ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Sunday, June 23, 2019

አይዞሽ! ኢትዮጵያ።ከባህርዳሩ እና ከአዲስ አበባው ግድያ በኃላ ሶስት አካላት ሶስት ነገሮችን መማር አለባቸው (የጉዳያችን ማስታወሻ)

    ጀነራል ሰዓረ መኮንን 
ዶ/ር አምባቸው መኮንን 
  • የጀነራል ሰዓረ መኮንን ግድያ ከሀገር ውስጥ ሴራ ይልቅ የውጭ እጅ ምናልባትም የባህርዳሩን ግርግር ቀድሞ የሚያውቅ ግድያ እንዲፈፀም በከፍተኛ የገንዘብ ኃይል አቀናበረው  ቢባል የበለጠ ድምፀት ይሰጣል።

===================================
ጉዳያችን/Gudayachn
ሰኔ 17/2011 ዓም (ጁን 24/2019 ዓም)
========================================

አይዞሽ! ኢትዮጵያ

ሰኔ 15/2011 ዓም በባህር ዳር ከተማ የዓማራ ክልላዊ መንግስት ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር አምባቸው መኮንን እና የርዕሰ መስተዳድሩ የአረጃጀት ዘርፍ አማካሪ አቶ እዘዝ ዋሴ ተሰውተዋል።በአዲስ አበባ ደግሞ የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ጀኔራል ሰዓረ መኮንን እና ሜጀር ጀኔራል ገዛኢ አበራ መሰዋታቸውም የያዝነው ሳምንት መጨረሻ አሳዛኝ ዜና ነበር።የባህር ዳሩ ግድያ የተመራው በብርጋዴር ጀኔራል አሳምነው ፅጌ መሪነት መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ፕሬስ ሴክሬተራት አቶ ንጉሡ ጥላሁን ሰኔ 16/2011 ዓም በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል።

የደረሰው ሁሉ እጅግ የሚያሳዝን ነው።በግድያው ህይወታቸውን ያጡት ሁሉ አሟሟት የሚያሳዝን ቢሆንም የማዕከላዊ ፖለቲካን (ከአክራሪነት በራቀ መልኩ) የሚያራምዱት እና ብዙ በጎ ሕልም የነበራቸው ዶ/ር አምባቸው መኮንን እና ከዘረኘነት የፀዳ ሰራዊት መመስረት አለብን በሚል መርሃቸው የሚታወቁት በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ሳይቀር ከፍተኛ ሚና የነበራቸው የጦር ሰው ጀኔራል ሰዓረ መኮንን ላይ የተፈፀመው ግድያ ከሁሉ የከፋ በሀገር ላይ የተፈፀመ ወንጀል ነው።ኢትዮጵያ በታሪክ ሁሉን ተቃዋሚ እና የተለያየ ሃሳብ አራማጆችን አቅርባ ካለምንም ስጋት እንዲወጡ እና እንዲገቡ ፈቅዳ ባለችበት ዘመን በእዚህ ደረጃ በጥይት ወደመነጋገር ያረጀ እና ያፈጀ ዘመን የመመለስ በሽታ በራሱ ትልቅ ህመም ነው።የጀነራል ሰዓረ መኮንን ግድያ እንዴት ከባህርዳሩ ጋር ተገናኘ? የሚለው ጥያቄ አሁንም የሚጠየቅ ነው።ሁለቱን ለማያያዝ የድርጊቶች ሂደት እስካሁን አልታዩም።

 የጀነራል ሰዓረ መኮንን ግድያ ከሀገር ውስጥ ሴራ ይልቅ የውጭ እጅ ምናልባትም የባህርዳሩን ግርግር ቀድሞ የሚያውቅ ግድያ እንዲፈፀም በከፍተኛ የገንዘብ ኃይል አቀናበረው  ቢባል የበለጠ ድምፀት ይሰጣል።በእዚህ የውጭ ተንኮል ዙርያ ግን ከህወሓት ዙርያ ካሉ ሰዎች እስከ የትኛውም አክራሪ በእጅ አዙር እጁ አለበት የለበትም የሚለው ወደፊት የሚገለጥ ጉዳይ ነው።በተለይ ጄኔራሉን በመግደል ጦሩ ውስጥ የመከፋፈል ዓላማ ያለው ማንም ኃይል ይህንን ከማድረግ አይመለስም።በሌላ በኩል የዶ/ር ዓብይ አስተዳደር በእንዲህ አይነት ተግባር ተሰማርቷል እያሉ በማኅበራዊ ሚድያ ላይ ትንታኔ ለመስጠት የሚሞክሩ አስቂኞች ግን ብዙ ያልተረዱት ነገር አለ።ይሄውም ሲጀመር ጀነራል ሰዓረ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ በለውጡ ሂደት ላይ የኃይል ሚዛኑን በተለይ ከትግራይ ጋር ካለው አንፃር ሁለቱም የምከባበሩ እና አንዳቸው ለአንዳቸው አስፈላጊ መሆናቸውን በደንብ የተረዱ ናቸው።በመቀጠል ሁለቱም በወታደራዊ ዲስፕሊን ጥሩ ደረጃ ያላቸው እና በመርህ ላይ የሚያምኑ ናቸው።ስለሆነም የጀነራል ሰዓረ ሞት ከህወሓት ይልቅ ሀዘኑ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ነው። ይልቁንም ህወሓቶች ጄኔራሉን ህወሐትን እንደከዱ አድርገው በማኅበራዊ ሚድያ ሰፊ ዘመቻ የከፈቱባቸው ሳሞራን በጡረታ አስወጥተው እርሳቸው ከአቢይ ጋር ይታያሉ በሚል እንደነበር የአንድ ዓመት ትዝታ ነው።አሁን ''የፈሰሰ ውሃ አይታፈስም '' የደረሰውን ሁሉ  በሃዘን እና በቁዘማ ከማሳለፍ እኩይ ተግባሩን በራሱ ወደ በጎ ተግባር የመቀየር እና ያለፉትን አካሄዶች መለስ ብሎ የመመልከት የውዴታ ግዴታ የሚሰጥ ወቅት ላይ ነን።

ከባህርዳሩ እና ከአዲስ አበባው ግድያ በኃላ ሶስት አካላት ሶስት ነገሮችን መማር አለባቸው

በባህርዳሩ እና በአዲስ አበባው ግድያ ዙርያ ሶስት አካላት ማለትም -

  • የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ 
  • ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ እና 
  • አክራሪ ኃይሎች (hardliners) የሚከተሉትን ሶስት ነገሮች በትምህርትነት መውሰድ አለባቸው።


የኢትዮጵያ ሕዝብ

አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ አሁን በኢትዮጵያ ላይ ያለውን ለውጥ በአንክሮ የሚከታተል፣ከልዩነት ይልቅ አንድነትን የሚናፍቅ ሆኖም ግን በብሔር አክራሪ ኃይሎች ድምፅ የተሰላቸበት እና አንዳንዱ ደግሞ የተደናገረበት ሁኔታ ነው ያለው።ይህ ከቅዳሜው አደጋ በፊት የነበረ አስታሳሰብ አድርጎ መውሰድ እና ከቅዳሜው ግድያ በኃላ ሕዝብ እንደ ሕዝብ ድርጊቱ የደውል ያህል የሚወስደው መሆን አለበት።ስለሆነም ሕዝብ በዋናነት ማድረግ ያለበት ብሔራዊ አንድነት እና ሕብረት ማጠናከር ነው።የሃይማኖት፣የማኅበረሰብ እና የክልል አደረጃጀት እንዲሁም የመገናኛ ብዙሃን የበለጠ ሊያተኩሩበት የሚገባ ጉዳይ ይሄው ብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ መሆን አለበት።በመሆኑም ዝምታን የመረጡ ሁሉ በእዚሁ ጉዳይ ላይ አትኩረው ለመስራት የሚነሱበት ጊዜ አሁን ነው።

እዚህ ላይ አሁንም የብሔራዊ አንድነት እና ኢትዮጵያዊነት ላይ እንደሚያተኩሩ ደጋግመው የነገሩን ለእዚህም እየሰሩ እንደሆነ ለአንድ ዓመት ያህል የተመለከትናቸው የጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ አካሄድን ማገዝ አሁንም ያለው  ብቸኛ አማራጭ ነው።ይህ ስለ ኢትዮጵያ ሲባል የሚደረግ እንጂ ግለሰብ ከመውደድ የተነሳ የሚደረግ አይደለም።ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ያህል አሁን ያለውን የኢትዮጵያ እና የአካባቢ ሀገሮች ውስብስብ ፖለቲካ የመረዳትም ሆነ በትዕግስት የመፍታት ክህሎት እና ስብዕና ያለው መሪ ለመሆኑ የሚነሳ ጥያቄ የለም።ስለሆነም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይን በርታ! የማለት እና የማገዝ ታሪካዊ ኃላፊነት አሁንም ከኢትዮጵያ ሕዝብ ይጠበቃል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ከእዚህ በፊት ከነበረባቸው ኃላፊነት በበለጠ አሁን ባለችው ኢትዮጵያም ያለባቸው ታሪካዊ ኃላፊነት ጨምሯል።የባሕርዳሩ እና የአዲስ አበባው ግድያ በኃላ ግን የሀገሪቱ ለውጥ በቶሎ መፋጠን እንዳለበት የሚያሳይ አዲስ ምልክት የመመልከቻቸው ጊዜ አሁን እንደሆነ ሁኔታው በራሱ አመላካች ነው። በረጅም ጊዜ ይመጣሉ ያሉት የለውጥ ሂደት በተለይ ብሔራዊ አንድነትን በሁለት እና ሶስት ዓመታት በሂደት እየደመሩ የመሄድ ስልት አሁን ካለው የአክራሪ ኃይሎች የስልጣን ሙከራ አንፃር ሲታይ በፍጥነት መወሰን የሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ መድረሳቸውን የሚያሳይ ነው።ለእዚህ ደግሞ ኢህአዴግ ከአጋር ድርጅቶች ጋር የምፈጥረው ውህደት ይኖራል ያለውን ሃሳብ በጊዜ ሰሌዳ ከአሁኑ ማሳወቅ እና ቢዘገይ በነሐሴ ወር መጨረሻ ላይ ይህንን መፈፀም እና የጎሳ ፖለቲካዊ አደረጃጀትን ቢያንስ በኢህአዴግ ደረጃ ማክሰም ወቅቱ የሚጠይቀው ሁኔታ ነው።

በሌላ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ከእዚህ በፊት በከፍተኛ ሁኔታ ሲቀርብባቸው የነበረው ጥያቄ አንዱ የአክራሪ ኦነግ ቡድኖች በኦዴፓ መዋቅር ውስጥ እና በምዕራብ ወለጋ ለተፈፀሙት ስርዓት አልበኝነት ተግባሮች ያሳዩት መለሳለስ ከአሁን በኃላ መቀየር እንዳለባቸው ማሰብ አለባቸው።በተለይ በእዚህ ጉዳይ ላይ  ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልፈቱበት የፈለጉት የራሱ የሆነ መንገድ ቢኖርም በአክራሪ ኃይሎች በኩል መለሳለሱ ሌላ ትርጉም እየተሰጠው ስለሆነ አሁን ቆንጠጥ ያለ እርምጃ በአክራሪ የኦነግ ኃይሎች ላይ አጠናክረው እርምጃ እየወሰዱ መሆኑን ህዝቡ ሊረዳው በሚችለው መጠን በተግባር ማሳየታቸው በዓማራ ክልል ያለውን የአክራሪ ኃይሎች ወደ ማዕከላዊ አስተሳሰብ የመምጣት ሂደት ላይ ትልቅ አስተዋፅኦ አለው።

አክራሪ ኃይሎች (hardliners)

በየትኛውም የፖለቲካ ኃይሎች አሰላለፍ ላይ ለዘብተኛ እና አክራሪ ኃይሎች መኖራቸው የታወቀ ነው።በእዚህ አገላለጥ አክራሪ ኃይሎች (hardliners) በተለይ በኦሮምያ፣በትግራይ እና በዓማራ ስም 'ዋልታ ረገጥ' አስተሳሰብ የሚይራምዱ አደረጃጀቶች፣ኃይሎች እና አክትቪስቶችን ነው።እነኝህ አካላት መሰረታዊ የአክራሪነት መነሻቸው ሶስት ነገሮች ላይ ያጠነጠነ ነው።እነርሱም ያለፈ የተሳሳተ ትርክት፣የወደፊቱ ላይ ያላቸው ስጋት (አለመተማመን) እና ከግለሰቦቹ የግል የስልጣን እና የመታወቅ ፍላጎት የሚመነጭ ነው።ከእዚህ ሁሉ የከፋው እና አሁን መታከም ያለበት ግን የወደፊቱ ላይ ያላቸው ስጋት ወይንም አለመተማመን ትልቁን ድርሻ የሚይዝ እና አደገኛው ነው።በእዚህም ሳቢያ የማዕከላዊ ስልጣኑን በተቻለ መጠን ተፅኖ ባሳረፈ መልኩ መቆጣጠርን እንደ ብቸኛ መንገድ አድርገው ያዩታል።ሆኖም ግን ከአሁን በኃላ አንዱ በብቸኝነት የተቆጣጠረው የስልጣን አካሄድ የበለጠ ደም አፋሳሽ መሆኑን የዘነጉት ይመስላሉ።

እነኝህ አክራሪ ኃይሎች (hardliners) በጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ የለውጥ ሂደት ላይም አስቸጋሪ ጋሬጣ ሆነዋል።ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ በመሃል ሆነው የእነኝህን አክራሪ ኃይሎች ፍላጎት ለማመጣጠን በንግግራቸው እና በሹመት አሰጣጥ ላይ ሁሉ ሲቸገሩ በግልጥ ይታያል።ጠቅላይ ሚኒስትሩ በእዚህ ደረጃ ሲቸገሩ ግን ሕዝብ እና ማዕከላውያን እንዲሁም ኢትዮጵያዊነት የሚያስቀድመው አብዛኛው ሕዝብ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ደግፎ መቆም የሚገባው ለእዚህ ነው።ኢትዮጵያን ለማስቀጠል ብዙሃኑ ማዕከላዊው እና ኢትዮጵያዊነት አራማጁ ከዝምታ መንፈስ መውጣት ያለበት ለእዚህ ነው።

አክራሪ ኃይሎች (hardliners) በህወሓት፣በኦነግ - ኦዴፓ፣ በአብን እና አክትቪስቶች በኩል በተለይ ከቅዳሜው የባህር ዳር እና የአዲስ አበባ ግድያ በኃላ ቆም ብለው ማሰብ የሚገባቸው ወሳኝ ጊዜ ላይ መሆናቸውን ማወቅ አለባቸው።ምክንያቱም በአክራሪ አካሄድ አገር እንዴት በአንድ ቀን ወደለየለት ትርምስ ልትገባ ትችላለች ብሎ አለማሰብ የበዛ የራስ ወዳድነት ስሜት ነው።ለማክረር በራሱ ሀገር ያስፈልጋል።በሌለ ሀገር ምንም ነገር አይኖርም።ስለሆነም የከረረ አስተሳሰቦች ወደ መሃል የሚመጡበት መንገድ ላይ ማተኮር እና የጎሳ ፖለቲካው አደገኛ መሆኑን የዶ/ር ዓቢይ መንግስት ተገንዝቦ የማስተካከል ስራዎችን ሲሰራ ቢይናስ የመለሳለስ እና የመተማመኛ ሂደቶች ላይ ማገዝ ይጠበቅባቸዋል።በመሰረቱ የአክራሪ ኃይሎች (hardliners)  ማቆጥቆጥ በራሱ ህወሓት/ኢህአዴግ ሰራሽ እንጂ ኢትዮጵያዊ መሰረት የለውም።ስለሆነም ኢትዮጵያዊ መሰረት ሲጠናከር አክራሪ ኃይሎች (hardliners) ቦታቸው እየጠፋ ይሄዳል።ይህ ግን በሂደት እና በሥራ የሚመጣ እንጂ የማኅበራዊ መስተጋብር ሂደቶች በአንድ ሌሊት ተሰርተውም ሆነ ተደምስሰው የሚያድሩ አይደሉም።

ለማጠቃለል ኢትዮጵያ አሁንም አይዞሽ! ልንላት ይገባል።ይህ ለውጥ ሲጀመር አሁን ከምናየው በላይ ፈተናዎች ሲጠበቁ ነበር።አሁን እየገጠመ ያለው የእዚህ አካል ክፋይ ነው።የቅዳሜው የባህርዳር እና የአዲስ አበባ ክስተትም አስተማሪ ሆኖ ማለፍ አለበት።ይሄውም ሕዝብ አንድነቱን በበለጠ መጠበቅ፣ጠቅላይ ሚኒስትሩም ለበለጠ ተግባራዊ ውሳኔ የሚነሱበት፣ኢህአዴግ ከጎሳዊ ፖለቲካ ግንባርነት ወደ ውሁድ የሚቀየርበት እና አክራሪ ኃይሎች ወደ መሃል የሚመጡበት እና እራሳቸውን የሚወቅሱበት እስከሆነ ድረስ ኢትዮጵያ በተሻለ መልኩ ችግሩን ትወጣዋለች።ከእዚህ በተረፈ ግን በተለይ በኦዴፓ ውስጥ ያሉ አክራሪ ኃይሎች ከአሁን በኃላ በአጋጣሚው መንግስት ወደ ለየለት የአምባገነን ስርዓት ለመቀየር የሚያደርጉት ጥረት የበለጠ ሌላ አክራሪ ኃይል በሌላው በኩል ይፈጥር እንደሆነ እንጂ መፍትሄ አይሆንም።የዓቢይ መንገድ እና ለሁሉም አባት ለመሆን የሚያሳየውን መንግስታዊ ባህሪ የተላበሰ አካሄድ እያገዙ አክራሪ ጎሳዊ ፖለቲካን ሞርዶ ሃገራዊ ማድረግ ለአክራሪ ኃይሎች የቀረበ የመጨረሻው መጨረሻ አማራጭ ነው።ይህንን ማድረግ ካልቻሉ ግን ሳይወዱ በግድ ለብሔራዊ ጥቅም ሲባል መደረጉ አይቀርም።



ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Thursday, June 20, 2019

A Changing Ethiopia: Lessons from U.S. Diplomatic Engagement (video) በኢትዮጵያ ለውጥ ዙርያ የአሜሪካ ዲፕሎማቶች ዕይታ (ቪድዮ)

Source :  US Institute of Peace

June 5/2019 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Sunday, June 16, 2019

''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች


Picture source = Beautiful Artist (America X Reader)

ጉዳያችን / Gudayachn
ሰኔ 9/2011 ዓም ( ጁን 16/2019 ዓም)

የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የቋንቋ ዎች ጥናት ማዕከል በ1993 ዓም ባሳተመው የአማርኛ መዝገበ ቃላት ላይ አማረ የሚለውን ቃል ሲተረጉም  ተዋበ፣ቆነጀ፣ውል አለ፣አሰኘ  የሚል ትርጉም ይሰጠዋል።በሀገራችንም ''ያማረ ሁሉ አይበላም'' የሚባል የቆየ አባባል አለ።አባባሉ በዋናነት ከላይ የሚያዩት ውስጣዊ ምንነቱ ያልታወቀ ሁሉ እንደማማሩ ላይሆን ይችላል የሚል መልዕክት አለው።መፅሐፍ ቅዱስም ''ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና'' (2ኛ ቆሮ 11፣14) በማለት የሚያምር ሰይጣን ስላለ ተጠንቀቁ በማለት ያስጠነቅቃል። 

ሰይጣን ርኩስ መንፈስ እንጂ የሚዳሰስ ስጋ አይደለም።ሆኖም ግን በፍጡራን ስጋ ላይ አድሮ ክፉ ሥራ ያሰራል።በፍጡር እባብ ላይ ያደረ ሰይጣን አዳምን ሲያስት በሚያምር መልክ መከሰቱ ሌላው ማሳያ ነው። ሰይጣን ቀንድ እና ጥፍሩን ብቻ አሹሎ ሳይሆን በሚያምር ሥራ፣በሚያምር አቀራረብ፣በሽንገላ ፈገግታ፣ለሰው ልጅ የሚቆረቆሩ በሚመስሉ ሰዎች፣የሃይማኖት ሰው በሚመስሉ ሰዎች፣ለጋሾች መሆናቸው በሚታወቁ ሰዎች፣ሲናገሩ ለሰው ልጅ በጎ የሚያስቡ በሚመስሉ ሰዎች ስር ሁሉ የሰይጣን ገንዘብ የሆነ ሥራ ይሰራል።


''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች የኢትዮጵያውያን ዋነኛ ጠላቶች  ናቸው።መልካም፣የዋህ፣ለሌላው የሚያስቡ፣ቅን እና ታጋሽ ኢትዮጵያውያን ሁል ጊዜ የሚነደፉት ''በሚያምሩ'' ሰይጣኖች ነው። ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች የተነደፉ ኢትዮጵያውያን በሚደርስባቸው እና እየደረሰባቸው ያለው መንገላታት ከሚገመተው በላይ ነው።''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ተቆነጃጅተው በጎ እንደሚሰሩ መስሎ በመታየት እየነደፉ ያልነደፉ መስለው ሲቁለጨለጩ መመልከት ሌላው አስገራሚው እውነታ ነው።''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ኢትዮጵያውያን ላይ በሶስት መልክ ይከሰታሉ።በእነኝህ በሶስት መልክ  የሚከሰቱት ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በሶስት ቦታዎችም ተንሰራፍተዋል።እነርሱም : -



  • በሀገር ቤት በትናንሽ የስልጣን ወንበሮች ላይ፣
  • በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን መሐል እና 
  • በየትኛውም ቦታ የሚገኙ የእምነት ቦታዎች ነው።


''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በሀገር ቤት በትናንሽ የስልጣን ወንበሮች ላይ  


በሀገር ቤት የሚገኙ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ከወረዳ እስከ ሚኒስትር መስርያቤቶች ውስጥ በኃላፊነት ተቀምጠው ተቆነጃጅተው አደባባይ የሚታዩ ነገር ግን በውስጥ የሰይጣን ሥራ እየሰሩ የሚገኙ ናቸው።ቀድመው የለውጥ ሐዋርያ መስለው ዲስኩር ላይ ቀዳሚ ናቸው።ምናልባትም በማያውቃቸው መሐል  ሲጎማለሉ ለለውጥ የቆሙ አልያም በጎ የሕዝብ አሳቢ መስለው ይታያሉ።ውስጣቸው ግን ነጣቂዎች፣በዘር ፖለቲካ የተነከሩ፣የገንዘብ ጥማታቸውን ለማርካት ሺዎች የሚፈናቀሉበትን መንገድ ማታ ማታ ሲሸርቡ ያመሻሉ። መግደል፣ክህደት እና ሸፍጥ የውስጥ ገንዘባቸው ነው።ከላይ ስታዩ ግን ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ናቸው እና ደጎች፣በንግግራቸው የሚያፈዙ፣እራሳቸውን ለሕዝብ የሰጡ የሚባል ስም አትርፈዋል። የሚያምር ሁሉ የሚበላ የሚመስለው ምስኪን ሕዝብ ጉዳዮችን በአንክሮ ማየት ትቷል እና ማማራቸውን ብቻ እንጂ ውስጣቸው ነጣቂ ተኩላ መሆናቸውን አይረዳም።የጊዜ ጉዳይ እንጂ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች አንድ በአንድ በሕዝብ ዓይን ውስጥ የሚገቡበት እና የተቀቡት መዋብያ ተገልጦ ሰይጣንነታቸው የሚታወቅበት ጊዜ ሩቅ አይደለም።

''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን መሐል


በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የሁለት ተከታታይ ትውልድ ስደት ውጤት ናቸው።ሁለቱ ትውልዶች በሀገራዊ ጉዳይ የጋራ ርዕይ ቢኖርባቸውም በአካሄድ የተለያየ እሳቤ ሊኖራቸው ይችላል።የሚያሳዝነው ግን ከሁለቱም ትውልድ ውስጥ የማይታወቁ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በብዙሃኑ በውጭ የሚኖሩ የዋህ፣ቅን እና በጎ አሳቢዎች መሐል ሆነው ስያምሷቸው ኖረዋል።በውጭ ሀገር የሚኖሩ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ቅድምያ በጎ አድራጊ ለመምሰል ከቤተሰባቸው ጀምሮ የወሬ ዘመቻ ይከፍታሉ። ዋና መሳርያቸው የአውሮፓ እና የአሜሪካ ዋጋው የቀነሰ የስልክ ወሬ ነው።ሐሜት ጧት ፈጥረው፣ከቀትር በኃላ አሳድገው፣ምሽት ላይ ስልካቸውን ከፍተው የፈጠሩትን ሃሜት እንደ ዶሮ እንቁላል ታቅፎ የሚፈለፍልላቸው ሁነኛ ሰው ይመርጣሉ።ብዙ ጊዜ ለሀሜት መፈልፈያነት የሚመረጡ ሰዎች የዋሆች እና ቅኖች ከመሆናቸው የተነሳ የሃሜት ፈልፋይ እና አሰራጭ መሆናቸውን ላያውቁ ይችላሉ ወይንም   እያወቁ በይሉኝታ ተይዘው  በሃሜት ውጉ የተባሉትን ይወጋሉ።

በውጭ ሀገር ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በሚፈጥሩት የሃሜት ጦር ተወግተው ካሰቡት በጎ ሥራ ሁሉ እርግፍ አድርገው የተዉ ወይንም ''የሀበሻ ነገር አያሳየች'' ብለው ከማኅበራዊ ኑሮ ሁሉ እራሳቸውን አግልለው የሚኖሩ በጣም ብዙ ኢትዮጵያውያን አሉ። ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በቁጥር በጣም በጣም ጥቂት ናቸው። ነገር ግን በጣት የሚቆጠሩ ሆነው ብዙ ሺዎችን የማመስ አቅም አላቸው።ምክንያቱም አይታወቁማ! እነርሱ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ስለሆኑ የሚታየው የተቆነጃጀው ማንነታቸው እንጂ ሰይጣናዊ የሃሜት ጦራቸውን የሚያውቅ የለም። በውጭ ሀገር ባሉ ማኅበራዊ ድርጅቶች፣የህዝብ የእርስ በርስ ግንኙነት ሁሉ የሚበጠበጠው በእነኝህ እጅግ ጥቂት በሆኑ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች መሆኑን የሚረዳ እጅግ ጥቂት ነው።ይህ የሚያውቀውም  ልናገር ቢል የሚሰማው የለም።''የሚያምር'' ሰይጣን የሚታወቁበት ጊዜ እንደደረሰ ሲረዱ በጎ ስራዎችን ይጨምራሉ።የበለጠ ይቆነጃጃሉ።የእዚህ ጊዜ ሕዝብ ከንፈሩን እየመጠጠ ያሞግሳቸዋል።

በውጭ ሀገር ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ላለፉት ሃያ ሰባት አመታት በቀድሞው ኢህአዴግ/ህወሓት መዋቅር ውስጥ በጥቅም እየተያዙ ዲያስፖራውን ለመበጥበጥ እና የእርስ በርስ ግንኙነቱን ለማላላት እና እንዳይቃወም ለማድረግ ተጠቅሞበታል።በአንድ ብዙ ኢትዮያውያን የሚኖሩበት የውጭ ሀገር  ከተማ ውስጥ ''የሚያር'' ሰይጣን ከተገኘ (ከተገኘች) በከተማው ውስጥ የቀድሞውን መንግስት ይቃወማሉ የተባሉ ሰዎችን በወዳጅነት ቀርበው፣ በፈገግታ እየሸነገሉ ከጀርባ ግን በፈጠራ ወሬ እንዲያሙ ተልኮ ይሰጣቸዋል።''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ናቸው እና እነርሱ ይታመናሉ።

''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ሁል ጊዜ አሸናፊ አይደሉም።ማንም የማይከታተላቸው እና የማያውቃቸው ይመስላቸዋል።በውጭ ሀገር ከሀገር ቤት ጀምሮ የምታውቁት ወዳጅ፣ከቤተሰብ ጀምሮ የምያውቃችሁ አሳቢ፣ የቅርብ ዘመድ ይሆንና ከእናንተ መሃል ሌላው ሰው ከጥንት የምታውቁት ወይንም የቅርብ ዘመዳችሁ መሆኑን በማያውቅበት ሁኔታ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ለራሳችሁ ወዳጅ፣ወይንም ዘመድ ሲያማችሁ እና ብዙ እርቀት የተንኮል ሥራ ሲሰራ የእየቀን እኩይ ተግባር እጃችሁ ላይ ይወድቃል።በሀገር ቤት በአንዳንድ መስርያ ቤቶች ውስጥ ፀሐፊዎች የዋና ሥራ አስኪያጁ ዘመድ መሆኗን ሳያውቅ በሃሜት  የተጠመደ ሰራተኛ አይነት ውሰዱት።

''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በዕምነት ቦታዎች 

''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በተለይ በዕምነት ቦታዎች ውስጥ  ተቀባብተው ሲገቡ ምዕመኑን እርስ በርሱ እንዳይፋቀር፣እንዳይተሳሰብ እና ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ነጥለው የሃሜት ሸክማቸውን ያራገፉባቸው ሁሉ የተጫኑት ውሸት እውነት ስለሚመስላቸው ''የሚያምሩት'' ሰይጣኖች በእውነትም የሚያምሩ ናቸው ብለው ስለሚያምኑ ብዙዎች ከአገልግሎት፣ሌላውን ከመርዳት እና ከቅን ሥራ ሁሉ ''በሚያምሩ'' ሰይጣኖች እየተወጉ እያዘኑ ከእምነታቸው ይርቃሉ አልያም እያዘኑ ለሚያምኑት አምላክ ያመለክታሉ።''የሚያምኑት'' ሰይጣኖች ግን የወጉትን እያዩ በፈገግታ እየሸነገሉ ምንም እንዳላደረጉ ይታያሉ።


''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በእምነት ቦታዎች የዋሃንን ሲወጉ ከእራሳቸው በቀር የገዛ ቤተሰባቸው፣ልጆቻቸው እና የትዳር አጋሮቻቸው ሁሉ እንዳያውቁ አድርገው ነው። በቤተሰባቸው መሃል ሁሌም ቅኖች ሆነው ለመታየት ከፍተኛ የፕሮፓጋንዳ ሥራ ይሰራሉ።በመቀጠል በቤተሰባቸው መሃል በዘሩት የሐሰት ወሬ የሚወጉትን ሰው እንዲጠላ አዲስ ትርክት ይፈጥሩለታል።ትርክቱ በዙርያቸው ለሚገኙ የቅርብ ዘመዶች፣አንደኛ ደረጃ ቤተሰቦች፣የቅርብ ወዳጆች እና የአገልግሎት ክፍሎች ውስጥ ለይተው ይመቹኛል ባሏቸው ሰዎች ሁሉ መርጠው የመርዛማ የጥላቻ ዘመቻቸው አካል እንዲሆኑ በከፍተኛ ደረጃ የአካል፣የስልክ እና የጥቅም መደለል ሥራ ሁሉ ይሰራሉ።በተለይ በስልክ ዘመቻቸው ወቅት የገዛ ቤተሰብ በማይሰማበት ጊዜ ይመርጣሉ። ከእዚህ ሁሉ በኃላ በሐሰት የወጉትን ሲመለከቱ  በሽንገላ ፈገግታ እየተመለከቱ መርካታቸውን ከፊታቸው መደበቅ ያቅታቸዋል።በእዚህ ሳብያ ብዙ ሰው ከእምነቱ እንዲርቅ፣ሰው እንዲጠላ እና ሰው ሁሉ ክፉ ነው ብሎ እንዲያስብ ያደርጉታል።ምክንያቱም ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች መጀመርያ ሥራ የሚጀምሩት ሊያጠቁ በፈለጉት ሰው ዙርያ ነው።በዙርያው (ዋ) ያሉትን ሰዎች በስልክ የፈጠራ ሀሜት ከምዘብዘብ የሰሙትን በጎ መረጃ ሁሉ አጣመው ትንታኔ በመስጠት የዋሆችን ይወጋሉ።በእርግጥ ማንኛውም ሥራ በሥራ ልምድ እንደሚዳብር ሁሉ ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች እየቆዩ ሲሄዱ በልምድ እየተካኑ ስለሚሄዱ ካህኑን ከምዕመኑ፣ ሸሁን ከሙስሊሙ ለመለየት አንዲት ጫፍ ፈልገው አስፍተው በመንገር ዱላ እስከማማዘዝ የመድረስ ልምድ አላቸው። ይህ ሁሉ ሲሆን ግን ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች የሚሰሩት ሁሉ ትክክል እንደሆነ እራሳቸውን ለማሳመን ምክንያት ይሰጡታል።ምክንያታቸው ግን ሕሊናን የማሸነፍ አቅም ስለሌለው ውስጣቸው እራሳቸውን መውቀሱን አያቆምም።

በእምነት ቦታዎች የሚታዩት ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች አንዱ አስገራሚ ድርጊታቸው ቀድመው የተበደሉ መስለው ማጮህ ነው። ቀድመው የተበደሉ መስለው መታየት አንዱ የመቆነጃጀች ዘዴ ነው።ቀድሞ መጮህ ''ጥሩ የሚያምር'' ሰይጣን ለመሆን ይመቻል።ቀድመው ከጮሁ በኃላ የስልክ እና የአካል ሃሜታቸውን ለመርጨት ይመቻል።ምክንያቱም ከንፈሩን እየመጠጠ የሚሰማ ያገኛሉ።በሌላ በኩል ደግሞ አመቺ የመሰላቸው ጊዜ  በጣም ግልጥ የሆኑ ለመምሰል በመነጋገር የሚያምኑ ሁሉ መስሎ በመቅረብ ለእየብቻ እያሙ ያቆሰሏቸው  ሰዎች እስኪገረሙ ድረስ በግልጥ የሚያወሩ መስለው ይታያሉ።ይህ ሌላው አስገራሚ ''የሚያምሩ'' ሰይጣን ገፅታቸው ነው።

ለማጠቃለል

 ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች የኢትዮጵያውያን የማኅበራዊ ችግር አንዱ እና ዋነኛው እየሆነ መጥቷል። በውጭ ሃገራት በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን መሃል ያደረሱት ጉዳት ቀላል አይደለም።በመጀመርያ ደረጃ የህዝቡን የእርስ በርስ ግንኙነት አበላሽተዋል።በሁለተኛ ደረጃ ማኅበራዊ ድርጅቶች አቅመ ቢስ እንዲሆኑ አድርገዋል።በሶስተኛ ደረጃ ብዙ አቅም ያላቸው ሀገር ወዳድ፣በጎ አሳቢ እና ቅን ኢትዮጵያውያን በራሳቸው በወገናቸው እንዲመረሩ እና በጅምላ ኢትዮጵያውያንን እንዲሸሹ አድርገዋል።''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ሌት ተቀን በስልክ እና በአካል የወረወሩባቸው የውሸት ጦር ስለሚዘገንናቸው ከእዚህ ሁሉ ጊዜ እና ፈጣሪ ይፍረድባቸው ብለው ተቀምጠዋል።ይህ ደግሞ ኢትዮጵያን እንደሀገር ኢትዮጵያውያንን እንደ ማኅበረሰብ ጎድቷቸዋል።

ለእዚህ ሁሉ መፍትሄው ግን ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች የሚለዩበትን ዋና መለያ ሃሜት ቀድሞ አውቆ ያላቸውን የተለየ ሃሳብ ለባለቤቱ እንዲነግሩ ነግሮ የወሬ ጊዜ ማሳጠር ነው። ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች በውለታ የገዟቸው አልያም በዝምድና ፍሬ የሌለው ''ወሬ'' በስልክ በማውራት የምያደክሟቸው ሁሉ ለመልካም የአዕምሮ ጤንነታቸው ማሰብ እና ''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ወደ በጎ ህሊና እንዲመለሱ ሲሆን በመምከር ካልሆነ መከራ እስኪመክር  በትዕግስት በመጠበቅ ለሰው ሁሉ በጎ ህሊና በመያዝ መኖር አለባቸው።''የሚያምሩ'' ሰይጣኖች ወደ ሰዋዊ ልቦናቸው ካልተመለሱ ክፋታቸው መገለጡ  የማይቀር ነው።ሕዝብ ግን መታወክ የለበትም።

ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

Monday, June 10, 2019

ከሠላሳ በላይ የዩንቨርስቲ መመረቂያ ፅሁፍ የተሰራበት የራያ ማኅበረሰብ ላይ ያተኮረ አዲስ ልዩ ውይይት (ቪድዮ)

ቪድዮ ምንጭ = አንዳፍታ (ጋዜጠኛ ስዩም ተሾመ) 


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Friday, June 7, 2019

የቶቶ ግብረ ሰዶማውያን በላልይበላ ሊያደርጉት ያሰቡት ጉዞ አፍሪካን ለመተንኮስ የታሰበ ነው።

የቅዱስ ላልይበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት 

ጉዳያችን/ Gudayachn
ሰኔ 2/2011 ዓም (ሰኔ 8/2019 ዓም)

ግንቦት 29/2011 ዓም ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል በለቀቀው ዜና እንዲህ ይነበባል: - 


ግብረ ሰዶማውያን በኢትዮጵያ ለማድረግ ያቀዱትን የቅዱስ ላሊበላ ገዳም ተቃወመው ።
የግብረ ሶዶማውያን አስጎብኝ ማኅበር በኢትዮጵያ ሊያደርግ ያቀደውን የጉብኝት መርሀ-ግብር እንደማይቀበለው የቅዱስ ላልይበላ ገዳም አስታወቀ፡፡
መቀመጫውን በአሜሪካ ያደረገው ‹ቶቶ› የተባለ የግብረ ሶዶማውያን አስጎብኝ ድርጅት በቀጣዩ ጥቅምት ወር 2012 ዓ.ም በኢትዮጵያ ጉብኝት እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡ ጉብኝት ከሚያደርግባቸው ቦታዎች መካከል የቅዱስ ላልይበላ ገዳም አንዱ ነው፡፡ ድርጅቱ በማኅበራዊ ሚዲያ የፊት ገጹ ላይ የቤተ ጊዮርጊስን ፎቶ በመለጠፍ ‹‹ላልይበላ እንገናኝ›› የሚል መልዕክት አስፍሯል፡፡
የአካባቢው ማኅበረሰብ እና የገዳሙ አስተዳዳሪ አባ ጽጌ ሥላሴ መዝገቡ ዕቅዱን ከተመለከቱ በኋላ የተሰማቸውን ሐዘን ገልጸዋል፡፡ አባ ጽጌ ሥላሴ እንደተናገሩት ግብረ ሶዶማዊነት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የተወገዘ እና ከተፈጥሮ የወጣ ተግባር ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም ‹‹ወንድ ከወንድ ሴት ከሴት ጋር ግንኙነት ቢያደርግ የተረገመ ይሁን፤ ከሃይማኖቱ ማኅበርም ይለይ›› በማለት እንደሚያስቀምጥ አስረድተዋል፡፡ በመሆኑም ጉብኝቱ ተገቢ እንዳልሆነና እንደማይደግፉት አባ ጽጌ ሥላሴ መዝገቡ ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያውያን ባሕል፣ እሴት እና ወግም ቢሆን ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው ድርጊት ነው፡፡ የሀገሪቱ ሕግም ቢሆን ድርጊቱን በወንጀል አስቀምጦታል፡፡
በመሆኑም አስጎብኝ ድርጅቱ ቢቻል ወደ ሀገሪቱ እንዳይገባ የሚመለከተው አካል መከላከል እንዲችል፤ ካልሆነ ግን ወደ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንዲገባ የማይፈቀድለት መሆኑን እንዲያውቅ አባ ጽጌ ሥላሴ አስታውቀዋል፡፡ ይህንን ተላልፎ ቢመጣ ለሚፈጠረው ሁከት እና ግጭት ቤተክርስቲያኒቱም ሆነች የአካባቢው ምዕመን ኃላፊነቱን እንደማይወስዱም አስታውቀዋል፡፡ ‹‹ይህንን አስመልክቶ እኛ አቋማችንን በደብዳቤ አሳውቀናል›› ብለዋል፡፡
የቱሪስት ወደ ሀገሪቱ መምጣት ለአስጎብኝ ድርጅቶች፣ ለሆቴሎች፣ ለቤተ ክርስቲያኒቱም ሆነ ለሀገሪቱ የሚሰጠው ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ከፍተኛ እንደሆነ እንደሚረዱ ያስወቁት የገዳሙ አስተዳዳሪ ‹‹ማንነታቸውን በግልጽ አሳውቀው በቡድን መምጣታቸው በማንኛውም መንገድ ተቀባይነት አይኖረውም›› ብለዋል፡፡
ጉዳዩን አስመልክቶ መንግሥት አቋሙን በአጭር ጊዜ እንዲያሳዉቅ ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት የጎንደር ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናት ኅብረት ጠይቋል፡፡ የግብረ ሰዶማውያን የኢትዮጵያ ጉብኝት መርሀ-ግብር ከሃይማኖት፣ ከሕግ፣ ከሞራል እና ከሀገሪቱ ባሕል ጋር የሚጻረር ስለሆነ መርሀ-ግብሩ እዉን የሚሆን ከሆነ ለሚፈጠረዉ ማንኛዉም ችግር መንግሥት ኃላፊነቱን እንደሚወስድም አስታውቋል፡፡
ኅብረቱ ለኢፌዴሪ ባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በጻፈዉ ደብዳቤ ‹ቶቶ› የተባለዉ አስጎብኚ ድርጅት ሊጎበኛቸው ካሰባቸው ቦታዎች መካከል ታሪካዊቷ ጎንደር እና በዉስጧ የሚገኙ ጥንታዊ አድባራትም ተጠቅሰዋል፡'' ይላል።የዜናው መጨረሻ ።

ላልይበላ ለምን?
ከላይ በዜናው ላይ እንደተጠቀሰው ቶቶ የተሰኘው የግብረ ሰዶማውያን ድርጅት ''ላልይበላ (ላሊበላ) እንገናኝ'' በሚል ለመጪው ጥቅምት /2012 ዓም ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት ማሰባቸው ከፍተኛ ተቃውሞ እያስተናገደ ነው።ይህ ጉዳይ በጠበቀ የሃይማኖት መሰረት ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያን ኢላማ ያደረገበት ዋና ምክንያት ኢትዮጵያን የመተንኮስ ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ ተደርቦ አፍሪካ ላይ ያለመ ተግባር ነው። በአፍሪካ ውስጥ ካሉት ሀገሮች ውስጥ በግልፅ ግብረ ሰዶማዊነት በሕግ የታገደባቸው ሀገሮች 33  ደርሰዋል።በመካከለኛው ምስራቅ ደግሞ  አስር ሀገሮች በሕግ ግብረ ሰዶማዊነትን መፈፀም በወንጀል እንደሚያስቀጣ ደንግገዋል።በሌላ በኩል የግብረ ሰዶማዊነትን ተግባር አጥብቀው ከሚቃወሙት  ሃገራት ውስጥ ሩስያ ተጠቃሽ ነች። ሩስያ በጉዳዩ ላይ ጥብቅ ሕግ ከማውጣቷ በላይ ፕሬዝዳንቱ በተደጋጋሚ ጉዳዩ የምዕራቡ ዓለም ትንኮሳ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የግብረ ሰዶማውያኑ ድርጅት ከኢትየጵያ ቅዱሳን ቦታዎች ውስጥ አንዱ የቅዱስ ላልይበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ለመገናኘት ቀጠሮ የያዙበት ዋናው ምክንያት ኢትዮጵያ ለአፍሪካውያን ያላትን ቦታ ተጠቅሞ በኢትዮጵያ ተሻግሮ አፍሪካን መተንኮስ ነው።በእዚህ አጋጣሚ ጉዞው ከተሳካ በኢትዮጵያ ያደረጉትን ጉዞ ትልቅ የሚድያ ሽፋን በማሰጠት የቀረው አፍሪካን የመተንኮስ እና በምሳሌነት ለማስያዝ ያለመ ነው።ጉዳዩ በአንዲት ሀገር ፣ሕዝብ እና የከበረ ዕምነት ላይ የተቃጣ ጥቃት ነው።ጉዳዩ የሃይማኖት ብቻ አይደለም፣ጉዳዩ የባህል እና የሞራል ጉዳይ  ብቻ አይደለም።ጉዳዩ ከእነዚህ ሁሉ በላይ ፖለቲካዊ ዓላማ አለው።ይህ እንስሳት ያማይፈፅሙት ከዘመናት በፊት ምድራችን የተቀጣችበት እኩይ ተግባር ዛሬ በእዚህ ትውልድ ጊዜ መታሰቡ በራሱ አሳዛኝ ነው። 

መጽሐፍ ቅዱስ ግብረ ሰዶማዊ ተግባር ኃጥአት እንደሆነ ይነግረናል (ኦሪት ዘፍጥረት 19፤1-13፣ ኦሪት ዘሌዋውያን 18፤22፣ ወደ ሮሜ ሰዎች 1፤26-27፣ 1ኛ ቆሮንቶስ 6፤9)፡፡ በተለይ ሮሜ 1፡26-27 ግብረሰዶማዊነት እግዚአብሔርን የመካድና ያለመታዘዝ ውጤት እንደሆነ ያስተምረናል፡፡ ሰዎች በኃጢአትና በአለማመን በሚቀጥሉበት ጊዜ እግዚአብሔር ከእርሱ የተለየ የከንቱነትንና የተስፋ-ቢስነትን ህይወት ለማሳየት አብዝቶ ለከፋ እና ነውር “አሳልፎ ይሰጣቸዋል”፡፡ 1ኛ ቆሮንቶስ 6፤9 ግብረ-ሰዶምን የሚያደርጉ “ዓመፀኞች” የእግዚአብሔርን መንግሥት እንደማይወርሱም ይነግረናል፡፡ይህ ግልጥ ሃይማኖታዊ ትዕዛዝ ነው።

ይህ የኢትዮጵያን ዕምነት፣ባህል እና ታሪክ ያላገናዘበ ጉብኝት በራሱ ጠብ ጫሪ ከመሆኑ የተነሳ መንግስት በግብረ ሰዶማውያን ዙርይ ወሳኝ የሆነ ውሳኔ ማሳለፍ እንዳለበትም አመላካች ነው። አሁን ባለበት ሁኔታ ከህዝብ ዘንድ የተነሳው ከፍተኛ ቁጣ  አንፃር ምን ሊፈጠር እንደሚችል አይታወቅም። ስለሆነም መንግስት መጪውን ዘመን ያገናዘበ  አሰራር ከአሁኑ መቀየስ አለበት።ጉዳዩ በኢትዮጵያ ሕዝብ ስነ ልቦን፣እምነት እና ስልጣኔ ላይ ሁሉ የተቃጣ ሙከራ ነው።በመሆኑም መንግስት በማያወላዳ መልኩ በጉዞው ለሚሳተፉ የመግብያ ፈቃድ በመከልከል እና ተያያዥ የሕግ ማዕቀፎችን ማውጣት አለበት።የእዚህ አይነቱ እርምጃ መውሰድ ሕዝብ በራሱ ተደራጅቶ በግብረ ሰዶማውያን ላይ ሕዝብ በብስጭት  ለሚወስዳቸው እርምጃዎች ሁሉ ሌላ የፀጥታ ችግር እንዳይሆን የሚረዳ እርምጃ ይሆናል።  

በመጨረሻም ቅዱስ ሲኖዶስን ጨምሮ በኢትዮጵያ ያሉ መንፈሳዊ ማኅበራት ኅብረት ጭምር የግብረ ሰዶማውያንን ጉዞ ከማውገዝ አልፈው ለሚመለከተው የመንግስት አካልም ማሳሰብያ መላካቸው ጉዳዩ ከፍተኛ ትኩረት እንዲሰጠው የሚያመላክት ሌላው አመላካች ጉዳይ ነው።የግብረ ሰዶማውያን ጉዳይ በቀጣይ ዓመታትም ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ፣ሕዝብ እና የሃይማኖት አካላት  ጭምር የሚገጥማቸው ከግብረ ሰዶማውያኑ  ስብስብ ብቻ ሳይሆን ግብሩን ባፀደቁላቸው መንግስታቶቻቸው መዋቅር ውስጥ እየገቡ በሌሎች ሀገሮች ላይ ግብሩን ለመጫን የሚያደርጉት ጥረት ከፍተኛ የቁጣ መልስ ከአፍርካውያንም ሆነ ከእስያ መንግሥታት ገጥሟቸዋል።ኢትዮጵያም ካላት ታሪካዊ ኃላፊነትም አንፃር ይህንን ከሃይማኖት፣ከባህል እና ከሰዋዊ ሞራል ጋር ሁሉ የሚቃረን ተግባርን በቀዳሚነት መቃወም አለባት። በተለይ ጉዳዩ ወደ አፍሪካ ሲመጣ  የአፍሪካውያንን እጅ ለመጠምዘዝ የማድረጉ ሙከራ በቀጣይ ጊዜያትም የሚሞከር ሊሆን ይችላል። ስለሆነም ሕዝብ በዕምነቱ እና በሰውነቱ ላይ በጠላትነት የተነሳበት የግብረ ሰዶማውያን ተግባር በኢትዮጵያ እስከመቼውም አለመቀበል እና ይልቁንም ዓለም አቀፍ ፀረ ግብረ ሰዶማውያን እንቅስቃሴን ኢትዮጵያ መቀላቀል እና ማስተባበር  እስከመጨረሻውም መታገል ይገባታል።ይህ ደግሞ በሥጋዊውም ሆነ ነነፍሳዊ ሕይወት ሁሉ ታላቅ በረከት ነው። 

ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com