ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, June 30, 2023

የዘመኑ ምሑር ችግር፣ትልቁን ሀገራዊ ስዕል ትቶ በጥቃቅን የመንደር ጉዳዮች የመዋጥ ችግር ነው።


=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

ኢትዮጵያ ትልቅ ሀገር ነች።በእኛ ዘመን እንደገባችን መጠንም ብቻ አይደለችም።ከ20ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ ጀምሮ የተነሳው ትውልድ የገጠመው የዕውቀትም ሆነ መጪውን የሚያመላክተው የኮከብ ምሑራን እጦት በእጅጉ ጎድቶታል። ከ1960 ዎቹ የተነሳው የተማሪዎች እንቅስቃሴ የመሩት ሐያዎቹን ያልዘለሉ፣በስሜት እና ከውጭ የግራ ክንፍ ጽሑፎች ባነበቡት የኢትዮጵያን ታሪክ ለመገልበጥ የሞከሩ መሆናቸው በቀጣይ ሀገሪቱን ወዴት እንደመራት እና ዛሬ ድረስ የእዚህ ሁሉ ውጤት ለጎሰኛ እና ስርዓት አልበኛ የፖለቲካ ድርጅቶች መፈልፈል አሳልፎ ሰጥቶትን ብዙ ነገሮች እንዲበላሹ አድርጎ ኢትዮጵያን ጎድቷል።

አሁን ያለው ምሑር ችግር ትልቁን ሀገራዊ ስዕል ትቶው በጥቃቅን ጉዳዮች መዋጥ። ትውልድ የሚያሻግረውን አጀንዳ ጥሎ ከከንፈር እስከ አፍንጫ የሚደርስ አጀንዳ አንጠልጥሎ መብረር እንደ አዋቂ እያስቆጠረ ነው።ይህ የሀሳብ ልዕልና የመውረድ ችግር በጊዜ ካልተገታ አጠቃላይ ውድቀት ያስክትላል። የሚድያ ውይይቶቹ፣ኢትዮጵያን በሚመለከት የሚቀርቡት የወቅታዊ ጉዳይ ተብለው የሚነሱት ርዕሶች ትውልዱ ትልቅ እና ተሻጋሪ ሃሳቦችን ላይ እንዲያሰላስል የሚያደርጉ ሳይሆኑ፣እገሌ የተባለው ማኅበራዊ ሚድያ ላይ የወጣው መረጃ ተብሎ ምሑራን ሃሳብ ይስጡበት ተብሎ የሚጠየቅበት፣ከተጨባጭ መረጃዎችና የጥናት ውጤቶች ይልቅ ''እየተወራ ያለው '' ተብሎ የሀገር ፖለቲካ የሚተነተንበት ሂደት ይህንን ትውልድ ከማስደንበር እና መጪውን ጊዜ አጨልሞ እያየ እንዲባንን ከማድረግ በላይ የነገዋን ኢትዮጵያ ፈጽሞ አይገነባም።

የኢትዮጵያን ፖለቲካ ስናነሳ የምናነሳበት ጥግ በጣም ደካማና የመንደር ጉዳይ ላይ ያተኮረ ከመሆኑ የተነሳ ኢትዮጵያን አስፈንጥረው የሚያነሱ አንኳር ጉዳዮችን ለትውልዱ ለማሳየት እና አጀንዳ ለመፍጠር ምሑራንም ሆኑ ጋዜጠኞች ሲጥሩ አይታይም። ለእዚህ ደግሞ ምክንያቶቹ ሁለት ናቸው። አንዱ ከፍተኛ የአቅም ማነስ እና ልዩነት ይታያል።ወቅታዊውን ጉዳይ አብስሎ የመከታተል፣የማንበብ፣ለማወቅ የመጣርና፣ያወቁትን እውነት ለማንጠር ያለመቻል ችግር በግልጽ ይታያል።ይህ አቅም ደግሞ በድንገት በአንድ ምሽት የሚመጣ አይደለም።ልምድ፣ዕውቀትና አንጥሮ የመለየት አቅም ማዳበር ላይ ብዙ ይቀረናል። ሁለተኛው ምክንያት ለተከታታይ ዓመታት በጠባብ የጎሳ አስተሳሰብ ስርዓት ውስጥ ተነክሮ የመውጣት ችግር ነው። ይህ ሁለተኛው ችግር በተለይ አጥብቦ የማየት ችግር በመሆኑ የተሻለ ነገር ለማማተር ስንኩል የሆነ አካሄድ አስከትሏል።

ባጠቃላይ ኢትዮጵያ ትልቅ ሀገር ነች።መጪው ትውልድ ደግሞ የዛሬ ጋዜጠኞች እና ምሁራን በሚያነሱት የአስተሳሰብ ልክ በየቀኑ እየተቀረጸ ይሄዳል። የዛሬ ምሁራን እና ጋዜጠኞች የሚያነሱት ትልቁን የኢትዮጵያ ጉዳይ ሳይሆን ጥቃቅን እና የመንደር ወሬዎች ላይ ባተኮሩ ቁጥር ለትልቋ ኢትዮጵያ የሚቆም ትውልድ እና የቱ የሀገሪቱ ትልቅ አጀንዳ መሆን እንዳለበት የማያውቅ ትውልድ ማፍራት ይጀመርና ኢትዮጵያን ወደ የባሳ አደጋ ይዟት ይሄዳል። የሀሳብ ልዕልና የመውረድ ችግር በጊዜ ካልተገታ አጠቃላይ ውድቀት ያስክትላል።ስለሆነም በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ የምትወያዩ፣ የምትጽፉ እና ወቅታዊ ጉዳዮች በሚል የሀገር ጉዳይ ላይ የምትናገሩ ሁሉ ከትናንሽ አጀንዳዎች ወጥታችሁ፣ ትልቁ፣ሀገራዊና ትውልድ ተሻጋሪ በሆኑ ሀሳቦች ላይ አትኩሩ።ትልቅ ሀገርን የሚመጥን አጀንዳ ከወሬ እና ከይመስለኛል ሀሳቦች የራቀ ጠንካራ እና ውስጥን የሚሰረስር ትውልድ የሚያነቃ ነው። 
==========///==========

Tuesday, June 13, 2023

ኢቲቪ ሊሸልማትና ለሴት ጋዜጠኞች ምሳሌነቷ በስራዎች ዙርያ ጥናታዊ ፊልም ሊሰራላት የሚገባው ከጋዜጠኛ ብዙ ወንድማገኘሁ ጋር የሀገሬ ቲቪ ያደረገው ቃለ መጠይቅ ክፍል 1 እና 2 ቪድዮ።

ኢትዮጵያን ተራራ እየቧጠጠች፣ቁልቁለት እየወረደች በኢቲቪ ''ተጓዥ ካሜራችን" ፕሮግራም አስተዋውቃለች።ከሀገር ወጥታም ለኢትዮጵያ ስትሟገት ኖራለች።በዘመነ ህወሓት ኢቲቪ ካለጡረታ አስወጣት።ከ20 ዓመታት ስደት በኋላ ሀገሯ ገብታ ከሀገሬ ቲቪ ጋር ቃለ መጠይቅ አድርጋለች። ኢቲቪ በክብር ጠርቶ ሊሸልማት፣ የጋዜጠኝነት ስራዋን በጥናታዊ ፊልም አዘጋጅቶ ምን ዓይነት ድንቅ ሴት ጋዜጠኞች እንዳሉ ለአሁኑ ትውልድ ሴት ጋዜጠኞች ሊያስተምርበት ይገባል።

ከድንቋ ጋዜጠኛ ብዙ ወንድማገኘሁ ጋር ሀገሬ ቲቪ ያደረገው ውይይት ክፍል 1 


ክፍል 2





Friday, June 9, 2023

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ዳግማዊ አፄ ምንሊክ ኢትዮጵያን በደን ለማልበስ የጀመሩትን በጎ ጅምር በማስቀጠላቸው ሀገራዊም፣ዓለም አቀፋዊ ሽልማት ይገባቸዋል።



  • ማመስገን ''አድርባይ'' በሚያስብልበት ዘመን ላይ ብንሆንም።ይህንን መልካም ስራ ሳያመሰግኑ ማለፍ ግን ፈጽሞ አይቻልም።
  • የዳግማዊ ምንሊክ የደን ልማት
  • አሁን ኢትዮጵያ እያለማች ያለችው የደን ልማት አጀማመር፣
  • የሚተከሉት ችግኞች ቁጥር እንዴት ታወቁ?
  • ዘንድሮ ለመትከል የታሰበው ምን ያህል ነው?

ማመስገን ''አድርባይ'' በሚያስብልበት ዘመን፣መሳደብ ተከታይ በሚያበዛበት ዘመን ላይ ብንሆንም።መልካሙን ስራ ሳያመሰግኑ ማለፍ ፈጽሞ አይቻልም።
  
ይህንን የጉዳያችንን ገጽ የዛሬ 11 ዓመት ስጀምር የመጀመርያ ጽሑፌ የማመስገን ባሕላችን ምን ያህል እንደተጎዳ በሚገልጽ ጽሑፍ ነበር።ለእዚህም ማጠናከርያ የሆነኝን የአዲስ አበባ ንግድ ሥራ ኮሌጅ መምህሬ ዶ/ር ማረው ዘውዴ ክፍል ውስጥ ስለ የማመስገን ባሕላችን የተናገሩት ነበር። የዛሬ 11 ዓመት የመጀመርያው የጉዳያችን ጽሑፍ ርዕስ እና ሊንክ ''የምስጋና አና የ ወቀሳ ባህላችን'' የሚል ነበር።

ዛሬ ላይ ለአንዳንዶቻችን መልካሙን ለማመስገን የሚያሳቅቅ፣መውቀስ (መውቀስ ተገቢ መሆኑ ሳይዘነጋ)፣መሳደብ እና ማጥላላት ግን ብዙ ተከታይ የሚያስገኝበት ጊዜ ነው።ብዙ ወቀሳ ካለ ሊዘለል የማይችለውን መልካሙን እና ዳግማዊ ምንሊክ ከአውስትራልያ ድረስ የበሃርዛፍ ችግኝ እያስመጡ ኢትዮጵያን በደን የማልበስ ግዙፍ ስራ ያስቀጠሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን በእዚህ የደን ልማት ስራቸው አለማበረታታት ፈጽሞ አይቻልም።

የዳግማዊ ምንሊክ የደን ልማት

ዳግማዊ ምንሊክ ኢትዮጵያን በደን የማልበስ እቅዳቸው ብቻ አይደለም አስደናቂ የሚያደርጋቸው።ከመቶ ዓመታት በፊት የአካባቢ ጥበቃ ሳይንስ ያላቸው ግንዛቤ እና የመጪው ዘመንን የኃይል ፍላጎት ቀድመው መተንበያቸው ነው።ንጉሱ ከአካባቢ ጥበቃ በላይ አስደናቂ የሚያደርጋቸው ተጨማሪ ሦስት ጉዳዮችም ናቸው

የእዚህ ጽሑፍ ርዕስ ወደሆነው የደን ልማት ጉዳይ ስንመጣ ንጉሱ ለኢትዮጵያ ያስተዋወቁት የበሃርዛፍ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ የአበባ እና የፍራፍሬ ዛፍ ዝርያዎችን (ለምሣሌ የኮክ ፣ የእንጆሪና የወይን ) ከአውሮፓ እያስመጡ አራብተዋል። የባሕር ዛፍ ወደ ኢትዮጵያ በንጉሰ ነገስቱ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጣ አድርገው እንዲራባ ባይደረግ ኖሮ በኢትዮጵያ ላለፉት አንድ መቶ ዓመታት ውስጥ ሊፈጠር የሚችለው የኃይል ክፍተት ቢጠና የንጉሰ ነገስቱ ውሳኔ ምን ያህል ለውጥ እንዳመጣ በሚገባ ለመረዳት ይቻል ነበር።

ከዳግማዊ ምንሊክ በኋላ በንጉሱ ዘመንም ሆነ በወታደራዊ መንግስት ዘመን የደን ልማት ስራ በኢትዮጵያ ተከናውኗል። በተለይ በወታደራዊው መንግስት ዘመን በሀገር አቀፍ ደረጃ ዘመቻዎች ተደርገው አሁን ድረስ የሀገሪቱ አሻራዎች ሆነው የሚታዩበት ማሳያ ቦታዎች አሉ።

አሁን ኢትዮጵያ እያለማች ያለችው የደን ልማት አጀማመር 
  • ሐምሌ 22 ቀን 2011 ዓ.ም 'አረንጓዴ አሻራ' በሚል ዘመቻ ጠቅላይ ሚንስትር ዐብይ አሕመድን ጨምሮ ከፍተኛ ባለሥልጣናትና የተለያዩ አካባቢ ነዋሪዎች በአገር አቀፍ ደረጃ የችግኝ ተከላ መርሐግብር በይፋ ተጀመረ።
  • ከእዚህ ዘመቻ በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ባዘጋጁት 'ገበታ ለሸገር' የእራት ግብዣ ላይ በሕንድ ተይዞ የነበረውን በመላ አገሪቱ ዛፍ የመትከል ክብረ ወሰን ለመስበር የሚያስችል ዘመቻ ለማካሄድ ማሰባቸውን በንግግራቸው ለመጀመርያ ጊዜ ይፋ አደረጉ።
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው "ሕንድ 100 ሚሊዮን ዛፍ በመትከል ክብረ ወሰኑን ይዛለች። እኛ በመላ አገሪቱ ሁለት መቶ ሚሊዮን ችግኝ ለምን አንተክልም?" በሚል አባባል ገልጸውት ነበር።
  • በእዚያው የክረምት ወቅት የክረምት ወቅትም 4 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የሚመራ የሚኒስትሮች ኮሚቴ ተቋቋመ።
  • ለእዚሁ ለሐምሌ 22 ቀን 2011 ዓም የዛፍ ተከላ ዘመቻ በኦሮሚያ 126 ሚሊዮን፣ በአማራ 108 ሚሊዮን፣ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል 48 ሚሊዮን፣ በትግራይ ዘጠኝ ሚሊዮን ችግኞች ሊተከሉ እቅድ ተይዞ፣ ቦታ ተመርጦ፣ ጉድጓድ ተቆፍሮ ተዘጋጀ።
  • የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በበኩሉ በሁሉም ወረዳዎች 3 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል የሚያስችለው ዝግጅት አደረገ።
  • "የአራዳ ልጅ ዛፍ ይተክላል" በሚል በትዊተር ላይ የተጀመረ ዘመቻ ተቀጣጠለ። የዚህ ዘመቻ አስተተባሪዎች "ዛፍ መትከል ጤናን መገብየት ነው" በሚል በተለያዩ የአዲስ አበባ አካባቢዎች ዛፍ ለመትከል ጥሪ አቀረቡ።
  • ሐምሌ 22 ቀን በአንድ ጀንበር 200 ሚሊየን ችግኝ ለመትከል ለተያዘው እቅድ 54 ሚሊየን ብር መመደቡ ተግለጸ የሚያስተባብረው ብሔራዊ የቴክኒክ ኮሚቴ ስራውን ማቀላጠፍ ጀመረ።
  • ከተመሰረተ ከ30 ዓመታት በላይ የሆነውና የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዎርጊስ መስራች የሆኑበት የኢትዮጵያ የአካባቢና ልማት ማኅበር የረጅም ጊዜ ህልሙ የሆነው ስራ መጀመሩ አስደሰተው ለተግባራዊነቱም ከግንባር ቀደምቶቹ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀሳብ ደጋፊ ሆነ።
  • በወቅቱ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በአፈር አጠባበቅ ላይ እየሠሩ የነበሩት አቶ መሀመድ እንድሪያስ ስለ የኢትዮጵያ የደን ሽፋን ማሽቆልቆል በወቅቱ ለቢቢሲ ሲያብራሩ በ1990ዎቹ አካባቢ የአገሪቱ የደን ሽፋን መጠን 15 ሚሊዮን አንድ መቶ አስራ አራት ሔክታር ነበር የሚሉት መምህሩ፤ በ2000 ላይ 13 ሚሊዮን ሰባት መቶ አምስት አካባቢ መሆኑን በመጥቀስ፤ በ2010 ላይ አስራ ሁለት ሚሊዮን ሁለት መቶ ዘጠና ስድስት፤ በ2018 ላይ ደግሞ አስራ ሁለት ሚሊዮን 147 ሔክታር አካባቢ ሽፋን መኖሩ ጠቅሰዋል።

የሚተከሉት ችግኞች ቁጥር እንዴት ታወቁ?

በሐምሌ 22፣2011 ዓም በአንድ ጀንበር 200 ሚልዮን ችግኝ ለመትከል የታቀደው ዕቅድ 300 ሚልዮን ችግኝ በመትከል የህንድን በሦስት እጥፍ የበለጠ ሥራ ተሰርቷል። ጥያቄው ቁጥሩ ትክክል ነው? እንዴት ተቆጠረ የሚለው ጥያቄ ነው። የችግኞቹ አቆጣጠር በተመለከተ 
  • የችግኝ ቆጠራውን በተመለከተ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጅ ሚኒስቴር ኃላፊነት ሲሆን በሥሩም አንድ ቡድን ተቋቁሟል። ቡድኑ የችግኝ ተከላዎችን አቆጣጠራቸውንና ምዝገባቸውን የሚከታተል ነው።
  • በሚኒስትር መስሪያቤቱ የበለጸገ ሶፍትዌር የተተከሉትን ችግኞች በመቁጠር ሂደት ወሳኝ ስራ እንደተሰራ በአንድ ወቅት መስርያቤቱ በሰጠው ማብራርያ ላይ ገልጿል።
  • ሶፍት ዌሩ በዛፍ መትከያ ቦታዎች ላይ የተከላውን ሂደት ለመቆጣጠር የተመደቡ ሰዎች ስልክ ላይ ብቻ የሚሠራ ሲሆን በአካል በመገኘት የቆጠሩትን ችግኝ ብዛት የሚያስተላልፉበት ሥርዓት አለው።
  • በዚህም መሠረት በተመደቡበት ቦታ ላይ ምን ያህል ችግኞች እንደተተከሉ ቁጥሩን ሲያስገቡ ሶፍት ዌሩ በተለያዩ ቦታዎች የሚደርሱትን አሃዞች በማጠቃለል እየደመረ ውጤቱን ይሰጣል። በመጨረሻ ላይም በአጠቃላይ በመላዋ ሃገሪቱ የተተከሉትን ችግኞች ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ እንደሚያሳውቅም ቢቢሲ አማርኛ ከአራት ዓመታት በፊት ሰፊ ዘገባ ሰርቶበታል።
  • እዚህ ላይ የሚነሳው ጥያቄ ከተተከሉ በኋላ ምን ያህሉ እንክብካቤ እየተደረገ ነው? ለመትከል የተቋቋመው ግብረኃይል ያህል ለመንከባከብም ህብረተሰቡ እራሱ ሊያቋቁመው የሚገባ ግብረኃይል መኖር አይገባውም ወይ? የሚለው ጥያቄ አሁንም አለ።ከተተክሉት ምን ያህሉ እየጸደቁና የክረምት ዝናብ እስኪመጣ ለምልመው የመቆየት አቅም አዳበሩ? የሚለው በተመለከተ ተአማኒ ጥናት ተደርጎ መቅረብ ያለበት ነው።
ዘንድሮ ለመትከል የታሰበው ምን ያህል ነው?

ሁለተኛው የደን ልማት  ምዕራፍ ትናንት በአፋር ሲከፈት
  • የመጀመርያው የደን ልማት ምዕራፍ ከሐምሌ 22፣2011 ዓም እስከ ዘንድሮ ያለው ሲሆን፣ትናንት ሰኔ 1፣2015 ዓም በአፋር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣የክልል ፕሬዝዳንቶች እና የፈረንሳይ፣ጣልያንና ቻይናን ጨምሮ በርካታ በአዲስ አበባ ተቀማጭ የሆኑ ዲፕሎማቶች በተገኙበት የተጀመረው ሁለተኛው ምዕራፍ የደን ልማት (ችግኝ ተከላ) መርሐግብር አራት ዓመታት የሚወስድ ሲሆን በእነኝህ ዓመታት ውስጥ ደግሞ 25 ቢልዮን ችግኞች ለመትከል ስራ ተጀምሯል።
  • በመጀመርያው ምዕራፍም እንዲሁ ከ25 ቢልዮን በላይ ችግኞች መተከላቸው ይታወቃል።
  • በእዚሁ በሁለተኛው ዙር  በሁለተኛው ምዕራፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር 60 በመቶ የጥምር ደን እርሻ ችግኞች፣ 35 በመቶ ደግሞ የደን ችግኞች ሲሆኑ 5 በመቶ ለከተማ ውበት የሚውሉ ችግኞች መሆናቸውን በማስጀመርያ መርሐግብሩ ላይ ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አብራርተዋል።
ለማጠቃልል ይህ የደን ልማት ስራ ለኢትዮጵያ የህልውናዋ ወሳኝ እና ቁልፍ ከሆኑት ጉዳዮች ውስጥ ነው።የእዚህ ዓይነቱ ስራ ደግሞ የፖለቲካ እና ፖሊሲ አውጪው አካል የቁርጠኝነት ልክ በሚፈለገው ደረጃ ካልሆነ ተግባራዊ ማድረግ አይቻልም። ለእዚህ ደግሞ ሀሳቡን ከማመንጨት ጀምሮ በተከታታይ ለተግባራዊነቱ የፖለቲካ አመራር ቁርጠኛነት እንዲኖር የጠቅላይ ሚኒስትሩ ትኩረት መስጠት ወሳኝ ለመሆኑ ማንም ሊረዳው የሚገባ ነው። የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አንዳንድ አክቲቪስቶች ሳይቀሩ የተከሉትን የዛፍ ቁጥር እየቆጠረ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሽልማት ሲሰጥ ኢትዮጵያ ለምትሰራው ስራም ሆነ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መስጠት የሚገባውን ያህል እውቅና አለመስጠቱ ብቻ ሳይሆን የዜና ሽፋኖችም ሆኑ በዛፍ የመትከል ስነስርዓት ላይ ለምሳሌ የተባበሩት መንግስታት የአካባቢ ጥበቃ ቢሮ ወይንም ዋና ጸሐፊው ተገኝተው ኢትዮጵያን ማበረታታት ግዴታቸው ነበር። ምክንያቱም ኢትዮጵያ የምትተክለው ለእራሱ መተንፈሻ ብቻ ሳይሆን ለዓለም የአካባቢ ጥበቃ ከፍተኛ አስተዋጾ የሚያደርግ ነው። ለሁሉም ግን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ዳግማዊ ምንሊክ ኢትዮጵያን በደን ለማልበስ የጀመሩትን በጎ ጅምር በማስቀጠላቸው ሀገራዊም፣ዓለም አቀፋዊ ሽልማት ይገባቸዋል።
=============////==========

ማስታወሻ - 

ለእዚህ ጥንቅር ጉዳያችን ቢቢሲ አማርኛ፣ኢዜአ እና ፋብኮ ዘገባዎች ለመዳሰስ ሞክራለች 


Wednesday, June 7, 2023

''ያንን ጉድጓድ ማን ማሰው? ያ! ሰው። ማን ገባበት? የማሰው።'' ኢትዮጵያዊነትን ቀና ለማድረግ የተኛህ ንቃ! የጀዋር የሌሊት ወፍ ፖለቲካና የኦነግ ሸኔ ኦሮምያን የመገንጠል ቅዠት።


በጅማ ጎዳናዎች ላይ ሰዎች ''አዕምሮውን ስቷል'' የሚሉት እርሱ ግን የራሱ ፍልስፍና እና አስቸጋሪ የህይወት ውጣ ውረድ ላይ ያለፈ ሰው ነው በቀይ ሽብር ጊዜ ለተፈጸመው ግድያ እና እርሱን ተከትሎ ለመጣው እልቂት በእየመንገዱ እየዞረ የሚናገር ሰው ነበር።ታሪኩ እውነተኛ ታሪክ ነው።ስሙ ለጊዜው ይቆይና ሸገር ኤፍኤም ሰሞኑን በስንክሳር ሳምንታዊ መርሐግብሩ ላይ የግለሰቡን እውነተኛ ታሪክ አስደምጦናል።ግለሰቡ በጅማ መንገዶች ላይ እየዞረ ይለፍፍ ከነበረው ውስጥ ''ያንን ጉድጓድ ማን ማሰው? ያ! ሰው። ማን ገባበት? የማሰው።'' የሚለው እዝነ ልቦናዬን የሳበው አባባል ነው።

ኢትዮጵያዊነትን ቀና ለማድረግ የተኛህ ንቃ!

ኢትዮጵያ ላይ ጉድጓድ የማሱባት ሁሉም እራሳቸው ገብተውበታል። ይህ ግን ዝም ብሎ በተዓምር ብቻ የመጣ አይደለም። ለኢትዮጵያ መስዋዕትነት የከፈሉ ለማንነቷ የቆሙ የእውነት ዜጎች ስላሏት ነው።ባለፉት አርባ ዓመታት ውስጥ ብቻ በትንሹ ቆንጽለን ለማስታወስ ብንሞክር ከኡጋዴን በረሃ እስከ የኤርትራ በርሃዎች፣በምጽዋና አሰብ በር ላይ በጨበጣ ውግያ እየተሞሻለቁ ለኢትዮጵያ አንድነት ህይወታቸውን ከሰዉት እስከ የቅርቡ ኢትዮጵያን ለማፍረስ መከላከያ ሰራዊቷ ላይ የተከፈተው የህልውና ዘመቻ ድረስ ሺዎች ለኢትዮጵያ ሞተዋል። ይህች ሀገር በቀልድ የተሰራች አይደለችም።በፌዝ እና በቧልትም የሚዘባበቱባት ምድር አይደለችም። የደም ዋጋ ነች። ሰንደቅ ዓላማዋን  ለመስቀል የሚነዝራቸው የባንዳ አስተሳሰብ ስንኩልነት ያጠቃቸው ሊያናንቋት እንደሚፈልጉት አይደለችም።የማንም ሀገር ህልውና በመሽሞንሞንና በዋዛ ተከብሮ አልኖረም። ኢትዮጵያዊነትም ኢትዮጵያዊነት የሚጠሉትን በማሽኮርመም አይከበርም።

የኢትዮጵያ ህዝብ ኢትዮጵያዊነትን በከፍተኛ ግለት እና ማንነት እንዳያስከብር እንቅፋት የሆነው አንዱ ምክንያት ኢትዮጵያውያንን በጎሳ የመከፋፈል ሴራ ነው። ኢትዮጵያዊነቱን ለማስከበር የተነሳ የእገሌ ጎሳ ፍላጎት ልታሟላ ነው እየተባለ ሲሸማቀቅ ኖሯል።ይህ ደግሞ እንደ ሀገር ከመጉዳት አልፎ ኢትዮጵያን ወደ አደገኛ ቁልቁለት እየመራት ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ ከደቡብ እስከ ሰሜን፣ከምስራቅ እስከ ምዕራብ በአንድነት ቆሞ ኢትዮጵያዊነቱን አጽንቶ እንዳይይዝ ምሑራን የተባሉቱ ሳይቀር በኦሮሞ፣አማራ፣ትግራይ ወዘተ የብሔር አስተሳሰብ ውስጥ ተሰንገው የእየብሔራቸው ተንታኞች ሆነው መክነው ቀርተዋል። ኢትዮጵያዊነት በእዚህ ሁሉ መሀል እየተጎሳቆለ እና እየደበዘዘ የመጣ እንዲመስል ሆኗል።ኢትዮጵያዊነት በሰሜን ቢበርድ ደቡብ ያቀጣጥለዋል፣ ምዕራብ ቢያቀዘቅዘው ምስራቅ ይዞት ይነሳል።በሁሉም ዘንድ ግን ኢትዮጵያዊነት እንደ የተዳፈነ ፍም በድንገት እንደቋያ እየተቀጣጠለ ይንቦገቦጋል።ለእዚህ ነው ዘላቂው ኢትዮጵያዊነት እንጂ እንደኩፍኝ የሚጠፋ ነገር ግን ሀገርን አደጋ ላይ የሚጥል የጎሳ ፖለቲካን ጭዳ ማድረጉ አይቀርም። ለእዚህ ግን ከምሑር እስከ ጨዋ፣ከሊቅ እስከ ደቂቅ ኢትዮጵያዊነትን ማቀንቀን እንደገና ማቀጣጠል የሁሉም ኢትዮጵያዊ ግዴታ ነው። እያንዳንዱ ጥቃቅን እንቅስቃሴ ኢትዮጵያዊነትን ለመነቅነቅ የሚደረጉ ማናቸውም እንቅስቃሴዎች፣ጽሑፎች እና ሙከራዎች ሁሉ ላይ የማያዳግም አጸፋዊ ምት ለመስጠት ከሀገር ውስጥ እስከ ባሕር ማዶ ያሉ ኢትዮጵያውያን ከምር ካልተነሳን ኢትዮጵያን ለባንዳና ዱርዬ ሸኔ እና መሰሎቹ አስረክበን የታሪክ ተጠያቂ የመሆን ግዙፍ አደጋ ላይ ነን። 

የጀዋር የሌሊት ወፍ ፖለቲካና የኦነግ ሸኔ ኦሮምያን የመገንጠል ቅዠት።

ኢትዮጵያ ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ የገባችበት የለውጥ ሒደት ውስጥ ያለፈችባቸው ውጣ ውረዶች ከውጭ የኢትዮጵያ ጠላቶች ብቻ የተፈበረኩ አይደሉም። ኢትዮጵያን ገልብጦ ለመስራት እና የነበረ ታሪኳን አፍርሶ የባዕዳን ተገዢ ለማድረግ የሚሮጡ የራሳችን ወገኖች የጥፋት ድግስ ውጤት ነው። የለውጦቹ ሒደቶች ኢትዮጵያዊነትን እያኮሰሰ መከፋፈል እና የሀሰት ትርክቶችን እያመነዠከ የሚኖር የጀዋር እና የኦነግ ሸኔ ኦሮምያን የመገንጠል ቅዠት ውስጥ በገቡ ሩቅ አላሚ ቅርብ አዳሪዎች ሀገር ታውኳል። የእነኝህ የጥፋት ኃይሎች ሴል በመንግስታዊ መዋቅር ውስጥ ገብቶ ፖሊሲ ለማጣመም ከመሞከር የጸጥታ ኃይሉ በቀጥተኛ ጭፍጨፋ ውስጥ እንዲገባ ሙከራ እስከማድረግ ደርሷል።

የጀዋር ፖለቲካ የሚለው በግለሰብ ስም ተጠቀሰ እንጂ ሃሳቡ በእርሱ አስተሳሰብ ውስጥ ተግተልትለው የሚጓዙ ሁሉ የሚመለከት ነው። ጀዋር ስለ ኦሮምያ ክልል ይጨነቃል ብሎ የሚያስብ ወይንም አጀንዳው የኦሮምያ ክልል የብሔርተኝነት ፖለቲካ የሚመስለው ካለ ተሳስቷል። የጀዋር የፖለቲካ ማኔፌስቶ የሚጀምረውም የሚያልቀውም ሆነ ሙሉ መገለጫው ከእዚህ በፊት '' የሜጫ ንግግሩ'' ተብሎ በሚታወቀው የአሜሪካን ሀገር ንግግሩ የተቋጨ ነው። ኦሮምያን የፈለጋት በእዚሁ ንግግሩ ላይ እንደገለጸው የጽንፍ አክራሪ እስልምና ለማራመድ ከሌላው ክልል በተሻለ የእምነቱ ተከታዮች ይገኛሉ በሚል እና ክልሉ የተሻለ የተፈጥሮ ሀብት ባለቤት ነው በሚል የሚማልሉ አንዳንድ የመካከለኛ ምስራቅ ሀገሮችን የቆየ አጀንዳ ማስፈጸም ብቻ እና ብቻ ዓላም ያደረገ ነው። 

ጀዋር የኦሮምያ ክልል መተራመስ፣የአማራ ክልል ሰላም ማጣት እና የኢትዮጳ ማዕከላዊ መንግስት አለመረጋጋትን እና የኦሮምያ ክልል የመገንጠል ዓላማን ማራገብ እንደ ስልታዊ ማስፈጸምያ እንጂ አንድም የኦሮምያ ብሔርተኝነት መቆርቆር ፍላጎት የለውም። ጀዋር የሌሊት ወፍ ፖለቲካ በለውጡ መሃል ላይ አራምዷል። የሌሊት ወፍ አንድ የቆየ ታሪክ ይነገርላታል። ይሄውም በአንድ ወቅት የሰማይ አዕዋፋት እና የምድር አራዊት ተጣሉ ይባላል።የምድር አራዊት የሰማይ አዕዋፋት መሬት ላይ አያርፏትም፣ውሃም አይጠጡም ምግብም አይበሉም ብለው አመጹ።የሰማይ አዕዋፋት ደግሞ የምድር አራዊት ዝናብ እንዳያገኙ፣ፀሐይ እንዳይሞቁ እንደደመና አጥልተን እንጎዳቸዋለን ብለው ተነሱ።በእዚህ መሃል ታድያ ከምድር አጥቢ እንስሳትም ሆነ ከሰማይ አዕዋፋት የምትመደበው የሌሊት ወፍ የምድር አራዊት እና የሰማይ አዕዋፋት ላስታርቅ ብላ ተነሳች። ሆኖም ግን ለማስታረቅ ተነስታ ሁለቱን ለማጣላት ላይና ታች ሮጠች። ሆኖም ሁለቱም የሰማይ አዕዋፋት እና የምድር አራዊት አንዳቸው ካለአንዳቸው እንደማይኖሩ አውቀው ታረቁ።ሲታረቁ የሌሊት ወፍ ለሁለቱም ታቀብል የነበረው የማጣያ ነገሯ ተገለጠ። ጀዋር በአንድ ወቅት የኦሮምያ አንድነት ምክርቤት ይህንን ሰነድ ፈርሙ፣ ያንን ቅደዱ እያለ መኖርያው ቤት ድረስ እየጠራ ሲያፈራርም ነበር። በሌላ ጊዜ ደግሞ ኦነግ ሸኔን ከኦሮምያ ክልል ጋር ለማስታረቅ ወለጋ ወረድኩ ሲልም ተደምጧል። ሆኖም ግን በሂደት ኦነግ ሸኔም ሆነ የኦሮምያ ክልል ብልጽግና አላመኑትም።የእርሱ አጀንዳ የኦሮምያ ክልል ጉዳይ አይደለም። አጀንዳው ሌላ ነው። ይህ ማለት ግን ከብልጽግናም ሆነ ከኦነግ ሸኔ ከግለሰቡ እና ተከታዮቹ ጋር አይሞዳሞዱም ማለት አይደለም። የሁሉም ጠላት ኢትዮጵያዊነት እና የኢትዮጵያ ያለፈ ታሪክ ጠልነት አገናኛቸው እንጂ አሁንም የጀዋር ግብና መድረሻ አክራሪ መንግስት በኢትዮጵያ ማቆም ነው።ይህንን ደግሞ በግልጽ ወደፊት የበለጠ ፍንትው እያለ የሚመጣ ሃቅ ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ የኦነግ ሸኔ እና የጀዋር መንገድ አንድ ሌላ የጋራ ነጥብ ላይም ይገናኛል።ይሄውም የኦሮምያ ክልልን በረጅም ጊዜ መገንጠል እና የራሷ መንግስት ማድረግ ለእዚህም ከወዲሁ ፖለቲካዊ፣ማኅበራዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ አደረጃጀት ማጎልበት በሚለው ጉዳይ ላይ ነው። የጀዋር እና የቡድኑ ፍላጎት በኦሮምያ መገንጠል የአክራሪ መንግስት በኦሮምያ ይመሰረታል በሂደት የምስራቅ አፍሪካን በአክራሪ መንግስት ተጽዕኖ ውስጥ ማስገባት እና መስፋፋት ነው። ይህንን ስልት ደግሞ አንዳንድ የመካከለኛ ምስራቅ ሀገሮች ለረጅም ጊዚ ሲያልሙት የነበረው እና የአፈጻጸሙ ሂደት ሲያጠኑት የነበረ ነው። ኦሮምያን የመገንጠል ፍላጎት የለም የሚለው የአንድ ወቅት የጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ የፓርላማ ንግግርን እዚህ ላይ ሙሉ በሙሉ ውድቅ ማድረግ ቀዳሚ ጉዳይ ነው። 

የኦሮምያ ክልልል ህዝብም ከወዲሁ ሊያውቀው የሚገባው ይህ ሁሉ በክልሉ ያለው ግርግር መድረሻ ክልሉን መገንጠል ነው። በክልሉ የሚገኙ የሌላ ክልል ተወላጆች ማባረር፣የንግድ ተቋሞቻቸውን ለምሳሌ በሻሸመኔ የተፈጸመው ዓይነት የማውደም ስራ፣የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንን እና መስጊዶችን ማውደም፣የትርክት ታሪክ መፍጠር እና ለማሳመን መሞከር፣የክልሉ ሰንደቅ ዓላማ እና መዝሙር ከብሔራዊ መዝሙር አልቆ ለማሳየት የሚደረገው መጋጋጥ ሁሉ ግቡ ኦሮምያን ለመገንጠል ነው። መገንጠሉን ብሔርተኞቹ ከብሔር አንጻር ሲያዩት ጀዋር እና ቡድኑ ግን ሁሉንም በመጨረሻ አስወግዶ የአክራሪ ጽንፈኛ መንግስት ከተቻለ በኢትዮጵያ ደረጃ ካልተቻለ በኦሮምያ ክልል ደረጃ መመስረት ነው። በእዚህ ፍላጎት ውስጥ የጊዜ ጉዳይ እንጂ የኦሮምያ ክልል የአሁኑ ግፈኛ እና ሙሰኛ ቡድን ጨምሮ የብልጽግና መንግስትም እንዲዳከም እነኝሁ ቡድኖች አብረው ይሰራሉ። የኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግስት መዳከም ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያዊነት ያቀነቅናሉ የሚባሉ የአማራ፣አፋር፣ሱማሌና ጌድዮ ጭምር ሰላም እንዳይኖራቸው እና እንዲታወኩ የኢትዮጵያዊነት አጀንዳ እንዲታወክ ሁሉም ቡድኖች አብረው ይሰራሉ።

መፍትሔዎቹ 

ኢትዮጵያውያን ዋና ግባችን ሊሆን የሚገባው ዛሬም ኢትዮጵያዊነት እና ኢትዮጵያዊነት ብቻ መሆን አለበት። የጀዋር የሌሊት ወፍ ፖለቲካም ሆነ የኦነግ ሸኔ ዓላማዎች ኢትዮጵያዊነትን ማደብዘዝ ነው።ይህንን መሰሪ አካሄድ አለማወቅ ትልቅ ጥፋት ነው። ኢትዮጵያዊነትን አጉልቶ ለማስኬድ ደግሞ አንዳንዶች እነርሱ ስልጣን ላይ ሲመጡ ብቻ የሚሳካ አድርገው ይህንኑ ስልጣን ለመያዝ በሚደረግ ፍትጊያ ውስጥ ብቻ ይጠመዳሉ። የፖለቲካ ስልጣን ማለት ቤተመንግስት መግባት ብቻ አይደለም። በየትኛውም መንገድ ተጽኖ ፈጥሮ ዓላማን ማስፈጸም ነው።ኢትዮጵያዊነትን የማይቀበል እና የማያጎላ መንግስት እንዳይኖረን የግድ ቤተመንግስት መግባት እና ፖሊሲ አውጪ መሆን ብቻ አሁን ባለንበት የ21ኛው ክ/ዘመን ብቸኛው መንገድ አይደለም። የማስፈጸም አቅምን መገንባት እና አሁን ያለውን መንግስት ፖሊሲ አስገድዶም ሆነ አስረድቶ ኢትዮጵያዊነትን ጠብቆ እንዲሄድ ማድረግ ዓይነተኛው መንገድ ነው። የሚወጣውን ጸረ ኢትዮጵያዊ ፖሊሲ መቃወም እና ኢትዮጵያዊ አጀንዳዎች በትክክል እንዲተገበሩ የጎሳ ፖለቲካ እንዲሽቀነጠር ተጽዕኖ የመፍጠር መንገድ በራሱ የፖለቲካ ስልጣን ነው። ይህንንም ከሰላማዊ ትግል እስከ የምሁራን ተከታታይ ሞጋች ጽሑፎች እና ንግግሮች፣ከትምሕርት ፖሊሲው አስጣጥ እስከ የመገናኛ ብዙኃን የእየዕለቱ መልዕክቶች ሁሉ መዳሰስ እና በኢትዮጵያዊነት ቅኝት እንዲቃኙና ትውልድ እንዲያፈሩ ማድረግ ሁሉ የተጽዕኖ መፍጠርያ እና መተግበርያ መንገዶች ናቸው። ኢትዮጵያዊነት አገንግኖ እንዲወጣ እና የጎሳ ፖለቲካን አሽቀንጥሮ ሁሉም በህብረ ብሔራዊ ስሜት ከጎሳ አደረጃጀት የጸዳ እውነተኛ የፌድራሊዝም ስርዓት በኢትዮጵያ ለማምጣት የሞት ሽረት ትግል ያስፈልጋል። ይህ ደግሞ አክራሪ የሌሊት ወፍ ፖለቲከኛን ሴል ከማምከን እስከ የጎሳ ፖለቲካ ሙሰኞች ድረስ ያለውን ትብተባ መበጣጠስ ይጠይቃል።ዛሬም ለአፍታ መዘናጋት አይገባም። ኢትዮጵያዊነትን ቀና ለማድረግ የተኛህ ንቃ! ይህ ግዙፍ ኃይል የተዳፈነ እረመጥ ነው።ሲነሳ ማንም አይስቆመውም።ጀዋርም ሆነ ኦነግ ሸኔ፣የጎሳ ፖለቲካ የተከለው ህወሓትም ሆነ የጽንፍ ኃይሎች ሁሉ በኢትዮጵያ ላይ ጉድጓድ ምሰዋል።ነገር ግን በማሱት ጉድጓድ ገቡ።ነገሩ እንደ የጅማው ምስኪን ''ያንን ጉድጓድ ማን ማሰው? ያ! ሰው። ማን ገባበት? የማሰው።'' እንዳለው ነው። አሁን ኢትዮጵያዊነትን ቀና እናድርገው።የጎጥ ፖለቲካን እንቅበረው። በህብረት ከተነሳን እንችላለን።ነገር ግን በየጎጡ እየተቧደንን ለኢትዮጵያ ጠላቶች ሀገራችንን የማስረከብ አደጋ ላይ ነን።
================//////=============
ቀና በል!
በድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሣሁን




ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...