋ ደርሶባቸዋል። የካራ ቆራ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን ተቃጥሏል። 

● በኢትዮጵያ እነኝህን የአሸባሪ ጥቃት አድራሾች ከአልሸባብ ወይም ከቦኮ ሀራም በተግባር በዓላማና በሚፈጽሙት ሽብር ተመሳሳይ ሲሆኑ በሚከተሉት ጉዳዮች ይለያሉ። 

1) ሽብር የሚፈጽሙት በሀገር ወይም በክልል አልያም በአንድ አካባቢ የሚከሰትን ፖለቲካዊ ነውጥ ወይም ክስተት ጠብቀው ወይም ሽፋን አድርገወ ነው። ለምሳሌ ከሰኔ 22 ቀን ምሽት ጀምሮ እስከ ሰኔ 24 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ ባሉት ሦስት ተከታታይ ቀናት የደረሱት የአሸባሪዎች ጥቃት የታዋቂውን ክርስትያን አርቲስት የሃጫሉ ሁንዴሳን ሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. ምሽት በአዲስ አበባ ግድያ እና ግድያውን ተከትሎ የተከሰተውን አለመረጋጋት እንደሽፋን በመጠቀም የተፈጽመ ነው። ከላይ በሁለተኛ ደረጃ የተጠቀሰው የሽብር ጥቃት በጥቅምት 12፣ 2012 ዓ.ም. አንድ ፖለቲከኛ ያስተላለፈውን መግለጫ ተከትሎ በርካታ ወጣቶች ወደ ሰልፍ ወጥተው ቅሬታቸውን በመግለጽ ላይ በነበሩበት ወቅት ምሽት የየአካባቢው ነዋሪ ያልሆኑ ጸጉረ ልውጥ ሰዎች በየአካባቢው ተጠራርተው በመንቀሳቀስ በክርስትያኖች ላይ ጥቃት አድርሰዋል።

2) አልቃይዳ፤ አይሲስ አልሸባብ ውይም ቦኮ ሀራም ሽብር ፈጽመው ኃላፊነት ይወስዳሉ፤ በኢትዮጵያ የሚገኙ አሸባሪዎች ግን ኃላፊነት አይወስዱም። ማንነታቸውንም አይገልጹም። እንዲያውም በተለያየ መልኩ በሚያደራጇቸው በሚረዷቸውና በሚደግፏቸው ሰዎች አማካይነት ምንም ችግር እንደሌለ፤ የማንም ክርስትያን ዝንብ እንኳን እንዳልነተካው አጥብቀው በየሚድያው እየጮሁ ሽፋን ይሰጧቸዋል። ትክክለኛ ዑላማዎችና ሙስሊሞች አሸባሪዎችን ለማውገዝና ድርጊታቸውን ለመንቀፍ ሲሞክሩ ከአሸባሪዎቹና ከደጋፊዎቻቸው የተቃውሞ ዘመቻ ይደረግባቸዋል። የመንግስት ባለስልጣናትን አጥብቀው ይጎተጉታሉ። ጫና ይፈጥራሉ። አስፈለጊ መስሎ ሲታያቸው የክርስትያኖችን የድረሱልን ጩኸት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በማድረግ እውነተኛው ሙስሊም ከእነርሱ ጋር እንዲሆን ይቀሰቅሳሉ፣ ጫናም ያደርጋሉ። መንግስት ክርስትያኖችን ዝም እንዲያሰኛቸው ጫና ይፈጥራሉ።

3) በስልጣን ላይ የሚገኛው የኢትዮጵያ መንግስት የክርስትያኖች መከራ እንዳይሰማ ጫና ይፈጥራል። አሸበሪዎች በነጻነት እየተንቀሳቀሱ ብቻ ሳይሆን አሁንም ክርስትያኖችን እያሳደዱ መንግስት ግን ጭራሽ ክርስትያኖችን (ድምጻችን ይሰማ) ያሉትን ያስራል። ዶዶላ በጥቅምት 2012 ዓ.ም. አሸባሪዎች ቀርተው ክርስትያኖች እስካሁን ድረስ ያለምንም ጥፋት እንደታሰሩ ነው። በጉዳዩ ላይ ማብራርያ እንዲሰጠው ሄውማን ራይትስ ወች ባላፈው መጋቢት ወር ቢጠይቅም ከኢትዮጵያ መንግስት አስካሁን መልስ አላገኘም።

4) በኢትዮጵያ አሸባሪዎች እንቅስቃሴና ሽብር እንዲሁም የክርስትያኖች የመከራ ህይወት በዓለም መድረክ ያልተነገረ፤ ሚድያው በቅጡ ያልዘገበው፤ በተዘጋ ቤት ውስጥ የሚነድ አደገኛ አሳት ነው። 

በአሁኑ ሰዓትም ክርስትያኖች በአሸባሪዎች ዛቻ እየደረሰባቸውና ቀጣዩንና መጪውን ጊዜ በመፍራት ላይ ይገኛሉ። አሸባሪዎች ለበለጠ ጥፋት እየተዘጋጁ ስለሆነ ለሚመለከታቸው አካላት የሚከተለውን ጥሪ አናደርጋለን። 

1) ተጎጂዎች በሃይማኖታቸው ምክንያት በደረሰባቸው የአሸባሪዎች ጥቃት የተነሣ፣ ቤተሰባቸውን አጥተዋል። ወጥተው ወርደው ያፈሩት ሀብት ንብረት በአንድ ጀንበር ወድሞባቸው በአሁኑ ወቅት በመቃብር ቤቶች፤ በቤተ ክርስቲያን አዳራሾች እና በግለሰቦች መኖሪያ ቤቶች ተሰብስበው ይገኛሉና የኢትዮጵያ መንግስት ለሞቱት ቤተሰቦችና ሀብት ንብረታቸውን ላጡ ዜጎቹ አስፈላጊውን ካሳ በመክፈል ወደ ነበሩበት ህይወት ሙሉ በሙሉ መመለስ አስቸጋሪ ቢሆንም አንኳ ከዚህ በኋላ በሕይወት የመኖር እና ሀብት የማፍራት ሰብአዊ እና ዜግነት መብታቸውን በማስከበር፣ የደኅንነት እና የኑሮ ዋስትና በአፋጣኝ ሊያረጋግጥላቸው ይገባል፡፡

2) የሽብር ጥቃቱን ያቀዱትን፣ የፈጸሙትን ያስተባበሩትንና የተባበሩትን ኀይሎች እንዲሁም፣ የተጣለባቸውን ሓላፊነት ወደ ጎን በማለት ጥቃቱን በዝምታ የተመለከቱትን አልፈወ ተርፈው የተባበሩትን በመንግስት መዋቅር ውስጥ ያሉትን ሹማምንት እና የጸጥታ አካላት የኾኑ አጥፊዎችን፣ የኢትዮጵያ መንግስት ፥ በቁጥጥር ሥር በማዋል እና በሕግ ተጠያቂ በማድረግ ፍትሕ ርትዕ እስከ መጨረሻው እንዲሰፍን ማድረግ ይኖርበታል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ፥ ይህንን ኃላፊነቱን መወጣት በተለያየ ምክንያት ካልቻለ ጉዳዩን በዓለም አቀፍ ደረጃ ወደ ሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊ በሆኑ መንገዶች በማድረስ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የኢትዮጵያ መንግስት ሹማምንት እና ሌሎች አጥፊዎች በዓለም አቀፍ ደረጃ በህግ እንዲጠየቁ ለማድረግ እንገደዳለን።

3) የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎችን ከአሸባሪዎች ጥቃት የመጠበቅ ግዴታና ኃላፊነት አለበት ። ስለሆነም ይህ ረጅም ርቀት ተሂዶበት ከፍተኛ ዝግጅት ሲደረግበት የቆየ የአሸባሪዎች አስነዋሪ ተግባር እንዴት ከመንግስት ደኅንነትና ጸጥታ አካላት ክትትልና እይታ ውጭ ሊሆን እንደቻለ ወይንም እነኝህ የጸጥታ አካላት መረጃው ከነበራቸው ለምን አሸባሪዎችን ማስቆምና ዜጎችን ከጥቃቱ መከላከል እንዳልቻሉ መንግስት ምርመራ አድርጎ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድና ውጤቱንም ለህዝብ ይፋ ማድረግ ይኖርበታል። ከዚህ ጋር በተየያዘ ይህ የአክራሪ እስልምና የሽብር ጥቃት በዓለም አቀፍ የጆንሳድ ወይም የዘር ማጥፋት ህግ መሰረት አንድን ድርጊት ጆንሳይድ ለማለት ማሞላት ያለበትን ዝርዝር ጉዳዮች ሙሉበሙሉ በሚባል መልኩ ያሟላ ስለሆነ የኢትዮጵያ መንግስት የደረሰውን ጥፋት በዘር ማጥፋት ወንጀል ሊመለከተው ይገባል።

4) በኢትዮጵያ የፌዴራል መንግሥት፣ በተለይም ደግሞ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ሹማምንት በኦርቶዶክሳውያን ላይ የማሸማቀቅ፣ የማሳደድ፣ ከመንግስት የስልጣን መንበር ከማግለል ተግባራት እንዲታቀቡ። በስውርም ሆነ በግልጽ የተለያዩ ጫና በመፍጠር የመንግስት ስልጣንን ለማግኘት ወይም ያላቸውን ለማቆየት ኦርቶዶክሳውያን እምነታቸውን እንዲቀይሩ ለማድረግ የሚደረገው አስነዋሪ ተግባር በገለልተኛ አካላት እንዲጣራና የእርምት እርምጃ እንዲወሰድበት ይገባል። በአሁኑ ወቅት ያለውን የከፍተኛ ሹማምንት ስብጥርና የኦርቶዶክሳውያንን ውክልና መመልከት እየተደረገ ለቆየው ኦርቶዶክሳውያንን የማግለል አካሄድ አንድ ማስረጃ ነው። 

በፖሊተካ ጫና የተነሳ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የውስጥ ተፈጥሮ የነበረው የአስተዳደር ልዩነት ተወግዶ አንድነቷን ጠብቃ ለልጆቿና ለሀገር የሚገባውን አገልግሎት እንድታበረክት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ያደረጉትን አስተዋጽዖ እኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆች የማንረሳው በጎ ተግባር ነው። ነገር ግን ይህን የጠቅላይ ሚኒስትሩን በጎ ተግባር በተጻረረ መልኩ የቤተ ክርስቲያኗ አንድነት ተጠብቆ የሚገባውን አገልግሎት እንዳትሰጥ፤ አሁን የምናቀርበውን አይነት የፍትህ ጥያቄ እንዳታቀርብና መንግስትን ስለፍትህ እንዳትሞግት ይልቁንም የቤተ ክርስቲያኗ አንድነት እንዲጠፋና እንድትሸማቀቅ ከተቻለም ሙሉ በሙሉ እንድትዳከም በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የሚገኙ አንዳንድ ሹማምንት ጠርዝ የለቀቀ የብሔር ፖለቲካ አራማጆች ጋር በግልጽና በስውር በመቀናጀት ቤተ ክርስትያኗ የማታውቀው ነገር ግን በራሷ በቤተ ክርስትያኗ ስም ሕገ ወጥ ክልላዊ መዋቅር ያቋቁማሉ። የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣን የሆኑ ግለሰብ የቤተ ክርስቲያኗን መዋቅር የሚፈታተኑ እንቅስቃሴዎችን መምራታቸውና የቤተ ክርስትያኗን ክብር የሚያጎድፉ መግለጫዎችን በሚዲያዎቻቸው ላይ ጭምር ማሰራጨታቸውም አሁን ለተከሰቱት ችግሮች ቁልፍ ምክንያትና የማብረታቻ ግበዓት ሊሆን እንደሚችል ይታሰባል። እነዚህ አካላት አሁንም ድረስ ቤተ ክርስትያኗን ያሸማቅቃሉ፤ ያስፈራራሉ። የቤተ ክርስቲያኒቱ አሠራር ከሚፈቅደው ውጪ በየወረዳው ጽ/ቤቶችን ያቋቁማሉ፤ አህጉረ ስብከት የመደቧቸውን ኃላፊዎች በመሻርና በኃይል በማባረር የራሳቸውን ቡድን ይሾማሉ፡፡ የመንግሥት ሹማምንትም እነዚህን ሕገ ወጥ አካሄዶች ከማስቆም፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ከፍተኛ የሥልጣን ባለቤት ቅዱስ ሲኖዶስንም ከመስማት ይልቅ ይህን ድርጅት በመያዣነት በመያዝ ቤተ ክርስትያኗን በፈለጉት መልክ ለማሽከርከር ይሞክራሉ። እናም ይህን አስነዋሪ ተግባር የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ መንግሥት፣ ባስቸኳይ እንዲያስቆም ጥሪ አናቀርባለን። 

5) የኢትዮጵያ ኃይማኖቶች ተቋማት ጉባኤ በሃይማኖታቸው ምክንያት ብቻ ሰዎች ሲገደሉ ሀብት ንብረታቸው ሲወድምባቸው የአምልኮት ቦታዎች ሲቃጠሉና ሲደፈሩ “የእውነት አፈላላጊ” ኮሚቴዎችን አቋቁሞ ትክክለኝ መረጃዎችን ለህዝብ ማቅረብ ይጠበቅበታል.። ስለሆነም ከላይ የተጠቀሱትን የአሸባሪዎች ጥቃትን በተመለከተ በግልጽ ሊያወግዝና መግለጫ ሊያወጣ ይገባል። ይህ የአሸባሪዎች ጥቃት ሆነ እነ አልሸባብ አልቃይዳና ሌሎች ተመሳሳይ አሸባሪዎች የሚያደርጉት ጥቃት እውነተኛ ሙስሊሞችንና እስልምናን አይወክልም። የእነዚህ ነውረኛ አሸባሪዎች ጥፋት አሁን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለይ ይበርታ እንጅ ሁላችንም በአንድነት ካላስቆምነው ሁሉንም የእምነት ተቋማት ማዳረሱ በፍጹም አይቀርም። ስለሆነም የኢትዮጵያ ኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት በእምነት ተቋማት መካከል ውይይቶች ከታች ከህብረተሰቡ ጀምሮ እየተደረገ ለዘመናት በመተሳሰብ በፍቅር የኖርንበት እሴት እንዲጠበቅና አሸባሪዎችና ነውረኞች በህዝቡ ዘንድ አንዳይደበቁ የበኩሉን ኃላፊነት መወጣት ይኖርበታል።

6) በዚሁ አጋጣሚ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያናችን መዋቅራት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማሳካት፣ አስተዳደራዊ ሥራዎችን ለማዘመንና ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመሆን የምእመናንን ደኅንነት ለመጠበቅ የሚያደርጓቸውን ጥረቶች ለመደገፍ ምንጊዜም ዝግጁና ቁርጠኛ መሆናችንን ለመጠቆም እንወዳለን፡፡ 

እግዚአብሔር አምላክ ለሞቱት መንግስተ ሰማያትን፣ለቤተሰቦቻቸው መጽናናትን፣ ጉድትና ንብረት ለወደመባቸው ብርታትና ጥንካሬን ይስጥልን። 


እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና መላው ዓለምን ይባርክ። ሕዝቡንም በቸርነት ይጠብቅልን። 

ዓለምአቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ማህበራት አንድነት ጉባኤ 

ጳጉሜ 12012 

ኢሜል፡ office@eotcadvocacy.org 


No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...