ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Sunday, February 26, 2023

ሦስት ሳምንት ያልሞላት አራስ እናትን ቤት በግሪደር አፍርሶ በከተማ ዙርያ ከተማ ልመሰርት ነው ያለው የኦሮምያ ክልል ፕሮጀክት፣እውን የከተማ ፕሮጀክት መስፈርት ያሟላል?

የኦሮምያ ክልል በሸገር ፕሮጀክት ስም የአዲስ አበባ ዙርያ ነዋሪዎችን ቤት ሲያፈርስ
ፎቶ ቢቢሲ አማርኛ።

===========
  • ስሜት ፕሮጀክት አይሆንም።ቂምም ልማት አይሆንም። ምኞትም ውጤት ሆኖ አያውቅም።
  • በዓለም ላይ በዋና ከተማ ዙርያ ከተማ ልገነባ ነው የሚል ፈላስፋ እስካሁን አልተሰማም።የእዚህ ዓይነት ፕሮጀክት በመሰረታዊ የከተማነት መርሕ (Basic Principle of Urbanization) ላይም አይታወቅም።
  • አዲስ አበባን የፈጠራት የነገስታቱ ነጋሪት እና አዋጅ ሳይሆን የንግድ እና እንዱስትሪ መስፋፋት ነው።

በእዚህ ጽሁፍ ስር የሚከተሉትን ርዕሶች ያገኛሉ 
  • በዋና ከተማ ዙርያ ከዋና ከተማ የተነጠለ ሌላ ከተማ?
  • የሸዋ ኦሮሞን ለመግፋት ውስጣዊ ዓላማ የያዘው የሸገር የከተማ ፕሮጀክት፣
  • የሸዋ ኦሮምኛ ተናጋሪዎች የሸገርን ፕሮጀክት በሶስት ምክንያቶች አይደግፉትም።
  • በሸገር ፕሮጀክት ስም መሬታቸውን የተነጠቁት አሳዛኝ ዜጎች ቢቢሲ እንደዘገበው ታሪክ
===========
=========
ጉዳያችን ልዩ
=========


በዋና ከተማ ዙርያ ከዋና ከተማ የተነጠለ ሌላ ከተማ?

በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ስድስት ከተሞችን በማጣመር 12 ክፍለ ከተሞች እና 36 የወረዳ አስተዳደሮችን በማዋቀር  ሸገር ከተማ እገነባለሁ የሚለው የኦሮምያ ክልል ፕሮጀክት በርካታ ጥያቄዎች በውስጡ ይዟል። ከተማ ጥሩ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ ለማልማት እፈልጋለሁ ያለ የማንንም አልሚ እንቅፋት መሆን አይፈልግም።ስለሆነም የሸገር ከተማ ለማልማት እፈልጋለሁ ያለው የኦሮምያ ክልልን በማልማቱ የሚቃወመው የለም። ምንም ይሁን ምን ዛሬ የለማው ነገ ዞሮ ዞሮ የኢትዮጵያ ሃብት ስለሆነ ማልማት በራሱ ችግር ሊሆን አይችልም። ችግር የሚሆነው የልማቱ ግብ ነገ ህዝብ የሚያስታርቅ ነው የሚያጣላ? የሚለው ነው።ከተማነት በባህሪው ህዝብ የሚያስታርቅ ነው።ከተማነት በቋንቋ እና በጎሳ መታጠር እና ማጠር አይደለም።ከተማነት ከሃገር አልፎ ዓለም አቀፋዊ አስተሳሰቦች የሚንሸራሸሩበት አንዱ ስለሁሉም፣ሁሉም ስለአንዱ የሚያስብበት ድንበር የለሽ የአኗኗር ዘይቤ የተላበሰ የቅርቡንም ሆነ የሩቁን እየተቀበለ ከአካባቢው ጋር አስማምቶ የሚያኖር ቦታ ነው።

በዓለም ላይ ሀገሮች በዕቅድ ከተማ ይገነባሉ።በአፍሪካም ይህንን የሚያደርጉ አሉ።ለምሳሌ በናይጄርያ የሌጎስን ከተማ በአቡጃ አዲስ ከተማ የመገንባት ሥራ ሊጠቀስ ይችላል። አቡጃ ግን በሌጎስ ከተማ ዙርያ በከተማ ዙርያ ከተማ ተደርጋ አልተገነባችም። በአቡጃ እና ሌጎስ ከተማ መሃል የ715 ኪሜ እርቀት አለ።በዓለም ላይ በዋና ከተማ ዙርያ ከተማ ልገነባ ነው የሚል ፈላስፋ እስካሁን አልተሰማም።የእዚህ ዓይነት ፕሮጀክት በመሰረታዊ የከተማነት መርሕ (Basic Principle of Urbanization) ላይም የለም አይታወቅም። ከተሞች በህዝብ ብዛት አሰፋፈር ይመሰረታሉ።ለህዝቡ መስፈር ምክንያት ከሚሆኑት ምክንያቶች ውስጥ አንዱ ምጣኔ ሃብታዊ ምክንያት ነው።ምጣኔ ሃብታዊ ምክንያቶቹ ደግሞ ንግድ እና ኢንዱስትሪ ናቸው። በንግድ እና ኢንዱስትሪ እንቅስቃሴ የኢትዮጵያን ንግድ እስከ ግማሽ ድረስ የሚንቀሳቀስባት የምትባለው አዲስ አበባ ዙርይ የሚመሰረተው ከተማ ከአዲስ አበባ ጋር ምን ዓይነት የንግድ ግንኙነት ይኖረዋል? ከአምስት ሚልዮን በላይ የሆነ ህዝብ የያዘ ከተማ የከበበ ሌላ ከተማ ምን ዓይነት ነው? ከተሞች ሲሰፉ የሚቀመጥላቸው ሕግ እና አሳሪ ማኅበራዊ ግንኙነት ይዘው አይደለም። በራሳቸው መስተጋብራዊ፣ታሪካዊ እና ትውልዳዊ የባሕል ውርርስ እንዲሁ በነጻነት የሚያድጉ እና የሚሰፉ ናቸው።ይህ ነው የከተሞች ባህሪ። የኦሮምያ ክልል ከአምስት ሚልዮን በላይ ሕዝብ የከበበ በዋና ከተማ ላይ ሌላ ዋና ከተማ የመፍጠር ፍልስፍና ከመሰረታዊ የከተሞች እድገት አንጻርም የተቃረነ ነው። እየተፈለገ ያለው የጎሳ ፖለቲካ የሚያቀነቅነው ክልል ጎሳ አልባ የሆኑ ግን ኢትዮጵያዊነታቸውን የሚያቀነቅኑ የከተሞችን የፍልስፍና ጥግ በጎሳዊ አስተሳሰብ ለመቅረጽ የሚሞክር ፖለቲካዊ ግብ ያለው ነው። ማኅበራዊ ሳይንስ በፖለቲከኞች ቢሮ ውስጥ በሚደረግ ስብሰባ በቀላሉ የሚዘወር የሚመስላቸው የኦሮምያ ክልል አማካሪ ምሁራን በዘርፉ ያላቸው ደካማ ዕውቀት ከማስደንገጥ አልፎ ጤንነታቸው በራሱ አሳሳቢ አይደለም ማለት አይቻልም።

የሸዋ ኦሮሞን ለመግፋት ውስጣዊ ዓላማ የያዘው የሸገር የከተማ ፕሮጀክት


የሸዋ ኦሮምኛ ተናጋሪዎች የሸገርን ፕሮጀክት በሶስት ምክንያቶች አይደግፉትም።

የኦሮምያ ክልል የሸገር የከተማ ፕሮጀክት በሸዋ ኦሮሞ ላይ የተጫነ የግድ ፕሮጀክት ነው።ፕሮጀክቱን ከአባገዳዎች፣እስከ የአዲስ አበባ ዙርያ ነዋሪ የኦሮምያ ተወላጆች፣ከገበሬ እስከ ሰራተኛ ተቃውሞታል። ተቃውሟቸውንም በሺህ የሚቆጠሩ የሸዋ ኦሮሞዎች ሰልፍ በመውጣት ተቃውመውታል። ይህንንም ኢሳትን ጨምሮ የሃገር ውስጥ እና የውጭ ዜና ዘጋቢዎች ዘግበውታል።ይህም ሆኖ ግን ዛሬ አቶ ሽመልስ ፕሮጀክቱ በሕዝብ ተቀባይ የሆነ ይመስል ዛሬ አባ ዱላ እና አብረዋቸው ያሉትን በዙርያቸው ሰብስበው ከተማው ተመሰረተ ብለዋል። የሸዋ ኦሮሞዎች የሸገርን ፕሮጀክት በሶስት ምክንያቶች አይደግፉትም።ይሄውም 

1ኛ/ የመሬታቸውን ዋጋ በፍጥነት ስላወረደው።

በአዲስ አበባ ዙርያ ያሉ ባለይዞታ የሸዋ ኦሮሞዎች የመሬታቸው ውድነት እና ተፈላጊነት አንዱ ምክንያት ከአዲስ አበባ ጋር ያላቸው ቁርኝት ነበር።አዲስ አበባ ጋር በመጠጋት በራሱ የመሬቱ ዋጋ ተፈላጊ ያደርገዋል።አዲስ አበባ እየሰፋ ሲሄድ የእነርሱም ቦታ መጠቃለሉ ስለማይቀር ቦታቸው አይደለም ለመሸጥ ለመከራየት ሳይቀር ዋጋው እየጨመረ ስለሚሄድ ለልጆቻቸው ሳይቀር ቅርስ ሆኖ ነበር የኖረው። የአቶ ሽመልስ 'አላዋቂ ሳሚ' ዓይነት ምክር ግን በዛሬዋ የሸገር ከተማ ምስረታ ብቻ የሸዋ ኦሮምኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን በአዲስ አበባ ዙርያ ያለው የመሬታቸው ተፈላጊነት ወርዶ ማደሩ ስለሚታወቅ ይህ ፕሮጀክት ሲሳይ ሳይሆን ችግር ሆኗል።

2ኛ/ ፕሮጀክቱ ከሸዋ ውጭ ያሉ ኦሮሞዎችን በአዲስ አበባ ዙርያ ለማስፈር ያለመ እና ሥራ የጀመረ በመሆኑ።

የሸገር ፕሮጀክት አንዱ የሸዋ ኦሮምኛ ተናጋሪዎችን ያስቆጣበት ምክንያት ከእዚህ በፊት በአቶ ለማ መገርሳ ተፈጽሟል የተባለው በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ከሸዋ ውጭ የሆኑ የኦሮሞ ማኅበረሰብ የማስፈር ሥራን በሸገር ፕሮጀክት ለመቀጠል በመታሰቡ እና ይህም በሚልዮን የሚቆጠሩ በኢትዮጵያዊነታቸው ጥብቅ ናቸው የሚባሉትን የሸዋ ኦሮምኛ ተናጋሪዎች በኦነግ ደጋፊ ከሸዋ ውጭ በሚመጡ የኦሮምኛ ተናጋሪዎች የመተካት ዓላም መያዙን ስለሚረዱ ነው። በእዚህም ሳብያ በአዲስ አበባ ዙርያ ያሉ በሺህ የሚቆጠሩ የሸዋ ኦሮምኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን ቀስ በቀስ ይዞታቸውን እየለቀቁ እንደሆነ የአደባባይ ምስጢር ነው።

3ኛ/ አዲስ አበባ ይፈጸም የነበረ ጉዳይ በመቶ ኪሎ ሜትሮች እርቀት እንዲጓዙ ስላደረገ።

በአዲስ አበባ ዙርያ የነበሩ ነዋሪዎች የመሰረታዊ አገልግሎት የመንግስት የቢሮ አገልግሎት ያገኙ የነበረው በቅርባቸው ካለው የአዲስ አበባ አስተዳደር የነበረ ሲሆን አሁን እንደ ሰበታ፣ ቡራዩ፣ ለገጣፎ፣ ለገዳዲ፣ ሱልልታ ኤር ሞጆ የመሳሰሉት ከተሞች የአስተዳደር አገልግሎትም ሆነ ሌሎች ተዛማች አገልግሎቶችን ለማግኘት ቅርባቸው ወዳለው ወደ አዲስ አበባ እንዳይመጡ አዲሱ የሸገር ፕሮጀክት ስለሚያግዳቸው እጅግ እሩቅ ወደ ሆኑ አዋሳኝ የኦሮምያ ክልል ለመሄድ ይገደዳሉ። በእዚህም ነዋሪዎቹ በጎሳ ፖለቲካዊ የከተማ ምስረታ ፕሮጀክት ምን ያህል እንደተጎዱ የሚያውቁት እነርሱ ናቸው።

ለማጠቃለል የሸገር ፕሮጀክት በትክክል እንደ የኦሮምያ ክልል አገላለጽ ''የስማርት ከተማ'' እንመሰርታለን የሚለውን አባባል የክልሉን ሃብት ሙሉ በሙል ቅንጡ ከተማ መገንባት ላይ ለማዋል ካልታሰበ በቀር በነዳጅ ሃብታቸው የበለጸጉ ሃገሮችም ቢሆን በዋና ከተማ ዙርያ ሌላ ከተማ እንገነባለን የሚል ቅዠት ውስጥ አልገቡም። የኦሮምያ ክልል ይህ ፕሮጀክት ለከፍተኛ የሙስና እና የሃገር ሃብት መባከን ብቻ ውሎ ጥቂት ቅምጥል ባለስልጣናት ኪሳቸውን የሚያደልቡበት ፕሮጀክት ሆኖ ልክ የኦሮምያ የኢኮኖሚ አብዮት ሲባል እንደነበረው እና አሁን የት እንዳለ የማይታወቀው ፕሮጀክት ሁሉ መቀለጃ እንዳይሆን ያሰጋል። ኢትዮጵያ የበላው ሲሄድ የሚበላው ሲመጣ የሚኖርባት ሃገር መሆኗ ያሳዝናል።ይህ ጉዳይ ዐይን ባወጣ አምባገነንነት እና የጎሳ ፖለቲካ ተሸፍኖ የሃገር ሃብት እንዲሁ ሲባክን ማየት አሳዛኝ ነው።ፕሮጀክቱ ፖለቲካው ግርግር እና ከአዲስ አበባ ጋር መነታረክያ አጀንዳን በሸገር ከተማ ስም ተቋማዊ የኦሮምያ ክልል ዲፓርትመንት ከመክፈት ባለፈ እና የሸገር ከተሞች የተባሉትን ዋና ዋና መንገዶች በመቀባባት ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ከማዋል ባለፈ የሸገር ፕሮጀክት ትርፍ የሚሆነው የባለስልጣናቱ ኪስ መድለብ ብቻ እና ብቻ ነው። 

የመጨረሻው መጨረሻ ማሳረግያ ዓረፍተነገሬ ግን ሃገር ኢንዱስትሪ ሳትገነባ ቅምጥል ስማርት ከተማ ለመገንባት ስትጋጋጥ ማየት ምን ያህል አላዋቂነት ነው? ስማርት ከተማ ውስጥ በእንዱስትሪ ያላመረተ፣እርሻ ያላረሰ ዝም ብሎ ከተማ እየተደረደረለት ጥፍሩን እያጸዳ እንዲኖር ነው? እንዱስትሪ እና ንግድ ከተማን ይፈጥራል። አዲስ አበባን የፈጠራት የነገስታቱ ነጋሪት እና አዋጅ ሳይሆን የንግድ እና እንዱስትሪ መስፋፋት ነው።የኦሮምያ ሸገር ፕሮጀክት የፕሮጀክትነት ትንሹን መስፈርትም አያሟላም።ፕሮጀክት ሕዝብ ካልተውያየበት እና ካልተስማማበት በትሪልዮን የሚቆጠር ገንዘብ ቢፈስበት አይሳካም።ቢሳካም ዕድሜ የለውም። አዬ! አለማውቅ ደጉ።በምኞት ፈረስ አስጋልቦ እንደ አቶ ሽመልስ ጥቁር መነጸር አድርጎ በንግግር ማሳመር መጎማለል ሲያመጣ ይገርማል! 

ከእዚህ በታች በሸገር ፕሮጀክት ስም ሦስት ሳምንት ያልሞላት አራስ እናትን ቤት በግሪደር ከማፍረስ ጀምሮ በሌሎች ዜጎች ላይ የደረሰውን ግፍ ቢቢሲ አማርኛ የዘገበውን ሙሉ ዘገባ ይመልከቱ።

 

ከሰሞኑ ቤቷ የፈረሰባት የ20 ቀኗ አራስ እና የሸገር ከተማ ነዋሪዎች እሮሮ


ቢቢሲ አማርኛ
25 የካቲት 2023
==========
“የቤቱን ጣሪያ ከቤት ሳልወጣ በላዬ ላይ አፈረሱት። ቆርቆሮውን ቤት ውስጥ ሳለሁ ነው የሚነቅሉት። ዕቃ ለመሸከፍም ጊዜ የለም” ይህንን የተናገረችው ከሰሞኑ በሱልልታ አካባቢ መኖሪያ ቤቷ የፈረሰባት እስከዳር ናት።

ለደኅንነቷ ሲባል ትክክለኛ ስሟ የማይገለጸው እስከዳር ከተገላገለች 20 ቀኗ ነው። የአራስ ጀርባዋም አልጠናም።

በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ ሱልልታ ለሁለት ዓመት የኖረችበት ቤት ሕገወጥ ነው ተብሎ በፀጥታ ኃይሎች የካቲት 16/2015 ዓ.ም. ፈርሶባት ዘመድ ላይ ወድቃለች።

ከሰሞኑ እየተካሄደ ካለው መጠነ ሰፊ መሆኑን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ ከገለጸው የቤት ፈረሳ ጋር ተያይዞ ያለ ምንም ማስጠንቂያ፣ ምትክ ሳይሰጣት ቤቷ ፈርሶ “ዘመድ ላይ ወድቄያለሁ ብላለች።”

ቤት ፈረሳው የተካሄደው ትናንት የካቲት 16/2015 ዓ.ም ከሌሊቱ 11 ሰዓት መሆኑን የምትናገረው እስከዳር በወቅቱም የተሰማት ድንጋጤ ቃላት አይገልጻውም ብላለች።

በእስከዳር አገላለጽ ጠመንጃ ታጥቀው የመጡ ግብረ ኃይሎች በዚህች ዕለት መጥተው የውጪውን አጥር በር ነቃቀሉ። ከዚያም ወደ ዋናው ቤት መጥተው ጣሪያውን ካፈራረሱ በኋላ ዕቃዋን ይዛ እንድትወጣ ተነገራት።

“እቃችንን እንድናወጣ ነግረውን ይሄዱና ዶዘር ይዘው በመመለስ ያርሱታል” ትላለች።

ልጇን ይዛ ከቤት አልወጣም ብላ የነበረ ቢሆንም፣ ተለምና ወደ ግቢው እንድትወጣ በኋላም በዛፍ ጥላ ስር ተጠልላ “አሻፈረኝ አልወጣም ብዬ የነበረ ቢሆንም ተለምኜ ወጣሁ” ትላለች።

አፍራሾቹ መሳሪያ ታጥቀው እና አቀባብለው በግራ እና በቀኝ ቆመው ነበር ብትልም አልወጣም ለማለት “ስለደነገጥኩ አልፈራሁም” ብለላች።

ቤቷ ከፈረሰ በኋላ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ሆና “ፈጣሪ ይድረስ ነው የሚባለው” ስትል ከቢቢሲ ጋር በስልክ በነበራት ቆይታ ተናግራለች።

በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ስድስት ከተሞችን በማጣመር 12 ክፍለ ከተሞች እና 36 የወረዳ አስተዳደሮችን በማዋቀር በተመሠረተችው ሸገር ከተማ ሱልልታ ልዩ ስሙ ቃርዮ ነዋሪ ናት።

ቤቷን ከአርሶ አደር ላይ መሬት ከገዛ ግለሰብ የገዛችው እስከዳር ውል ተፈራርማ ብትገዛውም ካርታ የለውም።

በሁለት ክፍሏ ቤት ከአራስ ልጇ በተጨማሪ ነፍሰ ጡር እህቷ ከባሏ ጋር አብረው ይኖሩ ነበር።

ስትገዛው ሁለት ክፍል ብቻ የነበረ ቢሆንም፣ በኋላ ማዕድ ቤትም ጨምረውበታል።

ከሰሞኑ አስተዳደሩ ሕገወጥ ግንባታ በሚል እንደ እስከዳር ያሉ በርካቶች ለረጅም ዓመታት የኖሩበት ቤት ፈርሶባቸዋል።

“ለአስራ አምስት ዓመት የኖርንበት ቤት ፈረሰብን”

በአዲስ አበባ የካ እና ቦሌ ክፍለ ከተሞች በኦሮሚያ ክልል፣ በሸገር ከተማ ሰበታ፣ ቡራዩ፣ ለገጣፎ፣ ለገዳዲ፣ ሱልልታ ኤር ሞጆ፣ ገላን ሰፋ ያለ የቤት ፈረሳ እየተካሄደ እንደሆነ አቶ ተስፋዬ ገመቹ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) ምክትል ዋና ዳይሬክተር ለቢቢሲ ተናግረዋል።

አንዳንዶቹ የፈረሱ ቤቶችም ከተሰሩ ከ15 እስከ 20 ዓመታትም የቆዩ መሆናቸውም ተገልጿል።

ቢቢሲም በሱልልታ ለአስራ አምስት ዓመት የኖሩና ከሰሞኑ ቤታቸው የፈረሰባቸውን ወይዘሮ አስቴር በሚያናግርበት ወቅት እያለቀሱ እና ሳግ ድምጻቸውን እየቆራረጠው “እኛ እንደ ኢትዮጵያዊ አልተቆጠርንም” ብለዋል።

እስከዳርም ሆነ ወይዘሮ አስቴር ቤታቸው ተለይቶ እንደፈረሰ ገልጸው፣ ማስጠንቀቂያም ሆነ ስለደረሰባቸው ችግር ምላሽ የሚሰጥ የመንግሥት አካል የለም ይላሉ።

አስራ አምስት ዓመት በዚህ ስፍራ እንደኖሩ የሚናገሩት ወ/ሮ አስቴር በመቶ ሺህ ብሮች (አምስት መቶ ሃምሳ ሺህ ብር) ያለቻቸውን ጥሪት አሟጠው ቤቱን እንደገዙት ያስረዳሉ። የመብራት አገልግሎት ካስገቡም አንድ ወር ደፍኗል።

ንግግራቸው በእንባ እየተቆራረጠ፣ የአካል ጉዳተኛ መሆናቸውን እየተናገሩ፣ ጥዋት ማታ እያለቀሱ እንደሚውሉም በሐዘን ተሰብረው ተናግረዋል።

ወይዘሮ አስቴር ጥሪታቸውን ያሟጠጡበት እና ለዚህን ያህል ዓመታት የኖሩበት ቤት እንዲህ ፈርሶ ሜዳ ላይ ሲወድቁ የተሰማቸው ስሜት “ውሻ እንኳን ክብር አለው” በሚል ነው የገለጹት።

ወይዘሮ አስቴር ሁለት ክፍል ያረፈበትን 200 ካሬ ሜትር ቦታ የገዙት ከአርሶ አደር ሲሆን እርሳቸውም ሌሎች ክፍሎች ጨምረውባቸዋል።

በሱልልታ አካባቢ ቤቶች መፍረስ ከጀመሩ 20 ቀናት አካባቢ እንደሆነ የምትናገረው እስከዳር የሚፈርሱ ቤቶች የኤክስ ምልክት በሰማያዊ ቀለም አንደተደረገባቸው ታስረዳለች። የእሷም ቤት ምልክት ቢኖረው ምክንያቱን ያስረዳቸው አካል ወይም መቼ እንደሚፈርስ የገለጸላቸው እንደሌለ ነው የምትናገረው።

አንዳንድ ቤቶች ከዚህ ቀደም ምልክት ተደርጎባቸው ለዓመታት ሳይፈርሱ እና ነዋሪዎቹም ሳይወጡ ስለቆዩ ነገሩ ግልጽ አልነበረም ትላለች።

“ቤታችን የፈረሰበትን ምክንያት አልተነገረንም” በማለት የሚናገሩት ሁለቱም ግለሰቦች ገንዘብም እንዲከፍሉ የተጠየቁ እና ገንዘብም በቀበሌ ከፍለው ከመጡ በኋላም እንደፈረሰ ያስረዳሉ።

ቢቢሲ ያናገራቸው ነዋሪዎች በብሔራቸው ምክንያት ኢላማ ተደርጎ ቤታቸው እንደፈረሰ በተደጋጋሚ ይናገራሉ። ኢሰመጉም እነዚህ ቅሬታዎች እንደደረሱት አቶ ተስፋዬ ተናግረዋል።

ይህንን ለማጣራት ወደ ሸገር ከተማ ከንቲባ በተደጋጋሚ ብንደውል ልናገኛቸው ስላልቻልን ምላሻቸውን ማካተት አልተቻለም።

ከቤት ፈረሳ ጋር ተያይዞ ደረሱ የተባሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች

ኢሰመጉ በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ ከቤት ፈረሳ ጋር በተያያዘ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መፈጸማቸውን የካቲት 15/2015 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስፍሯል።

በፈረሳዎቹ ወቅት ከመንግሥት በኩል ተመጣጣኝ ያልሆነ የኃይል እርምጃ መኖሩን የጠቆመው መግለጫው በዚህም የአካል ጉዳቶች ደርሰዋል ብሏል።

በአንዳንድ አካባቢዎች ደግሞ በፀጥታ ኃይሎች እና ቤቶቻቸው በሚፈርሱባቸው ነዋሪዎች መካከል ውጥረቶች መፈጠራቸውን መግለጫው ጠቅሶ፣ ቁጥራቸው ያልተጠቀሱ ሰዎችም ስለመታሰራቸው ኢሰመጉ መረጃዎችን ሰብስቤያለሁ ብሏል።

በለገጣፎ፣ ለገዳዲ አርባ አራት ማዞሪያ ኩራ ጂዳ ክፍለ ከተማ ለአስራ አምስት ዓመታት የኖሩት አቶ ሁሴን ከሰሞኑ በነበረው ውጥረት አንዲት ነፍሰ ጡር በጥይት ተመትታ ምኒልክ ሆስፒታል ህክምና እየተከታተለች እንደምትገኝ ገልጸዋል።

በርካታ ወጣቶች መታፈሳቸውን፣ መታሰራቸውን እና ድብደባ መፈጸሙንም ለቢቢሲ ገልጸዋል።

አቶ ሁሴን ለአስራ አምስት ዓመታት የኖሩበት ቤታቸው የፈረሰው የካቲት 11/2015 ዓ.ም. ነው። የእሳቸው ቤት በፈረሰበት ወቅት በተጨማሪ የ700 አባወራዎች ቤት ፈርሷል።

እሳቸውም በአካባቢው እንዳሉት ነዋሪዎች ትንሽ ቤት ያላትን 200 ካሬ ሜትር ከአርሶ አደር ላይ በ105 ሺህ ብር በውል ተፈራርመው የገዙት በ2000 ዓ.ም ነበር። በዓመታትም ውስጥ ቤቱን አስፋፍተው የሚከራዩ ቤቶችም ሰርተዋል።

በአካባቢው ለዓመታት ሲኖሩ የልማት አዋጥተዋል እንዲሁም ነዋሪ ናችሁ በሚል ዕውቅና ተሰጥቶን ጤና መድንም አውጡ ተብለናል ይላሉ።

“መብራት እና ውሃ በልማት ከፍለን ሊገባልን ትንሽ ቀን ነበር የቀረው” የሚሉት አቶ ሁሴን የአካባቢው ነዋሪ አንድ ሚሊዮን 400 ሺህ ብር መክፈሉን ገልጸው፣ ሕጋዊ ማህተም ያለው ደረሰኝ እንደያዙም ይናገራሉ። መብራት ኃይል ተሂዶም ተከፍሎ ሰሞኑን መብራት ሊቀጠል ጫፍ ደርሶ እንደነበርም ነው ለቢቢሲ የገለጹት።

ከአንድ ወር በፊት የአካባቢው አመራሮች ሰብስበዋቸው ባዶ ቤቶች የሌቦች መሰብሰቢያ እንዳይሆኑ ሊያፈርሷቸው መሆኑን እንደገለጹላቸው እና በእነዚህም ቤቶች ላይ ምልክት መደረግ መጀመሩን ያስረዳሉ።

ሆኖም አቶ ሁሴን እንደሚናገሩት ባዶ ቤቶቹን አፍርሰው ሲጨርሱ ሌሎችንም ማፍረስ እንደጀመሩ እና ለዚህም ተግባር ፖሊስ፣ ሚሊሻ፣ የአካባቢው ወጣት እና ልዩ ኃይል በጋራ ተጣምረው እየሰሩ ነው ብለዋል።

ቤት ማፍረሱም ጋር ተያይዞ ሕዝቡ ሲወጣ በጥይት የተመቱ ሰዎች አሉ ብለዋል። በአንዳንድ አካባቢዎች በር እየተገነጠለ፣ እስከ 40 ሺህ ብር አንዲከፍሉ የተጠየቁ አሉ ሲሉም ይወቅሳሉ።

በአካባቢያቸው የነበረ መስጊድ ጭምር በአፍራሽ ግብረ ኃይል ጣራው ተነቅሏል ብለዋል። “መስጊዱ ፈርሷል፣ ቁርዓኑ ተበታትኗል” ሲሉም በቁጭት ይናገራሉ።

“አንፈልጋችሁም ውጡ እየተባልን ነው” ይላሉ።

“ባለቤቴ ከወለደች ገና ሁለት ወሯ ነው” የሚሉት አቶ ሁሴን በአሁኑ ወቅት ከሁለት ልጆቻው ጋር ዘመድ ላይ ወድቀዋል።

“የምሄድበት ሁሉ ተምታቶብኛል” ብለዋል።

“መውደቂያ የለንም”

“ለዓመታት ያፈራነው ንብረት በአስር ደቂቃ ውስጥ ወድሞ፤ አሁን ደግሞ በዚህ የኑሮ ውድነት፣ ቤት ኪራይ አዲስ አበባ ላይ ጣሪያ በነካበት ሰዓት የት እንገባለን? መውደቂያ የለንም። ልጆቻችን ትምህርት ቤት ውሰዱ እያሉን ነው። የት እንውሰዳቸው?” ሲሉም ይጠይቃሉ።

አቶ ሁሴን ልጆቻቸውን ይዘው ዘመድ ቤት ቢጠጉም፣ በአርባ አራት ማዞሪያ ለአስራ አምስት ዓመታት የኖሩት ሌላኛው የአራት ልጆች አባት የሆኑት አቶ ሰይድ ሦስቱን ልጆቻቸውን ወደ ክፍለ ሃገር ልከዋል።

በአሰሪና ሠራተኛ አገናኝነት የሚተዳደሩት አቶ ሰይድ በአንድ ሺህ ብር ትንሽ ቤት ተከራይተው እቃቸውን በሸራ ውጭ ላይ አስቀምጠው ነው ያሉት።

አብዛኛው ነዋሪ በየእምነት ተቋማቱ ተጠግቶ፣ አፈር ላይ የተኙ፣ እቃቸው ውጭ ተበትኖ ያሉ፣ እዚህም እዚያም የወደቁ፣ በዘመድ አዝማዱ የተጠለሉ ሲሆን ቤተሰብ የሌላቸው ደግሞ ሜዳ ላይ ወድቀው “በአሳዛኝ ሁኔታ ላይ ናቸው” ብለዋል።

ሌሎች ደግሞ እቃቸውን እየጫኑ ወደ ወደ የመጡበት እየሄዱ ሲሆን ደብረ ብርሃን መጠለያም የገቡ እንዳሉ አቶ ሰይድ ያስረዳሉ። እቃቸውን ጭነው ወደተለያዩ ክልሎች ለመሄድ መኪናዎች ከ20 እስከ 30 ሺህ ብር ይጠይቃሉ ብለዋል።

እስከዳር መኪና ተኮናትራ መራ ቤቴ አካባቢ ለማቅናት ያሰበች ሲሆን፣ አቶ ሰይድ ሁኔታው ተስፋ አስቆራጭ ሆኖባቸዋል።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መቶች ጉባኤው አቶ ተስፋዬም የተፈናቀሉ ነዋሪዎች ያሉበት ሁኔታ በጣም የሚያሳስብ እንደሆነም ነው የሚናገሩት።

በላስቲክ ዳስ ሰርተው የሚኖሩ፣ ተጨማሪ ጉዳት እየደረሰባቸው እና ለሌሎች አደጋዎች እየተጋለጡ መሆኑንም በመጥቀስ “ሕግን ማስከበር ተገቢ ቢሆንም ሰብዓዊነት ሊሰማን ይገባል” ይላሉ።

አብዛኞቹም ነዋሪዎች የፈረሰባቸው ቤት ከ15 ዓመት በላይ የኖሩበት እንደሆነ ገልጸው “መጀመሪያ ላይ ሕገወጥ ናቸውም ከተባሉ በእንጭጩ (ከመነሻው) መቅጨት ይቻል ነበር” ሲሉም ያስረዳሉ።

አቶ ተስፋዬ እንደሚሉት “በአካባቢው ያለው ነዋሪ ማኅበራዊ መስተጋብራቸው ሰፍቶ፣ ትምህርት ቤት ልጆቻቸው እየተማሩ፣ ጥሪታቸውን አሟጠው የሰሩት ቤት ፈርሶ እሱን እንዲያጡ ተደርጎ፣ በዚህ ሁኔታ ሕግን ማስከበር ተገቢነት አለው ወይ የሚል ጥያቄን እንድንጠይቅ ነው የሚያደርገን።”

“ፈረሳው ወጥነት የሌለው አሰራር ታይቶበታል”

ኢሰመጉ ከቤት ፈረሳ ጋር ተያይዞ ባወጣው መግለጫ አንዳንዶቹ የሕግ ሥነ ሥርዓትን ያልተከተሉ፣ ሕጋዊ ቤቶችም ጭምር የፈረሱበት መሆኑን አስፍሯል።

በተጨማሪም አንዳንድ ቤቶች ደግሞ የመብራት እና የውሀ አገልግሎት የመንግሥት ተቋማት ያስገቡላቸው እና ይህ በሚደረግበት ወቅት ምንም አይነት የሕጋዊነት ጥያቄ ያልተነሳባቸው፣ አንዳንዶቹ የፈረሱ ቤቶች ከተሰሩ ከ15 እስከ 20 ዓመታት ያሳለፉ ናቸው ብሏል።

እነዚህና ሌሎች ጉዳዮች የፈረሳ ድርጊቱ ሕጋዊነት ላይ ጥያቄን እያስነሱ ነው ብሏል።

ሕጋዊ የሆነ ካርታ ያላቸው ሳይቀሩ፣ ሳይት ፕላን ያላቸው ቤቶችም እንደፈረሱ አቤቱታዎች እንደረሷቸው፣ እንዲሁም አንዳንዶቹ ሕገወጥ ቤት ገንብተው ያልፈረሱባቸው ቤቶች እንዳሉ የሚጠቅሱት አቶ ተስፋዬ፣ ወጥነት የሌለው አሰራር መሆኑን ያሰባሰቧቸውን መረጃዎች ዋቢ አድርገውም ይናገራሉ።

በስፋት እየተፈጸመ ነው በተባለው ፈረሳ አንዳንዶቹ ከጫካ ፕሮጀክት ጋር፣ አንዳንዶቹ ደግሞ ከሸገር ከተማነት ጋር ስለመያያዙ አቶ ተስፋዬ ያስረዳሉ።

እስካሁን ምን ያህል ቤቶች ናቸው የፈረሱት? በዚህስ ምን ያህል ሰዎች ተጎዱ ስለሚለው ጥልቅ ምርመራ እንደሚያደርጉና በቅርቡም ይፋ ይሆናል ብለዋል።

ከዚህ ቀደምም በተለያዩ ምክንያቶች ቤቶች የሚፈርሱ ቢሆንም አሁን በስፋት እየተደረገ መሆኑን ከደረሷቸው መረጃዎች ተረድተዋል።

የደረሱ አቤቱታዎችን ለመርመር ኢሰመጉ ሦስት መርማሪዎች እና አንድ አሽከርካሪ ወደ ሰበታ ታኅሣሥ መጨረሻ ላይ የላከ ሲሆን አራቱም ሠራተኞቹ ለእስር መዳረጋቸውን አቶ ተስፋዬ አስታውሰዋል።

ባልደረቦቹ በገላን ጉዳ ፖሊስ መምሪያ ለስምንት ቀናት ያህል ታስረው በዋስ ቢለቀቁም ጉዳዩ እልባት አላገኘም ብለዋል።

በአሁኑ ወቅት ሁኔታዎች የከፉ እንደሆኑም በርካቶች ሪፖርት ማድረጋቸውንም ያስረዳሉ።

መንግሥት ቀድመን ማስጠንቀቂያ ሰጥተናል ቢልም አቤቱታ አቅራቢዎቹ ለቢቢሲም ሆነ ለኢሰመጉ እንደተናገሩት ይህ ተፈጻሚ አልሆነም ይላሉ።

ማስረጃዎችን መመርመር ቢገባም አንዳንድ ሁኔታዎች ግን ቅድመ ማስጠንቀቂያ እንዳልተሰጠ አመላካች መሆኑንም አቶ ተስፋዬ ይጠቅሳሉ።

ለምሳሌ ያህልም ቤቷ የፈረሰባትን አራስ ሴት ዋቢ አድርገው “በምንም መልኩ ማስጠንቀቂያም እንኳን ተሰጥቶ ቢሆን መጠበቅ ይገባ ነበር። አንድ አራስ ወልዳ ተኝታ ብዙ ድጋፍ ሊደረግላት በሚገባበት ወቅት በላይዋ ላይ ቤት ሲፈርስ ትንሽ የሰብዓዊነት ጥያቄ ያስነሳል” ይላሉ።

ሆኖም ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷል ስለሚባለው ጉዳይ በአሁኑ ወቅት ድምዳሜ ላይ አልደረስንም ብለዋል።

ያለው ፈረሳ ወጥ አይደለም የሚያሰኙ ብዙ ምክንያቶች እንዳሉ የሚጠቅሱት አቶ ተስፋዬ ከሌሎች ቦታዎች ተፈናቅለው መጥተው ቦታ የተሰጣቸው ግለሰቦች እንዳሉ፣ ሕገወጥ ቤቶች ተብለው ያልፈረሱ እንዳሉም ይጠቅሳሉ።

“ወጥ አሰራር የሚኖረን ከሆነ እነዚህን ሰዎች ከማፈናቀላችን በፊት ምንድን ነው ልናደርግላቸው የሚገባው?” የሚለው መመለስ አለበት በማለት፣ እንደ መንግሥት የትኛውንም ማኅበረሰብ በተመሳሳይ ዐይን ማየት እንዳለበትም ያስረዳሉ።

“ሕግን ብቻ ማክበር ተገቢ ቢሆንም፣ እንደ ሁኔታው ግን ሰብዓዊነትንም ልናካሂድ ይገባል” ነው ያሉት አቶ ተስፋዬ።

አክለውም “እነዚህም ዜጎች ናቸው። ከዚህም ይሁን ከዚያ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ናቸው። በዝቅተኛ ኑሮም ላይ ያለ ይሁን ከፍተኛ ኑሮ ላይ ያለ፣ የትኛውም ብሔር ይሁን የትኛውም ኢትዮጵያዊ እኩል ግልጋሎት ነው ማግኘት ያለበት” ሲሉም ምክራቸውን ለግሰዋል።

በአሁኑ ወቅትም ቢሆን ቢቢሲ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች አርብ የካቲት 17/2015 ዓ.ም. ባናገራቸው ወቅት ገብርኤል የሚባልና ዶሮ እርባታ፣ ቻይና አካባቢም በርካታ ቤቶች እየፈረሱ እንደሆነ ተናግረዋል።

አቶ ተስፋዬም የፈረሳ ሂደቱ እንደቀጠለ መረጃዎች ደርሰውናል ብለዋል።

በዓለም ዓቀፍ ደረጃ የሰብዓዊ መብቶች ዓለም አቀፍ መግለጫ ማንም ሰው ለእራሱና ለቤተሰቡ ጤንነትና ደኅንነት በቂ በሚሆን የኑሮ ደረጃ የመኖር መብት አንዳለው እና ይህም መብት መጠለያን እንደሚጨምር ይደነግጋል።

ሊደረጉ የሚገቡ ጥንቃቄዎች እና መፍትሄዎች

ኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) ከቀረቡለት አቤቱታዎች በመነሳት ሊደረጉ የሚገባቸውን መፍትሄዎች እና ጥንቃቄዎች በሰሞኑ መግለጫው አካቷል።

በአዲስ አበባ ከተማ እና በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ በሚገኙ አካባቢዎች እየተከናወኑ ያሉ የቤት ፈረሳዎች ተገቢውን የህግ ሥነ-ሥርዓት የተከተሉ እንዲሆኑ እና በምንም አይነት ከቤት እና ከመሬት አስገድዶ የማፈናቀል ድርጊቶች እንዳይፈጸሙ
መንግሥት የቤት ፈረሳ እንቅስቃሴዎችን በሚያደርግበት ወቅት ሕጋዊ የሆኑ ቤቶችን ከማፍረስ እንዲቆጠብ
ሕጋዊ አይደሉም የሚባሉ ቤቶችም ቢሆኑ ቤት መስራት በሚጀመርበት ወቅት ማስቆም የሚቻልበት ሁኔታ ማመቻቸት
ከረጅም ዓመታት በኋላ የሚደረጉ ፈረሳዎች ሰብዓዊነትን ጥያቄ ውስጥ የሚከቱ በመሆናቸው የቤት ፈረሳ እንቅስቃሴው ለሕዝብ ጥቅም አስፈላጊ ሆኖ በሚገኝበት ወቅት ለሚፈርሱ ቤቶች ተገቢው ካሳ እንዲሰጥ
በቤት ፈረሳዎች ወቅት የሚስተዋሉ ከመንግሥት በኩል ተመጣጣኝ ያልሆኑ የኃይል አጠቃቀሞች በአስቸኳይ እንዲቆሙ
ከቤት ፈረሳ እንቅስቃሴዎቹ ጋር ተያይዞ የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ቤቶች በሚፈርሱበት ወቅት ለነዋሪዎች በቂ ጊዜ በመስጠት ቅድሚያ እንዲያሳውቁ
ንብረታቸውን ለማውጣት በቂ ጊዜ እንዲሰጡ ይህ ሳይሆን ቀርቶ ለወደሙ ንብረቶች ግን መንግሥት ተገቢውን ካሳ እንዲሰጥ እንዲሁም ይህንን ሕገ-ወጥ ድርጊት የሚፈጽሙ አካላትን በሕግ እንዲጠይቅ
በአካባቢ ላይ የሚኖሩ እና ቤቶቻቸው የሚፈርስባቸውን ሰዎች ጋር ውይይት በማድረግ አካታች የሆነ ዘላቂ መፍትሄን ማምጣትን አካቷል።
በአካባቢው የሚኖረው አብዛኛው ነዋሪ ዝቅተኛ ኑሮ ላይ እንደሆነ የሚናገሩት አቶ ሁሴን በበኩላቸው መውደቂያ የሌላቸው እና የዕለት ጉርስም መሸፈን የማይችሉ በመሆናቸው የቤቶች ፈረሳ ሊገታ ይገባል ይላሉ።

ከዚያ በተጨማሪም ቤታቸው ለፈረሰባቸው እና ለተፈናቀሉት “መቋቋሚያ እና መጠለያ ይሰጠን” ሲሉም ይጠይቃሉ።

*ለደኅንነታቸው ሲባል ያናገራቸውን ነዋሪዎች ትክክለኛ ስም አልተጠቀምንም።
============/////==============

Friday, February 24, 2023

በኦሮምያ ክልል ቦረና ህዝብ በድርቅ ይሰቃያል፣እነ አቶ ሽመልስ እና የኦሮምያ ባለስልጣናት ዛሬ በሸራተን አዲስ ሲዝናኑ ውለዋል።የአሁኑ እሁድም ለሌላ ድግስ እየተዘጋጁ ነው።



አቶ ሽመልስ አብዲሳ የኦሮምያ ክልል ፕሬዝዳንት ሆነው ሲሰየሙ ቃለ ምህላ ሲፈጽሙ።

በቦረና የደረሰው ድርቅ በተመለከተ:
  • ለአምስት የምርት ወቅት ዝናብ ያልዘነበበት፣
  • ከ3 ነጥብ 3 ሚልዮን በላይ የቀንድ ከብት አልቋል ይህም የክልሉ የከብት ሃብት ከሦስት አራተኛው በላይ አልቋል ማለት ነው።
  • ከሩብ ሚልዮን ህዝብ በላይ ተፈናቅሎ በ21 የመጠለያ ቦታዎች ተጠልሎ ይገኛል፣
  • አሁን እርዳታ አለ በተባለባቸው ቦታዎች ላይ በአማካይ ለስምንት ሰው በወር 15 ኪሎ እህል ለማዳረስ ቢሞከርም ይህ በቂ ባለመሆኑ ህዝብ እያለቀ ነው።

በኦሮምያ ክልል በቦረና የደረሰው ድርቅ እጅግ አስከፊ የድርቅ አደጋ ነው።ድርቁ ለኢትዮጵያ ቁርጥቀን ጊዜ ደራሽ የሆነውን እና ደጉን የቦረና ህዝብ በእዚህ ደረጃ መጉዳቱ ከልብ የሚያሳዝን ነው።የድርቁ አደጋ አስመልክቶ በዋናነት የክልሉ አስተዳደርም ሆነ ፌድራላዊ መንግስት ችግሩን አስመልክተው በተገቢ መንገድ አለመግለጻቸው አሳዛኝ ነው። በተለይ የኦሮምያ ክልል አስተዳደር ክልሉን በምን ያህል የተዝረከረከ መንገድ ብቻ ሳይሆን በህዝብ ህይወት እየቀለደ እንዳለ ያመለክታል። ይህ በእንዲህ እያለ በአቶ ሽመልስ የሚመራው የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት ዛሬ በሸራተን አዲስ ሆቴል ውሏል።ዛሬ በሸራተን አዲስ የዋሉት እነሽመልስ አብዲሳ በመጪው እሁድም በሌላ ድግስ ላይ እንደሚውሉ ነው የታወቀው። በሁለቱም ቀና የሸገር ከተማ ምስረታ በሚል የሚደረጉ የድግስ ግርግር ላይ የሚሰነብቱት እነሽመልስ እስካሁን ይህ ነው የተባለ የቦረና ድርቅን በተመለከተ የሰጡት መግለጫ የለም። የፌድራል መንግስትም ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ይህንኑ ጉዳይ አንስተው መንግስት ምን እየሰራ እንደሆነ ማብራርያ ይሰጣሉ ተብሎ ቢጠበቅም መንግስት እስካሁን ሚዛን የሚደፋ ነገር በጉዳዩ ላይ አልሰጠም። ዛሬ ለመጀመርያ ጊዜ በሚባል ደረጃ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ዜናው ላይ ጉዳዩን አስመልክቶ አንድ ዘገባ አሳይቷል።የኦሮምያ ክልል ባለስልጣናት ግን በድግስ ላይ ድግስ እየደገሱ ከሸራተን እስከ አደባባይ መታየት ላይ ተጠምደዋል። 

ከእዚህ በታች ጀርመን ድምፅ ራድዮ የካቲት 14/2015 ዓም ስለ ቦረና ድርቅ የዘገበው ሙሉ ሪፖርት ያገኛሉ።

በደቡብ ኢትዮጵያ በተለያዩ አከባቢዎች በተለይም በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን እና ሶማሌ ክልል ደቡባዊ ክፍሎች የከፋው ድቅር አሁንም መቋጫ አላገኘም፡፡ በነዚህ አከባቢዎች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ አርብቶ አደሮች ለድጋፍ እጃቸውን ያዘረጋው ድርቁ በሚሊየኖች የሚቆጠሩ የቀንድ እና የጋማ ከብቶችንም ጭምር ገድሏል አስከፊነቱም ቀጥሏል፡፡በደቡብ ኢትዮጵያ በተለያዩ አከባቢዎች በተለይም በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን እና ሶማሌ ክልል ደቡባዊ ክፍሎች የከፋው ድቅር አሁንም መቋጫ አላገኘም፡፡ በነዚህ አከባቢዎች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ አርብቶ አደሮች ለድጋፍ እጃቸውን ያዘረጋው ድርቁ በሚሊየኖች የሚቆጠሩ የቀንድ እና የጋማ ከብቶችንም ጭምር ገድሏል አስከፊነቱም ቀጥሏል፡፡

በተለይም በቦረና በርካታ ከብቶችን በማርባት ለሌሎች ይተርፉ የነበሩት አርብቶ አደሮች አሁን ለድጋፍ ፍለጋ እጃቸውን ሰጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሜትሮሎጂ እንደሚለው ግን ለአምስት ተከታታይ የዝናብ ወቅቶች በድርቅ የቀጠሉት የደቡብ ኢትዮጵያ አከባቢዎች እየመጣ ባለው የዘንድሮ የበልግ ወቅት ለመደበኛ የቀረበ ዝናብ በማግኘት ድርቁ መቋጫ ሊያገኝ ይችላል፡፡ማሊቻ ሞሌ ነዋሪነታቸው በቦረና ዞን ተልተሌ ወረዳ ነው፡፡ በዚህ አከባቢ የሃብትም የኑሮም መገለጫ የሆነው በርካታ ከብቶችን አሰማርቶ መዋል የሳቃቸው ምንጭ የደስታቸውም ጥግ ቢሆንም አሁን ያ ቀርቶ ታሪክ ሆነ ይላሉ፡፡ ምክኒያቱ ደግሞ ከተቋረጠ ወደ አምስተኛ ዙር የዝናብ ወራት እየሄደ ያለው የከፋው ድርቅ አሁንም ድረስ አለማቧራቱ ነው፡፡“ድሮ ባለን መሬት የሆነ ነገር ዘርተን ቢያንስ ለቀለባችን አናጣም ነበር፡፡ አሁን የሚታረስ የለም፡፡ መሬቱ ደርቋል እህል አያበቅልም፡፡ ከከብቶቻችን ቀረን ምንለው የለም፡፡ አሁን ተስፋ ቆርጠን የችግር የመጨረሻ ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡ ካሉኝ የበተሰብ አባላት ያልተራበ ማንም የለም፡፡ እንደውም ሶስቱ የቤተሰቦቼ አባላት በዚሁ ተማረው እግራቸው ወዳመራቸው ሄደዋል፡፡ አሁን ሰው በርሃብ ወደ መሞቱ ነው፡፡ አሁን እዚሁ ጎረቤተ ርሃብ በሚመስል መልኩ ሰው ሞቶ እዛ እያስተዛዘን ነው” ሲሉም ድርቁ እያደረሰባቸው ያለውን የማይገፋ አደጋ በሃዘኔታ ያብራራሉ፡፡

አርብቶ አደር ማሊቻን ጨምሮ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የቦረና ነዋሪዎቹ በተራዘመው ድርቅ አሁን አቅማቸው ተንኩታኩቷል፡፡ ዴንጌ ዋሪዎም በዚሁ ወረዳ ነዋሪ ሲሆኑ አሁንስ ተስፋችን ጨልሞ ሰማይ ብናይ ምንም ጠብ ያለ ነገር አጥተናል ከሚሉ ናቸው፡፡

“ታውቃለህ በድርቁ ሰው የካፋ ችግር ውስጥ ነው ያለው፡፡ ያላቸው ከብቶች በግ እና ፍየል እንኳ ሳይቀር አልቀዋል፡፡ ጠብ ያለ ዝናብ ባለመኖሩ የሚወጣ እህል የለም፡፡ የሚሸጥ ከብት በሙሉ በድርቁ አልቀዋል፡፡ አሁን ሰው በችግሩ በህይወት እስከማለፍ ደርሷል፡፡ የሚቀመስ በመጥፋቱ በዚሁ ዓመት ብቻ በዚህች ቀበሌያችን አራት ሰው የሚደርስ ተጎሳቅለው አልፈዋል፡፡ አሁን የሞቱት መጀመሪያ ሰውነታቸው ያብጣል፡፡ ከዚያን ምንም አይነት ምግብ መውሰድ ተስኖያቸው ተጎድተው ይሞታሉ” ሲሉ አስቸጋሪ ያሉት ማህበረሰቡ ያለበትን ችግር አብራርተዋል፡፡

ላለፉት አምስት የዝናብ ወራት ቦረና ምንም አይነት ዝናብ እንዳላገኘ የዞኑ እንስሳት ሃብት መምሪያ ኃላፊ ዶ/ር ቃሲም ጉዮ ከዚህ በፊት ለዶይቼ ቬለ በሰጡት ቃለመጠይቅ በከፋ ሁኔታ ቀጥሏል ባሉት ድርቅ በዞኑ ከቤት እንስሳት ብቻ 2.3 ሚሊየን ያህሉ ማለቃቸውን አስረድተዋል፡፡

የዞኑ አስተዳደርም ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ እንዳመለከተው ከ800 ሺህ በላይ የቦረና ህዝብ አሁን ላይ የእለት ደራሽ ምግብን ይጠባበቃል፡፡ ከቦረና በተጨማሪም ሶማሌ ክልልን ጨምሮ በደቡብ ኢትዮጵያ በተለይም ቆላማዎቹ አከባቢዎች ላይ የከፋው ድርቅ ጉዳትን አስከትሎ በርካቶችን የምግብ ዋስትና አሳጥቷል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሜትሮሎጂ ኢንስቲትዩት ግን ይህ የደቡብ ኢትዮጵያው ድርቅ ምናልባትም በዚህ ዓመት መቋጫውን ሊያገን ይችላል የሚል ተስፋን ያጫረውን ትንቢያ እየሰጠ ይገኛል፡፡ አሳምነው ተሾመ (ዶ/ር) በኢንስቲትዩቱ የሜትሮሎጂ ትንቢያ እና ቅድመ ማስጠንቀቂያ መሪ ስራ አስፈጻሚ ናቸው፡፡ ከየካቲት እስከ ግንቦት ወራት የሚያጠቃልለው የዘንድሮ የበልግ ወቅት ምንም እንኳ ዘግየት ብልም ለደቡብ ኢትዮጵያ አከባቢዎች በቂ ዝናብን ይዞ ይመጣል ሲሉም ይገልጻሉ፡፡ “ለደቡብ ኢትዮጵያ አብዛኛው አከባቢዎች የበልግ ወራት ዋነኛ የዝናብ ማግኛቸው ወቅት ነው፡፡ በዓመት ከ60 በመቶ በላይ ዝናብ የሚገኙም በዚሁ ወቅት ነው፡፡”

እንደ የሜትሮሎጂ ትንቢያ ባለሙያው ዶ/ር ተሾመ ማብራሪያ፤ ዓለማቀፋዊና አከባቢዊ የአየር ሁኔታዎችን ከግንዛቤ በማስገባት ተዘጋጀ ባሉት የበልግ ወራት የአየር ትንቢያ፤ ከመደበኛው ጋር የተቀራረበ ዝናብ በድርቅ በተመቱቱ የደቡብ ኢትዮጵያ አከባቢዎች ላይ ይኖራል፡፡ “አሁን ላይ የመካከለኛ የፓሲፊክ ውቅያኖስ መካከለኛ አከባቢዎች በላሊና ክስተት ውስጥ መሆኑ ቅዝቃዜ እንዲኖረው ያደርገዋል፡፡ የባህሩ ሙቀት ግን በሂደት ወደ መደበኛ ሁኔታ ይሄዳል፡፡ የህንድ ውቅያኖስም በተመሳሳይ ከቅዝቃዜ ወደ መደበኛ የሙቀት ደረጃ መሄዱ ከግንዛቤ ሲገባ አዎንታዊ የዝናብ መጠን ነው የሚጠበቀው፡፡ እነዚህ ክስተቶች በተለይም በበልግ ወቅት ዝናብ በሚያገኙ የአገራችን አከባቢዎች ብዘገይ ነው እንጂ መደበኛ እና ለመደበኛ የተጠጋ ዝናብ እንዲያገኙ ያስችላል፡፡”

==============/////===========

Thursday, February 23, 2023

የራሱን ሕግ የሚቆረጥም መንግስት እና በኦሮምያ ክልል እየተፈጠረ ያለው ስብስብ የ''ሂዝቦላ'' ሽብር ቡድን ግልባጭ ስብስብ ይመስላል።



  • ከሽብርተኛው ሂዝቦላ ጎን የሚሰለፍ ሚናውን ከአሁኑ ይለይ።ኢትዮጵያን ያለ እና ኢትዮጵያ ለሁሉም እኩል ትሆናለች የሚል የሽብር ቡድኑን ለመፋለም ይነሳ!
=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

የራሱን ሕግ የሚበላ መንግስት  

የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ የመንግስት ስሪቱን በሚዘውረው ብልጽግና ጎሳን መሰረት ያላደረገ ፓርቲ መሆኑን ቢናገርም፣በሕወሃት/ኢሃዴግ ከተቀመረው የጎሳ አደረጃጀት ያልራቀ ብቻ ሳይሆን ይልቁንም ክልሎች ለመረን የለሽ እና ህግ አልባ ባለስልጣናት ስር እንዲወድቁ እና ህዝብ ለመረረ ፈተና እንዲወድቅ ያደረገ ፓርቲ ሆኗል። ለእዚህ ማሳያው እሩቅ ሳንሄድ በወልቂጤ በቅርቡ ውሃ ለመጠየቅ በወጣው ህዝብ ላይ የክልሉ ልዩ ኃይል በከፈተው ተኩስ የሰው ህይወት ቢጠፋም፣ ጠያቂ የሕግ አካልም ሆነ ጠያቂ የመንግስት ክፍል እስካሁን ወደ አደባባይ እንዲቀርብ አልተደረገም። ይህንን ተከትሎ በወልቂጤ ከሰባት ቀን በላይ ህዝብ በቤት የመቀመጥ አድማ ሲያደርግ ጉዳዩን እና ችግሩ ላይ የተነፈሰ አንድም የመንግስት መገናኛ ብዙኃን ቢያንስ እስካሁን እኔ አላየሁም፣ አልሰማሁም። የመንግስት መገናኛ ብዙኃንን  በሚከፍለው ቀረጥ የሚያስተዳድረው ግን ይሄው ህዝብ መሆኑ ጥያቄ ውስጥ አይገባም። 

አሁን ያለው ሃገራዊ ሁኔታ ለመግለጽ የተለያዩ መስኮችን በፈርጅ በፈርጁ ማቅረብ ይፈልጋል። ሆኖም ግን ከሁሉም ፈርጆች ውስጥ የሕግ ጉዳይ ብቻ ብንመለከት ብልጽግና እጅግ የተዘባረቀ እና አለባብሶ የማለፍ ሂደት ላይ እንደተጠመደ ለማወቅ በጣም ግልጽ ነው። እዚህ ላይ ከህወሃት ጋር የተደረገውን ስምምነት ሂደት እና ሰሞኑን የኦሮምያ ክልል ለሸኔ እያቀረበ ያለው የእንደራደር ጥሪ መመልከት በቂ ነው። ህወሃት በኢትዮጵያ የተወካዮች ምክርቤት በሽብርተኝነት ፈርጆት ሳለ መንግስት ከምክር ቤቱ ጋር ምንም ዓይነት ንግግር ሳያደርግ ማለትም ቢያንስ የሆኑ ቅድመ ሁኔታዎች አስቀምጦ ምክር ቤቱ የሽብርተኝነቱ ፍረጃ አይነሳም ግን ውይይት መንግስት ያድርግ የሚል ይሁንታም ሳያገኝ የሄደበት ስምምነት አሁን መልሶ ለራሱ ለትግራይ ህዝብም ሌላ ትርምስ፣ለቀጠናውም ሆነ ለኢትዮጵያ ያልረጋ የሰላም ከባቢያዊ ሁኔታ ፈጥሯል። ይህ ዛሬ ስንመለከተው ቀላል ይመስላል።ከመንግስታዊ መርህ እና ህግ ጉዳይ ግን የአካሄድ ጥያቄ አለበት ብቻ ተብሎ የሚታለፍ አይደለም። በእርግጥ የሃገር ሰላም ጉዳይ አንገብጋቢ ጉዳይ ነው። ከእዚህ አንጻር የታየ ነው የሚል ምክንያት የሚሰጡ አሉ። ሆኖም ግን የአንድ ሰዓት ስብሰባ የተወካዮች ምክር ቤት አድርጎ በጉዳዩ ላይ ሃሳብ ሰጥቶበት ያልሄደበት ጉዳይ ላይ ይህንን ያህል እርቀት ተሄዶም ዛሬም ግልጽነት የጎደለው የተድበሰበሰ ሁኔታ ውስጥ መሆኑ አሁንም መልሰን የመርህ እና የህግ ጉዳዩ እንድናይ ያስገድደናል።

የሰሞኑ የኦሮምያ ጨፌ ምክር ቤት ከሸኔ ጋር ልነጋገር ብሎ ያወጣው መግለጫ ደግሞ በራሱ ሌላ የሕግ ጥሰት አለበት። በመጀመርያ ደረጃ ሸኔን ሽብርተኛ ያለው የፌድራል ተወካዮች ምክርቤት እንጂ የክልል ምክር ቤት አይደለም። ስለሆነም የክልል ምክርቤት በምን ስልጣኑ ነው ከሸኔ ጋር ለመደራደር መግለጫ የማውጣት ስልጣን ያለው? እነኝህ ሁሉ ሁኔታዎች ብዙ የሕግ ጥያቄዎች ያስነሳሉ። ሕግ ስትጠፋ ደግሞ ፍትሃዊነት ያጣ መንግስታዊ አሰራር ደግሞ መዘዙ የትዬለሌ ነው።አሁን በአጭሩ እየታየ ያለው መንግስት እራሱ ያወጣውን ሕግ የሚቆረጥም መሆኑ ነው። እንደእዚህ ዓይነቱ እና ሌሎች የመንግስት የተዘባረቀ እና የራሱን ህግ የመቆርጠም  አካሄድ ይሆን እንዴ የፌድራል ጠቅላይ ፍርድቤት ፕሬዝዳንት መዓዛ አሸናፊን ከስራ ያስለቀቃቸው? ችግሩ የህግ እና መርህ ጥሰቶቹ ለአሁኑ ትውልድ ብቻ ሳይሆን ለመጪው ትውልድም ይዘውትና ትተውት የሚሄዱት አደጋ መኖሩ ነው ክፋቱ።ጥያቄው የራስን ሕግ እየቆረጠመ የሚሄድ መንግስት ምን ያህል ሊጓዝ ይችላል የሚለው ነው?

በኦሮምያ ክልል እየተፈጠረ ያለው ስብስብ የ''ሂዝቦላ'' ሽብር ቡድን ግልባጭ ስብስብ ይመስላል።

የህወሃት መንግስት ወደ መቀሌ ሸሽቶ ከሄደ በኋላ የኢትዮጵያ ህዝብ ተስፋ ያደረገው የጎሳ ፖለቲካ ይቀራል።ሁሉም በእኩልነት የሚኖርባት ኢትዮጵያ ትመጣለች በሚል ነበር የለውጥ ሂደቱን የደገፈው። ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥም በኢትዮጵያ ከትግራይ ቀጥሎ የኦሮምያ ክልል የኢትዮጵያን ሰላም በመንሳት እና የግጭት እና የህዝብ ሰቆቃ የየዕለቱ ተግባር የሆነበት ክልል የለም።በኦሮምያ ክልል የጽንፍ አቋም እንዲበቅል ካደረገው የጀዋር ቡድን ጀምሮ እስከ የኦነግ የጽንፍ ክፍል ድረስ ሁሉም ወደ ክልሉ ገብቶ ከክልል ልዩ ኃይል እስከ የቀበሌ ስልጣን ድረስ ለመቆጣጠር ችሏል። ይህም ሆኖ በኦሮምያ ክልል ውስጥ ይህንን የጽንፍ ኃይል የሚቃወም ነገር ግን በእጅጉ እየተገፋ ያለ የኦሮምያ ክልል ተወላጅ እና በፌድራል ደረጃ ያለ ባለስልጣንም ብዙ ነው።

በኦሮምያ ክልል እየተፈጠረ ያለው ስብስብ የ ሂዝቦላ ሽብር ቡድን ግልባጭ ስብስብ ነው። የእዚህ የሽብር ቡድን አደረጃጀት ወታደራዊ ብቻ ሳይሆን ምጣኔ ሃብታዊ እና ማኅበራዊ አደረጃጀት አለው።ሂዝቦላ በፍልስጤም ምድር ይብቀል እንጂ በሊባኖስ የፖለቲካ፣ምጣኔ ሃብት እና ማኅበራዊ ህይወት ውስጥ እንዴት ሰርጾ እየገባ ለመንቀል ያልቻሉት ቅንቅን እንደሆነ ያለፈውን የሊባኖስ የቅርብ ታሪክ ላይ ቡድኑ ምን ያህል ተጽዕኖ እየፈጠረ የሽብር ሥራ እየሰራ እንዳለ መረዳት ይቻላል። ሂዝቦላ በሊባኖስ ውስጥ ትምህርት ቤቶች፣መስጊዶች፣ሆስፒታሎች እና የትራንስፖርት ኩባንያዎች ሁሉ ስለከፈተ በሊባኖስ ህዝብ ህይወት ውስጥ ገብቶ ምስኪኑን ህዝብ ለመንዳት እየሞከረ ነው። ከእዚህ ባለፈ ደግሞ በሊባኖስ መንግስት ውስጥ ሂዝቦላን የማይደግፉ ያላቸውን አስገድሏል፣አሰድዷል እንዲሁም በቤተሰባቸው ላይ ሳይቀር ጥቃት ፈጽሟል።

በኦሮምያ ክልል በክልሉ አስተዳደር፣ምክርቤት፣ልዩ ኃይል እና የእምነት ተቋማት ሳይቀር እንደአሜባ እየተስፋፋ ያለው የጽንፍ ኃይል ልክ እንደ ሄዝቦላ በሺህ የሚቆጠሩ ንጹሃንን በወለጋ እና በሌሎች ቦታዎች ፈጅቷል፣ንብረት አቃጥሏል፣ዘርፏል። ይህ ጥቃት ወደ ከተሞች ሲመጣ በከፍተኛ የሙስና ዘረፋ ላይ ተዘፍቆ በሚልዮን የሚቆጠር ሃብት ለማንቀሳቀስ ሲሞክር ይታያል።አሁን የጽንፍ ኃይሉ ከልሉ ፕሬዝዳንት ሽመልስ እስከ ታች ያለ የቀበሌ ሊቀመንበር መለየት ባልተቻለበት መንገድ ክልሉን በሂዝቦላ አደረጃጀት ለመምራት እየተንቀሳቀሰ ነው። የእዚህ ሂዝቦላዊ ንቅናቄ አንዱ መገለጫ የትዕዛዝ መስመሩም ሆነ የሴራ ሃሳብ አመንጪዎቹ አንድ ቦታ ላይ የተሰበሰቡ ሲሆን የተለያዩ ሴራዎችን በመጎንጎን ኢትዮጵያን ለማመስ እና ተጽዕኗቸው ውስጥ ለማስገባት ይሞክራሉ። ይህ ሂዝቦላዊ እንቅስቃሴ ህዝብ እንዲገዛለት የተለያዩ የማስፈራርያ አጀንዳዎች ይፈበርካል።አጀንዳዎቹ እንደማያዋጡ ቢያውቅም የሚፈልገው ኢትዮጵያውያንን ማሸበር ስለሆነ ሰላም ለመንሳት ይሞክራል። ለምሳሌ በቅርቡ በአዲስ አበባ የኦሮምያ መዝሙር ይዘመር አጀንዳ እና በቅርቡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ቅዱስ ሲኖዶስ ለመክፈል የተደረጉት ሙከራዎች ሁሉ ከእዚሁ በኦሮምያ ክልል ከሚንቀሳቀሰው እና እንደ አሜባ በፌድራል መንግስት ውስጥም ሰርጎ ገብቶ ሂዝቦላዊ አደረጃጀት ከያዘው ''ቲንክ ታንክ '' ቡድን የመነጨ ሃሳብ እና በልዩ ኃይሉ እና በገንዘብም ሲደገፍ የነበረ ነው።

በኦሮምያ የበቀለው ሂዝቦላዊ መዋቅር የመንግስትን ፖሊሲ ሁሉ ለማንቀሳቀስ ሲሞክር ብቻ ሳይሆን ሲሰራ በግልጽ እየታየ ነው።ከህወሃት ጋር የተደረገው ስምምነት ምንም እንኳን የኤርትራው ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ አሜሪካ ሰር ነው እንዳሉት ከዋሽንግተን ይምጣ እንጂ በኦሮምያ ያለው የሂዝቦላዊ እንቅስቃሴ ሃሳብ አመንጪዎች ከህወሃት ጋር በጓሮ መነጋገር የጀመሩት ቀድመው ነው።ለሂዝቦላዊ ስር በኦሮምያም ሆነ በፌድራል መንግስት ስር መስደድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ያሳዩት ቅጥ ያጣ ቸልተኝነት እና ስሱ የሆነ ዓይን አንዱ እና ዋና ምክንያት ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የሸኔ ጉዳይ በወለጋ ጫካዎች ውስጥ ብቻ ሳይሆን በኦሮምያ ክልል ሙሉ መዋቅር እና ልዩ ኃይል ውስጥ እንዲሁም በፌድራል መንግስት መዋቅር ውስጥ እንደሆነ በግልጽ አያውቁም ማለት ሞኝነት ነው። ሆኖም ግን ጉዳዩ ገፍቶ እዚህ ደረጃ ከመድረሱ በፊት የተወሰዱ እርምጃዎች አልተሰሙም። ይልቁንም የሂዝቦላ እንቅስቃሴ ሰሜን ሸዋ ላይ ልዩ ኃይል እያለ ያሰለፋቸውን አስቁሞ ከአማራ ክልል ወደ አዲስ አበባ የሚመጡትን የሚያግድ፣ ሰሞኑን ደግሞ ሸገር ከተማ ተብሎ በተሰየመው የአዲስ አበባ ዙርያ ባሉ ነዋሮዎች ላይ የማፈናቀል ሥራ እየሰራ ነው። በሽገር ዙርያ ያሉት ነዋሪዎች እየተፈናቀሉ ያሉት አማራ በመሆናቸው መሆኑን ለአንከር ሚድያ እና ኢሳት የገለጹበት መንገድ ሁሉ የሂዝቦላ ግልባጭ እንቅስቃሴ ፋሽሽታዊ ሥራ በግልጽ የሚያሳይ ነው።

ለማጠቃለል ኢትዮጵያን የሚያምሱ የሕግ ጥሰት የታየባቸው የመንግስት የራሱን ሕግ የመቆርጠም መዘዝ እና የሂዝቦላ ግልባጭ የሆነው በኦሮምያ ክልል እና በፌድራል መንግስት ውስጥ የሚንቀሳቀሰው የጎሳ ለበስ ግን ፍጹም ፋሺሽታዊ እንቅስቃሴ ዋና ግቡ ኢትዮጵያን በበለጠ አተራምሶ በሆነ የመንግስት ቅርጽ ሁሉንም ክልልሎች ለመዋጥ ነው።ይህ ዓላማው ደግሞ በሌሎቹ የብልጽግና አባል ክልሎች በደንብ ታውቋል።ለእዚህም ነው ሰሞኑን የአማራ ክልል ያወጣው መግለጫ ከአፋር እስከ ደቡብ ክልል፣ከሱማሌ እስከ ጋምቤላ ክልል በውስጥ አዋቂ እንደተዘገበው በጣም ትክክል ነው በሚል የተስማሙበት። ምክንያት የሂዝቦላ ግልባጭ በመጀመርያ ሊውጣቸው የፈለገው እንደርሱን እንደሆነ ገብቷቸዋል።መፍትሔው አንድ እና አንድ ነው።ከሽብርተኛው ሂዝቦላ ጎን የሚሰለፍ ሚናውን ከአሁኑ ይለይ።ኢትዮጵያን ያለ እና ኢትዮጵያ ለሁሉም እኩል ትሆናለች የሚል የሽብር ቡድኑን ለመፋለም ይነሳ!

============//////=========

Monday, February 20, 2023

ሰበር ዜና - የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ዛሬ ማምሻውን መግለጫ አወጣ። ''የፖለቲካ ግልሙትና የሚፈጽሙ እና የሴራ ፖለቲካ እየሸመኑ፣ዘረኝነት እያቦኩ'' ያላቸውን መታገል የሚያስፈልግበት ወሳኝ ጊዜ ላይ ደርሰናል ይላል መግለጫው።ሙሉ መግለጫውን ይዘናል።

ባሕርዳር ከተማ


በትላንት የታሪክ ምርኮኞችና በነገው ተስፋችን ቁማርተኞች ሕልውናዋን የማታጣ ሃገር መገንባት ከሁላችንም የሚጠበቅ ኀላፊነት ነው።

ባሕር ዳር: የካቲት 13/2015 ዓ.ም (አሚኮ) 

በምድራችን ካላፉት የሥርዓተ መንግሥታት ታሪክ ውስጥ በራሳቸው ሕዝብ መካከል ተቃርኖን እየሸመኑ አንዱን የማኅበረሰብ ክፍል ከሳሽ፣ ሌላኛውን  ደግሞ ተከሳሽ የሚያደርግ ጥልፍ በመጎንጎን የሀገረ መንግሥትነት ሕልውናቸውን ያጸኑም ሆነ ዘላቂ ሰላምና እድገታቸውን ያረጋገጡ መንግሥታት ተብለው ለአብነት ያህል እንኳ  ስማቸው የሚጠቀስ ነገሥታትም ሆኑ መንግሥታት የሉም። 

እንዳለመታደል ሆኖ ከታሪክም ሆነ ከአሁናዊ ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ ተመስርቶ የአንድ ሀገር ሕዝብን በአንድነት እና እኩልነት ላይ በተመሰረተ ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ ሕዝብና ሀገራቸውን ለመለወጥ ከመታተር ይልቅ፤ በየሚዲያው የጥላቻ ተረክን እየነዙ ፖለቲከኞች በፖለቲካ ገበያው ውስጥ ናኝተው ይታያሉ፡፡ 

መታወቅ ያለበት ሃቅ የትላንት መጥፎ ታሪክ ጠበቃዎች አይደለንም። ልንሆንም አንችልም። ሁኖም ግን ታሪክ ትምህርት ቤት መሆኑን እናምናለን። የትላንት ታሪካችንም ቢሆን መጥፎ ብቻ አይደለም። መጥፎ ታሪክ ካለም ለመጥፎ ታሪኩ ጠበቃ የመሆን ፍላጎት የለንም። ይልቁንም የትናንትናውን መጥፎ ታሪክ ላለመድገም እንጥራለን አብዛኛውን በጎውን የጋራ ታሪካችንን ደግሞ አሻሽለን ትውልድን ለመጥቀም እንተጋለን። ነገር ግን የትላንት የታሪክ ምርኮኞች ሆነን ህዝባችንን ለፖለቲካ በሽታ የማጋለጥ ፍላጎቱም ትልሙም የለንም። አላማችንም አይደለም። 

ይሁን እንጅ አሁን አሁን የትላንት ታሪክ ምርኮኛ ፖለቲከኞች ታሪክን እያዛቡ በማመንዠክ ዛሬያችንን ስለነገው ተስፋችን ከመሥራት ይልቅ ስለትላንቱ ተረከ-ታሪክ እሰጥ-አገባ መቆም የትውልዳችን ወትሯዊ ውሎ ሲሆን ይስተዋላል፡፡ 

የትላንት ታሪክ ምርኮኛዎች ትናንትን ከዛሬ በዉል ለይቶ ወደ ነገ መሻገር ሲሳናቸዉ በዘረኝነት ላይ የተመሰረተ ቁሞ ቀር የፖለቲካ አስተሳሰብን ማመንዠክ ልዩ ክህሎትና መገለጫቸው  እየሆነ መጥቷል፡፡  

ጀንበር መሽቶ በጠባ ቁጥር ልብስና ወንበር እየቀየሩ በተቀናጀ እና በተናበበ መንገድ የሚረጩት መርዛማነቱ ከልብስና ወንበራቸው ጋር አብሮ ያልተቀየረ የከፋፋይነት እርካሽ ፖለቲካዊ ብያኔና ፍረጃ የሀገርና የሕዝብን ሰላም፣ አብሮነት እና ልማት ምን ያህል እያቀነጨረው እንደሆነ ሊገነዘቡት አልቻሉም ወይም አልፈለጉም፡፡ 

ይህን መሰሉ ፖለቲካዊ ግልሙትና በሕዝብ ትከሻ ላይ ተንጠልጥሎ ስሁት ትርክት እየነዙ ደም አፋሳሽ በሆነ መንገድ  በሥልጣን ለመኖር ወይም ወደ ስልጣን ለመምጣት ቅጽበታዊ እድል ለማግኘት ካልጠቀመ በስተቀር  ለሀገር አንድነትና ሕልውና ፋይዳ ቢስ ስለመሆኑ ከሥርዓተ መንግሥታትና ከነገሥታቱ ታሪክም ሆነ ከዘመናዊው የፖለቲካ ሳይንስ አስተምህሮት መማር ይቻላል፡፡ 

በዚህ ወቅት በሰፊ ሀገርና በታላቅ ሕዝብ ውስጥ እየኖሩ የጠበበ ግላዊና ቡድናዊ የጥቅም ፍላጎትን የሕዝብ አስመስሎ በማቅረብ፣ በጥላቻ ላይ ተመስርቶ ፤ ስሁት ትርክትን ተደግፎ ግጭት እየዘሩ፤ መከራን ኮትኩተው ሞት እያሳጨዱ ቡድናዊ ጥቅሜን አስቀጥላለሁ ብሎ ማመን ከትናንቱ ታሪክና ከነገው ተስፋ ጋር ተጻራሪ መሆንን ከማስረገጡ ባሻገር ዛሬን በሕይወት የመኖር ጸጋን ለመንፈግ የፖለቲካ ቁማር ቋሚ ሰልፈኝነትን ያስረዳል፡፡ 

ይህን መሰሉ አሰላለፍ የአፍታ ተዝናኖት ይሰጥ ካልሆነ በቀር የጀንበር ማብቂያ ያህል እድሜ ያለው ግላዊም ሆነ ቡድናዊ ሕልውነትን አይሰጥም፡፡ የሰላም፣ የልማትና የዴሞክራሲ ያደረ ጥያቄ እና ያልበረደ ፍላጎት ያለውን ሕዝብ እየመሩና ለመምራት እየሻቱ በተቃራኒው የሴራ ፖለቲካ እየሸመኑ፤ ዘረኝነትን እያቦኩ መኖር የሚቻልበት እድልም ጊዜም የለንም፡፡  

ለዘመናት ተዋዶና ተዋህዶ በፍቅርና በአንድነት፣ በብሔርና በጎሳ ሳይከፋፈል፣ በቋንቋና ባህል ልዩነት ሳይለያይ፣ ብዙኅነቱን ተቀብሎ ለዘመናት ክብሩንና ታሪኩን ጠብቆ የኖረውን የኢትዮጵያ ሕዝብ የትላንት ታሪክ ምርኮኞች የሚከውኗቸውን ኢትዮጵያውያንን በቋንቋ እና በዘር የሚከፋፍሉና ሕዝባችን ውስጥ ቅራኔና ጥላቻ የሚፈጥሩ ንግግሮችንና ተግባራትን እንደ አንድ ሕዝብ  አምርሮ ሊቃወም፣ ሊታገልና ከውስጡ ሊያገላቸው ይገባል፡፡ 

ይህ ወቅት መላው ኢትዮጵያዊ እንደ አንድ ልብ ተባብሮ የታሪክ ምርኮኞችን መታገል የሚያስፈልግበት ወሳኝ ምዕራፍ እየሆነ መጥቷል። ሞቅ ቀዝቀዝ በሚል የትግል ሂደት ጠማማ የታሪክ ምርኮኞችና ቅን ልቦና የተሳናቸው የፖለቲካ ቆማሪዎች በኢትዮጵያ እና በኢትዮጵያውያን ላይ የጋረጡትን አደጋ ማስቀረት የሚቻለው ለእውነትና መርህ በመገዛት መታገል ሲቻል ነው። 

ስለሆነም የእስካሁኑ የትግል ስልትና አካሄድ ብቻውን በቂ ባለመሆኑ ሁሉን አቀፍና አሳታፊ፣ ተጠያቂነት ያለው ህዝባችንን ያማከለ፣ በመልካም ዓላማ ሀገር ግንባታን ማዕከል ያደረገ፣ ወጥነት ያለው፣ የሀሳብና ዴሞክራሲያዊ ፍትሐዊ ትግል ማድረግ የሁላችንም የሁል ግዜ  መደበኛ ሥራ ሊሆን ግድ ይላል።  

በትላንት የታሪክ ምርኮኞችና በነገው ተስፋችን ቁማርተኞች ሕልውናዋን የማታጣ፤ በጠንካራ የሕዝብ አንድነትና እኩልነት ላይ የፀና ሀገረ መንግሥት ለማቆም መረባረብ ከሁላችንም የሚጠበቅ ሃላፊነት ነው፡፡ 

የምናልመው ለውጥና ስኬትም ሆነ የሕዝባችን መሰረታዊ ጥያቄዎች በምኞትና በፍላጎት ብቻ ሊፈቱ የሚችሉ አለመሆናቸው ታውቆ ሁሉም ዜጋ ችግሮቻችንን ውጫዊ በማድረግ የሆነን አካል ብቻ እንዲፈታ ከመጠበቅ ወጥቶ፤ የበኩሉን ድርሻ በማድረግና በመተጋገዝ ተደማምጦ በአንድነት ለለውጥና ስኬት በመታገል ተስፋና ለጋ ውጤቶቻችንን በማዝለቅ እንደ ሕዝብ ለገጠመን ፈተና ደግሞ የጋራ መፍትሔ እያበጁ መሄድ ይገባል። አማራጩም ይሄው ነው!!

የአማራ ክልል የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ቢሮ

Saturday, February 18, 2023

ቤተክርስቲያን ባሕረጥበባት (መዝሙር) ቪድዮ

                                                                     

   
               

Friday, February 17, 2023

ህገወጦቹ እና የጀርባ ያለው ኃይል የሚፈልጉት ህዝብ በቁጣ ሁከት እንዲያስነሳ እና ሃገር እንዲተራመስ በእዚህም የጽንፈኞቹ መንግስት መመስረት ነው።ምዕመናን በጥንቃቄ መጓዝ ያስፈልጋል።

አዳማ፣ ናዝሬት ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን


በእዚህ ጽሑፍ ስር 
  • የህገወጡ ቡድንና የጀርባ ደጋፊው ኃይል ዋና ፍላጎት
  • በብልጽግና ውስጥ ያለው የችግሩ ሥር እና በሽመልስ የሚመራው ኦሮምያ ብልጽግና ውስጥ ያለው ሥር አሁን ይለያያል።
  • ምዕመናን በጥንቃቄ መሄድ ይገባናል።መንግስትም ሕግ የማስከበር ኃላፊነቱን የመወጣት ወሳኝ ጊዜ ደርሷል።

======
ጉዳያችን
======

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ውስጥ በጵጵስና ከሚያገለግሉት ውስጥ ሦስቱ በህገወጥ መንገድ ቅዱስ ሲኖዶስም ሆነ ቅዱስ ፓትርያሪኩ ሳያውቁ ኢጲስ ቆጶስ መሾማቸው እና ይህንኑ ተከትሎ ቅዱስ ሲኖዶስ በሦስቱም ላይ የውግዘት ውሳኔ ማስተላለፉ ይታወሳል።

ይህ በእንዲህ እያለ ክትናንት በስቲያ በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ሰበር ዜና በተላለፈው ዜና መሰረት ሦስቱም በሕገወጥ መንገድ የወጡት  እና ትናንት የካቲት 9 እና ዛሬ የካቲት 10/2015 ዓም በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን በቅዱስ ሲኖዶስ፣ህገወጦቹ ሦስቱ፣ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣በሚኒስትር ደረጃ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳይ አማካሪ ሙሓዘ ጥበብ ዲ/ን ዳንኤል ክብረት፣የጠቅላይ ሚኒስትሩ የጸጥታ ጉዳይ አማካሪ አምባሳደር ሬድዋን እና የአነጋገሩ ሽማግሌዎች ጭምር በተገኙበት የተደረጉትን ንግግሮች ለህዝብ ተላልፈዋል።በእነኝህ ውይይቶች ላይ ማንም ህዝብ ሊፈርድ በሚችለው እና እራሳቸው ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ ከእዚህ በፊት ከሰጡት መግለጫ በተለየ በእዚህ ውይይት ላይ በቅዱስ ሲኖዶስ በኩል ምንም ዓይነት የአካሄድም ሆነ የፍትሓዊነት ችግር እንደሌለ በአንደበታቸው ሲመሰክሩ ታይተዋል።

ከእዚህ በኋላ ዛሬ የካቲት 10/2015 ዓም የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ እና ሥራአስኪያጅ ብጹዕ አቡነ ጴጥሮስ እና ብጹዕ አቡነ አብርሓም ማምሻውን በሰጡት መግለጫ በስምምነቱ መሰረት ሦስቱም እየሄዱ አለመሆናቸውንና በህገወጥነቱ ለመግፋት ማሰባቸውን የሚገልጽ መግለጫ መስጠታቸው እና ከእዚህ መግለጫ በኋላ ቤተክህነት በሚገኘው የቀድሞ ቤታቸው ውስጥ እንደገቡ በመግለጫቸው ገልጸዋል። 

የህገወጡ ቡድንና የጀርባ ደጋፊው ኃይል ዋና ፍላጎት

አሁን የህገወጡ ቡድን (የቀድሞ ሦስቱ ጳጳሳት) ተልዕኮ ግልጽ እየሆነ ነው።በኦሮምያ ክልል ህዝብ ሆ! ብሎ ይቀበለናል ያሉት ስሌት ተገላቢጦሽ ሆነባቸው። በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ አዳራሽ በነበረው ውይይት ላይም ይህንኑ የህዝብ መነሳት እና በሄዱበት ሁሉ እንዳልተቀበላቸው ልክ ቤተክህነት ዱርዬ የገዛባቸው አድርገው ሊያቀርቡት ሞክረዋል። ኦሮምያ ክልል ያሉ ሰብረው የገቡባቸው ቤተክርስቲያኖች ሁሉ ህዝብ ቤተክርስቲያን መሄድ አቁሞ ቤቱ ተቀምጧል። በእዚህም ምክንያት አብያተ ክርስቲያናቱ ካለቅዳሴ ወና ሆነው የተቀመጡ ሲሆን በወለጋ አንዳንድ ቦታዎች ደግሞ አቡነ ናትናኤል ከእዚህ በፊት የቀደሱት ቅዳሴ በድምጽ ቅጂ እያቀረቡ የተቀደሰ ለማስመሰል ከቤት ያለውን ምዕመን ሊያታልሉ ሲሞክሩ ከቅዳሴ በኋላ በሞባይል ስልክ ያለው ዓለማዊ ሙዚቃ ሲገባ ሁሉ ተሰምቶ ቤተክርስቲያንን መዘባበቻ አድርገዋታል። 

በሽመልስ አብዲሳ የሚመራው የኦሮምያ ክልል ይህንኑ የህገወጡን ቡድን ከማጀብ ጀምሮ በተለያዩ ሆቴሎች እየቀለበ ከጽንፈኛ ቡድኖች ጋር እንዲመክሩ የሚያመቻች አካል ሆኗል። የኦሮምያ ክልል በብዙ መልኩ ከማዕከላዊ መንግስት ፈጽሞ የተለየ ብቻ ሳይሆን በከፍተኛ የሙስና ዝቅጠት ውስጥ የገቡት የጨፌ ምክርቤት አባላት ጭምር ግርግር በመፍጠርና የኦነግ ሸኔን ዓላማ በቢሮ ተቀምጠው አንድ በአንድ እያስፈጸሙ ይገኛሉ። በአሁኑ ሰዓት በኦሮምያ የሚኖረው ህዝብ ከኦነግ ሸኔ እኩል የኦሮምያ ልዩ ኃይልን ይፈራል፣ይጠላል። ይህ በእንዲህ እያለ የኦሮምያ ጨፌ የክልል ምክርቤት ለሸኔ የሰላም ጥሪ ማድረጉ ዛሬ ተሰምቷል።ሸኔ የሚሰራውን ሁሉ የኦሮምያ ክልል ልዩ ኃይል እየሰራው ነው። ዛሬ የኦሮምያ ክልል ጥሪ ያደረገው ለራሱ ነው ወይንስ ለሸኔ የሚለው በራሱ ጥያቄ መሆኑን ብዙዎች ይስማሙበታል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አንጻር እየተንቀሳቀሱ ያሉት ህገወጥ የቀድሞ ጳጳሳትም ሆኑ እነርሱን አጅቦ የተነሳው የኦሮምያ ብልጽግና ዋና ዓላማ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ብጥብጥ እንዲነሳ እና በእዚህ ሳብያ የኦሮምያ ክልል ከሸኔ ጋር ሆኖ አዲስ አበባን ለማጥቃት በእዚህ ትርምስ ከህወሃት ጋር ተመሳጥረው ኢትዮጵያን አተራምሶ የጽንፈኞቹን መንግስት ማቆም ነው።የቤተክርስቲያኒቱ ህገወጦች መንቀሳቀስ እንደጀመሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በተለይ የህገወጦቹን በሚደግፍ መልኩ የተናገሩት የብዙዎችን ቁጣ ቀስቅሷል። ነገሩ የፖለቲካ ጨዋታ ያለበት መሆኑ በትክክል ይሸታል። ከመግለጫቸው ብኋላ ግን የተቅላይ ሚኒስትሩ የለዘበ አቀራረብ ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አባቶች በኩል ስህተት እንደሌለ በሰሞኑ የተለቀቁት የህገወጡ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባቶች በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ ያደረጉት ውይይት ላይ ተንጸባርቋል። ለእዚህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሃሳብ መቀየር የታየባቸው ምክንያቶች ውስጥ የሚከተሉት ተጠቃሽ ናቸው።እነርሱም  
  •  የኦርቶዶክሱ ማኅበረሰብ ከሃገር ውስጥ እስከ ውጭ ያሳየው ንቅናቄ
  • የክልል መሪዎች ከደህንነት ሚንስትር ጋር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባደረጉት ስብሰባ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ያለፈውን መግለጫ በብርቱ ስለተቃወሙ እና የህጋዊ ሲኖዶስ ህጋዊነት መንግስት ማክበር እንዳለበት በጥብቅ ትዕዛዝ ስላስተላለፉ እና
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩም እራሳቸው ከብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በቤተመንግስት ያደረጉት ውይይት ላይ በአባቶች ላይ የሚጠቅሱት አንድም ነቁጥ ሳላላገኙ ይልቁንም በቃላቸው እንደተናገሩት ቤተክርስቲያን በቋንቋ አንጻር እየሰራች ያለውን ሥራ ከእዚህ በፊት የማያውቁትን ማወቃቸውን በመግለጻቸው የሚሉት ይጠቀሳሉ።

በብልጽግና ውስጥ ያለው የችግሩ ሥር እና በሽመልስ የሚመራው ኦሮምያ ብልጽግና ውስጥ ያለው ሥር አሁን ይለያያል።

አሁን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ላይ የገጠማት ችግር ሃይማኖታዊ ሳይሆን ዛሬ የቅዱስ ሲኖዶስ መግለጫ ላይ አቡነ አብርሃም እንዳሉት ፖለቲካዊ ችግር ሆኗል። ስለሆነም ፖለቲካዊ ችግሮች በማኅበራዊ ሚድያ ላይ በድፍኑ በሚታዩ የዘመቻ አስተያየቶች ደምድሞ ቁጭ የሚባልበት አይደለም። ጉዳዩ በተለያዩ ዕይታዎች ሲተነተኑ እና ተበትነው ሲቀርቡ ማድመጥ እና መመርመር ይገባል።አሁን በሚታየው ሁኔታ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አንጻር ያለው የብልጽግና አሰላለፍ እና የሽመልስ እና የኦሮምያ ክልል የጽንፈኛ ቡድን ከጀርባ ከባዕዳን ጋር ከሚያገናኙ አገናኝ መኮንኖች ጋር ያለው አሰላለፍ ይለያል። በብልጽግና በኩል አንዳንድ በእምነት የማይመስሏት ይህ የቤተክርስቲያኒቱ ላይ የተፈጠረውን ሁኔታ እንደ መልካም አጋጣሚ አይተው ቤተክርስቲያንን መውጊያ አድርገው ለማቅረብ ቋምጠው ቀርበው ነበር። ብልጽግና ሲባል ግን ሥራ አስፈጻሚ አካሉ የአማራ ክልል፣የአፋር፣ሱማሌ፣ደቡብ እና ሌሎች ክልሎችን የያዘ በመሆኑ እና የሥራ አስፈጻሚው አካል ደግሞ የሕግ መከበር አስፈላጊ መሆኑ ላይ እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ህጋዊ ሲኖዶስ ማክበር ላይ የሰጡት አስተያየት እና የምዕመናን ከሃገር ውስጥ እስከውጭ መነሳት ብልጽግናም ነገሩን ቀለል አድርጎ ለማየት የሞከረበት ዕይታ ስህተት እንደነበር ብቻ ሳይሆን የመንግስት ለውጥ ሊያስነሳ የሚችል የህዝብ ማዕበል ሊነሳ የመቻሉ ሁኔታ ግልጽ በመሆኑ ከህገወጦቹ ጋር በመቆም ጉዳዩ እንደማይፈታ ግልጽ በመሆኑ በሽመልስ የሚመራው የኦሮምያ ብልጽግና ያህል ሌላው የብልጽግና ሥራ አስፈጻሚ ቢያንስ የእነ ሽመልስ የድፍረት መንገድ መጨረሻው ሞት እንደሚሆን ግልጽ ሆኖለታል። ስለሆነም ከላይ የተሰጡት ምክንያቶች ሳብያ በብልጽግና ውስጥ ያለው የችግሩ ሥር እና በሽመልስ የሚመራዊ ብልጽግና ውስጥ ያለው ሥር አሁን ይለያያል። ይህንን ልዩነት አይቶ መሄድ በጅምላ ደምድሞ ከመሄድ (የቤተክርስቲያኒቱ ወቅታዊ ችግር ፖለቲካዊ መሆኑን እስከተረዳን ድረስ) የስሩ መጠን የበዛበትን ትክክለኛ ቦታ ለይቶ ማወቅ ቢያንስ በፖለቲካ አቀራረብ ላይ ጠቃሚ ነው። 

ምዕመናን በጥንቃቄ መሄድ ይገባናል።መንግስትም ሕግ የማስከበር ኃላፊነቱን የመወጣት ወሳኝ ጊዜ ደርሷል።

ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት የህገወጥ ቡድኑ ተልዕኮም ሆነ ከጀርባ የሚዘውሩት ዋና ፍላጎት የህዝብ ስሜት አስነስቶ ያልተደራጀ እና በብስጭት የተነሳሳ ብጥብጥ ማስነሳት ነው። በእዚህም ሳብያ የጽንፈኛ መንግስት ለማቆም ከሸኔ እና ህወሃት ጋር በመሆን ለመመስረት ዕቅድ አለ። በእዚህም ለዘብተኛው የብልጽግና ቡድንን መምታት ይፈለጋል። ለእዚህ ደግሞ ሃይማኖት የህዝብ ስስ ብልት በመሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን መተንኮስ ተፈልጓል። ስለሆነም ምዕመናን በቅዱስ ሲኖዶስ አባቶች ላይ ያለውን ዕምነት ከእዚህ ቀደም እንደነበረው መተማመኑን እና ከጎናቸው መሆኑን አጽንቶ መቀጠል አለበት።የቤተክርስቲያን ጥያቄ የፖለቲካ ጥያቄ አይደለም። ስለሆነም ብጹአን አባቶች የቤተክርስቲያኒቱ የማይነኩ እና የሚነኩ ድንበሮችን ስለሚያውቁ ከየተለያዩ ቡድኖች ሃሳቦች በተለየ የቅዱስ ሲኖዶስን ድምጽ መስማት መከተል ይገባል።

በሌላ በኩል መንግስት ሕግ የማስከበር ኃላፊነቱን መወጣት አለበት።ቤተክርስቲያን እየተሰበረች በሕገወጦች ስትወረር ቆሞ የሚመለከት ብቻ ሳይሆን ከሰባሪዎች ጋር አጅቦ እየገባ ንጹሃንን እየገደለ ህገወጦችን የማስገባት እኩይ ተግባር ባለፈው ሳምንታት በኦሮምያ ክልል ሲፈጸም ሰንብቷል።አሁን ደግሞ ጠቅላይ ሚንስትሩ፣አማካሪዎቻቸው እና ሽማግሌዎች በተገኙበት ስምምነት ከተደረገ በኃላ ህገወጡ ቡድን ሰጠ ተብሎ የተላለፈውን መግለጫ ተከትሎ የተከናወኑ የህግ ጥሰቶችን መንግስት ሕግ ማስከበር ካልቻለ፣ ህዝብ ህጉን ሊያስከብር መነሳቱ አይቀርም።ይህ ህግ የማስከበር ሂደት የመንግስት በሃይማኖት ጣልቃ የመግባት ጉዳይ ጋር አይገናኝም። ጉዳዩ ህጋዊ ሰውነት ያለው ከ70 ሚልዮን በላይ ምዕመን ተቋም የመጠበቅ እና ያለመጠበቅ መንግስታዊ ሃላፊነት ነው።ስለሆነም መንግስት ምስክር በሆነበት የህግ ጥሰት በዝምታ ከተመለከተ ብልጽግና ኢትዮጵያን በማፍረስ ሂደት ተሳታፊ ተደርጎ በታሪክም ሊያስጠይቀው ይችላል። 

ለማጠቃለል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ላይ ያፈነገጡት ቡድኖችም ሆኑ ተባባሪዎች መመርያ የሚቀበሉት ከጽንፈኛ የሸኔ ቡድን ነው።ከሸኔ ባለፈም ለእዚህ ልዩነት ከፍተኛ ገንዘብ እያወጡ ኢትዮጵያን ለመበጥበጥ የሚንቀሳቀሱ ባዕዳን ካለምንም ጥርጥር እየደገፉ እንደሆነ ከሰሞኑ ለህገወጡ ቡድን በሃገር ውስጥ ያሉ ግለሰቦች ያዋጡት ዝርዝር ሰሞኑን በዘሓበሻ ሚድያ የተለቀቀውን ስንመለከት የባዕዳን እጅ በሃገራችን ነጋዴዎች በኩል ምን እየሰሩ እንደሆነ ግልጽ አድርጓል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከጳጳሳት ጋር ያደረጉት ውይይ ላይ በእዚህ ጉዳይ እጃቸውን የከተቱ እነማን እንደሆኑ እነማን ኢትዮጵያን እንደሚወዱ እና ማን ሊያጠፉ እንደሚፈልጉ በሰሞኑ ሂደት ተመልክተናል ያሉት ይህንን የባዕዳን እጅ ጋር የተሞዳሞዱትን ነው ወይ? ማለት ይቻላል።በመሆኑም ምዕመናን በጥንቃቄ እና ለዘለቄታዊ መፍትሄ፣መንግስት ደግሞ ሕግ በማስከበር የማያወላውል አቋሙ ቀጥ ብሎ መሔድ ይጠበቅበታል።
======================////===========

Wednesday, February 8, 2023

የብልጽግና ፓርቲ በመንግስት ስም ''የጸጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል መግለጫ'' በሚል ያወጣው መግለጫ ፋሺሽት ጣልያን በ1929 ዓም በአዲስ አበባ ካወጣው መግለጫ ጋር ተመሳሳይ የሚያደርገው ጉዳይ።


አዲስ አበባ የቅዱስ ሲኖዶስ የሦስት ቀን ጥቁር የመልበስ ትዕዛዝ መሰረት ምዕመናን ጥቁር ለብሰው።

  • የብልጽግና ወታደሮች የፈጠሩትን የጸጥታ እና የደህንነት ችግር እንዳላየ ያለፈ በግፍ የተሞላ እና በደም የተጨማለቀ መግለጫ ነው

ግፍ እና የግፍ ግፍ ሞልቶ ፈሷል። ኢትዮጵያ ያመነችው፣ሚልዮኖች አደባባይ ወጥተው የደገፉት፣በመስቀል አደባባይ ቦንብ ሲወረወረወርበት እኔ ልሙት ብለው ከፊታቸው ቀድመው የደረሱ እና ህይወታቸውን የሰጡለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ኢትዮጵያን አሳዝኗታል። ሰሞኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግፍ በተሞላ አነጋገር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ላይ ህገወጥ ሲኖዶስ በኦሮምያ ክልል መመስረቱን ቀላል ጉዳይ ነው ብለው ከመቀለዳቸው በፊት፣ቤተክርስቲያኒቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ከባለቤታቸው ጋር በቤተክህነት ጠርታ በቅዱስ ፓትሪያሪኩ እጅ ካባ ሸልማለች።

ይህ ሁሉ የህዝብ ፍቅር መሰረቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያን እና አንድነቷን እንደሚደግፉ እና ለእዚያም እንደሚሰሩ በንግግራቸው በመግለጻቸው ነበር።ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ባለፈው ሳምንት ግዙፍ ሃገራዊ የጸጥታም ሆነ የኢትዮጵያን ህልውና አደጋ ላይ የሚጥል ብቻ ሳይሆን ሃገር የሚበትነውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስን የሚከፍል ህገወጥ ቡድን በኦሮምያ ክልል መመስረቱን አስመልክተው ጉዳዩን አቅልለው ለማሳየት ከመሞከር አልፎ የህገወጦቹ ቃል አቀባይ እስኪመስሉ ድረስ በጉዳዩ ላይ የካቢኔ አባሎቻቸውም ቃል እንዳይተነፍሱ ሲያስጠነቅቁ አምሽተዋል።

ዛሬ የካቲት 1፣2015 ዓም በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የሁለት ሰዓት የዜና እወጃ ላይ ሦስት ጊዜ እየተደጋገመ የተነበበው የብልጽግና ፓርቲ በመንግስት ስም ''የጸጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል መግለጫ'' በሚል ያወጣው መግለጫ ፋሺሽት ጣልያን በ1929 ዓም በአዲስ አበባ ካወጣው መግለጫ ጋር ተመሳሳይ የሚያደርገው ነጥብ አለ።

የዛሬው የብልጽግና የጸጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል መግለጫ ከጣልያን የ1929 ዓም መግለጫ ጋር የሚያመሳስለው ጉዳይ የግፍ መልዕክቱ ይዘት ነው። የጸጥታና ደህንነት ግብረ ኃይል መግለጫ የደህንነትና የጸጥታ የሚለው ስሙ ለኢትዮጵያ ከሆነ ሰሞኑን ከ30 በላይ የቤተክርስቲያኒቱ ምዕመናን ካህናትን ጨምሮ በጥይት ሲረግፉ፣ቤተክርስቲያን ደጆቿ በብልጽግና ወታደሮች እና በህገወጡ ቡድን ጀሌዎች የመሰበራቸው ጉዳይ የጸጥታና ደህንነት ጉዳይ አለመሆኑ ያስገርማል። የወጣቶችን ደም እየረገጡ የቤተክርስቲያንን ቅጽር ግቢ እየገቡ በሯን እየሰበሩ የገቡትን ህገወጦች በተመለከተ አንዳች ቃላት ያልጨመረው የዛሬው  የጸጥታና የደህንነት ግብረ ኃይል መግለጫ ጣልያን በየካቲት 12፣1929 ዓም የአዲስ አበባ ህዝብን ጨፍጭፎ ለጭፍጨፋው ምክንያት ያደረገው እራሳቸው  ኢትዮጵያውያንን  በወቀሰ መልኩ ካወጣው መግለጫ ጋር ተመሳሳይ ያደርገዋል።

በኢትዮጵያ ስም የጸጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል የተባለ የመንግስት ኮሚቴ መግለጫ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ምዕመናን ላይ የብልጽግና ታጣቂዎች ያደረሱትን የግፍ ጭፍጨፋ በዛሬው መግለጫው ዓይኑን በጥቁር ጨርቅ ሸፍኖ ምንም እንዳልሆነ ለማለፍ መሞከሩ በአሳፋሪ የመንግስት ታሪክ ውስጥ ተመዝግቦ ይኖራል። ቤተክርስቲያኒቱ መከፈል የለብኝም፣በመክፈል ስራው ደግሞ የመንግስት ግልጽ የሆነ ድጋፍ አለ፣ ካህናቶቼን እና ምዕመናኖቼን እየገደሉብኝ ነው ብላ በሦስት ቀን ጾምና ጸሎት ማዘኗ፣በደረሰባት ግፍ ልጆቿ ጥቁር ለብሰው መውጣታቸው ሁሉ እና ይህንንም ድምጿን ለማሰማት አደባባይ ታቦተ ህጉን ይዛ በሰላማዊ መንገድ ድምጼን ለምድርም ለሰማይም ገዢም አሰማለሁ ማለቷ እንደ ሁከት ፈጣሪ አድርጎ የሚተነትነው የብልጽግና የጸጥታና የደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል መግለጫ እንደ የጣልያኑ የ1929 ዓም የተገደለውን ህዝብ በወቀሰበት እና እራሱ ጨፍጭፎ በደም የተጨማለቀ መግለጫ እንዳወጣ ዛሬም ብልጽግና ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ከሠላሳ በላይ ንጹሃን ምዕመናን ካህናትንም ጭምር ገድሎ ስለሞቱት ምንም ያልተነፈሰው እና ገዳዮቹ የብልጽግና ወታደሮች የፈጠሩትን የጸጥታ እና የደህንነት ችግር እንዳላየ ያለፈ በግፍ የተሞላ እና በደም የተጨማለቀ መግለጫ ነው።
============////===========


Saturday, February 4, 2023

እነ አቶ አካለወልድ (የቀድሞው አቡነ ሳዊሮስ) ከዐቢይ መንግስት ጋር ቤተክርስቲያንን ለማፍረስ ያቀዱት ቀድሞ እንደነበር አዲስ መረጃ ወጥቷል። በአዕምሯችን ውስጥ የሚነሱ በወቅታዊ የኢትዮጵያ እና የቤተክርስቲያን ጉዳይ ዙርያ 7 ጥያቄዎች እና አጫጭር መልሶች።

  • ቤተመንግስትም ያለህ መከላከያም ያለ የኦርቶዶክስ ልጅ ሥራህን ለማንም ትተህ እንዳትወጣ።
  • ሃገር በጽንፈኛ እየፈረሰ ከኦርቶዶክሳዊነት ጎን እስከቆመ ድረስ ኢትዮ 360፣የቀድሞ የህወሃት አባል፣ኢህአፓ፣ የመቀሌ ልጅ፣የሱማሌ ፕሬዝዳንት ብሎ መለያየት የለም።ሁሉን በአንድ መስመር ተይዞ ይሄዳል።
==========
ጉዳያችን
=========
እነ አቶ አካለወልድ (የቀድሞው አቡነ ሳዊሮስ) ከዐቢይ መንግስት ጋር ቤተክርስቲያንን ለማፍረስ ያቀዱት ቀድሞ እንደነበር አዲስ መረጃ ወጥቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እና ምስጢራዊ የኦሮምያ ብልጽግና ቡድን ከአቶ አካለወልድ (የቀድሞው አቡነ ሳዊሮስ) ከዐቢይ መንግስ ጋር ቤተክርስቲያንን ለማፍረስ ያቀዱት ቀድሞ እንደነበር አዲስ መረጃ ወጥቷል። ግንቦት 24፣2014 ዓም ቅዱስ ሲኖዶስ የርክበ ካሕናት ጉባዔ 
ሲደረግ የጠቅላይ ቤተክህነት ሥራአስኪያጅ ምርጫ ሲደረግ የቤተክህነት ምስጢራዊ የብልጽግና ቡድን አቶ አካለወልድን ለማስመረጥ ከፍተኛ ፍትግያ አድርጓል።በምርጫው ሂደት ላይ ጉባዔውን ለማወክ ግልጽ የሆነ ማስፈራራት ሲፈጸም የኢጣልያ፣ፈረንሳይ እና አካባቢው ሊቀጳጳስ እና የኦስሎ መካነ ቅዱሳን ቅዱስ ገብርኤል ወአቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን የበላይ ጠባቂ አቡነ ሕርያቆስ ያደረጉት ተጋድሎ በአግባቡ ለሕዝብ አልተገለጸም።አቡነ ሕርያቆስ ጉባዔውን በግልጽ በመገሰጽም ሆነ የምርጫው ሂደት በህገ ወጦች እጅ ሊገባ ሲል ጉባዔውን እረግጠው በመውጣት ምርጫው ትክክለኛ መስመር እንዲይዝ ከፍተኛ ተጽኖ ለመፍጠር የሞከሩበት ሂደት በቤተርክስቲያኒቱ ታሪክ ሲዘከር የሚኖር ነው።

ይህ ብቻ አይደለም አቡነ ሕርያቆስ ምርጫው በመንግስት ማስፈራርያ መሆን የለበትም ብለው ጉባዔውን እረግጠው ከወጡ በኋላ ተለምነው ሲገቡ ምርጫው በሕጉ እንዲፈጸም ቃል አስገብተው ነበር። በመጨረሻም በምርጫው አርባ አምስት ሊቃነ ጳጳሳት የተገኙ ሲሆን ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅነት ከተወዳደሩት
1. ብፁዕ አቡነ አብርሃም 26 ድምጽ በማግኘት ሲመረጡ
2. ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦንስ 12
3. የቀድሞው ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ 7 ድምጽ አግኝተዋል፡፡
ለቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ በእጩነት ከቀረቡት መካከል
1. ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ 20 ድምጽ በማግኘት ሲመረጡ
2. ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል 17
3. ብፁዕ አቡነ ኤልያስ 8 ድምጾች አገኙ።

በቀጣይ ቀናት የብልጽግና የደህንነት ሰዎች በአቶ አካለወልድ አለመመረጥ በመብሸቅ ወደ አቡነ ሕርያቆስ ያረፉበት ቤት ድረስ ተልከው ለማስፈራራት የሞከሩ ሲሆን አቡነ ሕርያቆስም ካለአንዳች ፍራቻ ተገቢውን ምላሽ እንደመለሱ መረጃ አለ።ይህ ማለት አቶ አካለወልድ በቤተክህነት ሥራ አስኪያጅነት እንዲመረጡ ቢደረግ ኖሮ ምን ዓይነት ከባድ ጥፋት በቤተክርስቲያን ላይ የብልጽግና ቡድን ሊያደርስ በምስጢር ተዘጋጅቶ እንደነበር በሚገባ መረዳት ይቻላል። በመሆኑም አሁን እየተፈጸመ ያለው ቤተክርስቲያንን በግልጽ የመውረር እና የማፍረስ ተግባር መንፈስ ቅዱስ ባወቀ በእነ አቡነሕርያቆስ ላይ አድሮ ጉባዔውን ባያጸና ኖሮ በምስጢራዊ መስመር ከባድ ጥፋት ሊፈጸም እንደነበር በጣም ግልጽ ነው።

በአዕምሯችን ውስጥ የሚነሱ በወቅታዊ የኢትዮጵያ እና የቤተክርስቲያን ጉዳይ ዙርያ 20 ጥያቄዎች እና አጫጭር መልሶች።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ለማፍረስ ጥረት እየተደረገ ባለበት በእዚህ ጊዜ ብዙ ጥያቄዎች በአዕምሯችን ውስጥ ይመጣሉ።ከእነኝህ ውስጥ 20ዎች ብዬ ለመምረጥ ሞክርያለሁ።በእነርሱ ላይ የራሴን ምላሽ ለመስጠት እሞክራለሁ።እነኝህ ጥያቄዎች ነገ በማኅበራዊ ሚድያም ሆነ ሌላ ቦታ ስናገኝ አንድ ዓይነት ምላሾች እና ምንም ዓይነት መደናገሮች መኖር የለባቸውም።

ጥያቄ = የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እንደ ፖለቲከኞች በድርድር ይፈታል?

መልስ= ፈጽሞ በድርድር አይፈታም።ያለው መንገድ ቤተክርስቲያንን የከዱት ይቅርታ ቅዱስ ሲኖዶስን ጠይቀው፣የወሰዱትን መልሰው፣የሰበሩትን ጠግነው ሲቀርቡ ብቻ ነው። ፖለቲከኞችም ሆኑ አሁን የህዝቡን መነሳት አይቶ የጽንፍ ኃይሉ እንደፖለቲካ ድርድር የሚለው አሁን የህዝቡን መነሳት እና ነገሩ እንደማያዋጣ ሲያውቁ የሚያቀርቡት ነው።

ጥያቄ = ኦርቶዶክሳውያን የመንግስትን ሥራ ከቤተመንግስትም ከመንግስት ስራም ለቀው መውጣት አለባቸው?

መልስ = ፈጽሞ። መጀመርያ ሥራህ ቤተመንግስት ሆነ ጦር ሰራዊቱ ውስጥ ክልል ሆነ ቀበሌ ለቀህ መሄድ የለብህም። የሚፈለገው ይሄው ነው። በመጀመርያ ሃገሬ የእኔ ነች ማንም በችሮታ የሚሰጠኝ እና የሚነጥቀኝ አይደለችም ብሎ ማመን ያስፈልጋል።ይህንን እምነትህን ነው ቀድሞ ሊነጥቁህ የሚፈልጉት።ወለጋ ሃገርህ እንዳልሆነ ሊነርግሩ ሲሞክሩ ውስጥህ ሃገርህ ሌላ እንደሆነ የሚስብ ስሜት ሊፈጥሩብህ እንደሞከሩ ተረዳ።ስለሆነም ኢትዮጵያ ሁሉ ሃገርህ፣ስራህ ሁሉ ማንም በችሮታ የማይሰጥህ መሆኑም ማመን እና ባለህበት ሃገርህን እንደምትጠቅም ማመን አለብሕ

ጥያቄ = ቤተክርስቲያንም ሃገሬም ለገጠማት ችግር የእኔ ድርሻ ምንድን ነው?

መልስ = መጀመርያ ባለህበት የሥራ መስክ ይህ ያንተ ግዛት መሆኑን እመን። ቦታህን አትልቀቅ። ቀጥሎ ውጭ ሃገር ሁን ሃገር ቤት፣ቀበሌ ውስጥ ሁን መምህር በእጅህ ባለው እና ባንተ ልክ ልትሰራ የምትችለውን በደንብ ለይተህ በሌሎች የማይደጋገም ሥራ ከአንተ ችሎታ አንጻር መስራት ያለብህን ለይተህ ሥራ። ዝም ብለህ ተመልካች ከሆንክ ከሞተው በላይ ከቆመው በታች መሆንህን እመን። 

ጥያቄ = ዐቢይ ነገ በቴሌቭዥን ቀርቦ እያለቀሰ ተሳስቼ ነበር ብሎ ሊቀርብ ይችላል? ይህ ለውጥ ያመጣል?

መልስ = የለቅሶ ድራማ ጠብቅ።ለዓላማ የማይከፈል ነገር የለምና ያደርገዋል። ነገር ግን ባይሳካለትም በህሊናው ግን ቤተክርስቲያኒቱን ሰውቷታል። ቢያንስ በቅርቡ በሰጠው መግለጫ ህገወጦቹን እጅግ በሚያሳፍር ደረጃ ደግፏል።ማንም እንዳያግዳቸው የራሱን ካቢኔ ጨምሮ አስፈራርቷል።የሙስሊሞች ችግር ጊዜ የሰላም ሚኒስቴር መስርያቤት ችግሩን እንዲፈታ ተመድቦ የነበረበት ጊዜ እንዳልነበር አሁን ግን የሰላም ሚኒስቴርን ያስፈራራው እራሱ ጠቅላዩ መሆኑ የሄደበትን እርቀት ያሳያል።

ጥያቄ = ቤተክርስቲያንን የማጥፋት ሥራ የአካባቢውን ጂኦ ፖለቲክስ ይቀይራል?

መልስ = በትክክል ይቀይራል። ቤተክርስቲያንን የማጥፋት ሥራ በአንዳንድ መንግስታት የረጅም ጊዜ ዕቅድ ነበር።አሁን ዐቢይ ይህንን መነገጃ ለማድረግ ግልጽ ድፍረት አሳይቷል።ቤተክርስቲያን መፍረሷ ደግሞ ጂኦ ፖለቲካውን ያበላሻል ያሉ እንደሩስያ ያሉ መንግስታት በጥብቅ ጉዳዩን እየተከታተሉ ለመሆኑ አምባሳደሩ የሰጡት የሰሞኑ መግለጫ ማሳያ ነው።አምባሳደሮች በአንድ ሃገር የውስጥ ጉዳይ ብዙ አስተያየት አይሰጡም።የሩስያው አምባሳደር ይህንን ያህል እርቀት የሄዱት የቤተክርስቲያኒቱ ጉዳይ የጂኦፖለቲካ ጉዳይ ላይ የሚያዛንፈው ብዙ ጉዳይ ስላለ መሆኑን መረዳት ይቻላል።

ጥያቄ = ስሜታችን በንዴት እንዲጎዳ የሚያደርጉ ሥራዎች ሲገጥሙ ምን ላድርግ?

መልስ = በወቅቱ ሁኔታ መበሳጨት ተፈጥሯዊ እና ጤነኛነት ነው።ነገር ግን የቤተክርስቲያን ጠላቶች ዋና ግብ ማበሳጨት ብቻ ሳይሆን ተስፋ የቆረጥክ እንድትሆን ምስጢራዊ የስነ ልቦና ዘመቻ ማድረግ ነው። በመሆኑም አንዳንዴ ቤተክርስቲያንን ለማጥፋት የተነሱ መሪዎች እየገለፈጡ በተነሱት ፎቶ በኢቲቪ እንዲታዩ የሚያደርጉት የተረጋጉ ለመምሰል እና የስነ ልቦና ጦርነት ለማድረግ እንደሆነ በሚገባ ተረዳ።እራስህን አረጋግተህ ለሃገርህም ሆነ ለቤተክርስቲያንህ የሚገባውን ከራስህ ጠንካራ መንፈሳዊ ህይወት እና ኃይል ጋር እራስህን በራስህ አስታጥቅ እንጂ እየተበሳጨህ እራስህን አትጉዳ።ሥራ የሚጀምረው ምን ሰራሁ? ከሚል የራስ ጥያቄ ነው።

ጥያቄ = የሃይማኖት ጉዳይ ሲሆን ብቻ ልናገር ፖለቲካ ይቅርብኝ?

መልስ = ይህ ዛሬ ለደረስንበት ደረጃ ያበቃ የስህተት አስተሳሰብ ነው።አሁን ቤተክርስቲያንን እያመሰ ያለው የዶግማ ጉዳይ አይደለም። የጎጠኛ ፖለቲከኞች ከህወሃት ኢሃዴግ እና ብልጽግና እየተወራረሱ ያመጡት የዘር ፍጅት ፖለቲካ ነው።ስለሆነም መሞገት ያለብህ ፖለቲካውንም ጭምር ነው። ቤተመንግስቱ ሲስተካከል ቤተክህነቱ ይረጋጋል። ቤተመንግስቱን ትቼ ቤተክህነቱ ላይ ብቻ ልመልከት ካልክ ያለፈውን ስህተት ትደግመዋለህ። ቤተክርስቲያን ጎጥ አትቀበልም።ይህ ሃይማኖታዊ መልዕክት ነው። ጳጳሳት ሳይቀሩ የመንግስት ጎጠኛ መንግስት አንቀበልም ማለት ይችላሉ።ማውገዝም ይችላሉ። ቤተክርስቲያኒቱ የጎጥ ፖለቲካ መንቀል በትክክል ትችላለች።ይህ ደግሞ ፖለቲካ አይደለም። ሃይማኖታዊ መልዕክት ነው።ጎጠኝነት ክርስቲያናዊ አለመሆኑን በመንገር እና በመቃወም ብቻ ኢትዮጵያውያን ኢትዮጵያን ማቆም ይችላሉ።ይህንን የጎጠኘነት ፖለቲካ መቃወም ከካህን እስከ ዲያቆን፣ከጳጳስ እስከ ምዕመን ሊቃወመው የሚችለው አጀንዳ ነው።

አበቃሁ!
============////=========

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...