ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, May 22, 2023

መንግስት ከዲፕሎማሲያዊ መፋዘዝ ይውጣ! የአረብ ሊግ በአባይ ግድብ አንጻር የወሰነውን የጸብጫሪነት ተግባር በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የምላሽ መግለጫ ብቻ የሚበቃ ሊሆን አይገባም።መንግስት ያልሰራው ግዙፍ ስራ ኢትዮጵያን ለአደጋ እንዳያጋልጣት ያሰጋል።

የኢትዮጵያ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ዋና መስሪያቤት

  • መንግስት በፍጥነት ሊሰራቸው የሚገቡት አምስት ወሳኝ ዲፕሎማሲያዊ ተግባራት
=========
ጉዳያችን አለርት
=========

የአረብሊግ አንዱ የሚታወቅበት መለያው እንደባዶ ቆርቆሮ ብዙ መጮህ እና ትንሽ ማድረግ ነው።በፍልስጤም እስራኤል ግጭት፣በሊብያ፣የመን እና ሶርያ መንግስታት መፍረስ ላይ ሁሉ ብዙ በመጮህ የሚታወቀው የአረብሊግ ነገር ግን አንድ የጋራ ሰላም አስከባሪ ልኮ በጋራ የቀጠናውን ችግር ሲፈታ አልታየም። ሰሞኑን በሱዳን ጉዳይ ላይም ስብሰባ ተቀምጦ ብዙ ንግግር ሰምቷል። የአረብ ሊግ በውስጡ የተለያየ የመከፋፈል ስንጥቆች ስላሉት በስሜት የአካፋ ያህል የሚናገረውን አንዲት ማንኪያ ያህል የማድረግ ልማድ እንደሌለው ብዙዎች በድርጅቱ ላይ የሚሰጡት ምስክርነት ነው።

ሊጉ በኢትዮጵያ የአባይ ግድብ አንጻር በግብጽ አነሳሽነት አማካይነት ያሳየው ድፍረት ግን እንዲሁ በቀላል የሚታይ አይደለም። የግብጹ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር  ሳማህ ሃሰን ሸሪክ የአባይ ጉዳይ በአረብ ሊግ እያንዳንዱ መደበኛ ስብሰባ ላይ ቋሚ አጀንዳ እንዲሆን አስደርገዋል።የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የረጅም ጊዜ የዲፕሎማሲ ልምድ ያላቸው ግለሰብ ናቸው።የዛሬ ሦስት ዓመት ጉዳያችን ስለግለሰቡ ማንነት የጻፈችውን በእዚህ ሊንክ ላይ ያንብቡ።

የአረብ ሊግ መደበኛ ስብሰባውን ባደረገ ቁጥር የአባይ ግድብ ጉዳይን እያነሳ መፈትፈቱን የኢትዮጵያ መንግስት እንደዋዛ ሊመለከተው አይገባም። ባሕር ተሻግረው የኢትዮጵያ ወንዞች ጉዳይ ይመለከተናል የመካከለኛ ምስራቅ ጉዳይ ነው የሚለው የአረብ ሊግ የድፍረት ድፍረት ወሳኝ የሆነ አጸፋዊ የዲፕሎማሲያዊ ምት ይፈልጋል። ለእዚህ ደግሞ ኢትዮጵያ አቅሙም ሆነ ብቃቱ አላት። ነገር ግን ጉዳዩን እንዴት ማስተናገድ እንዳለባት መንግስት የተረዳ አይመስልም። የአረብ ሊግ በኢትዮጵያ የውስጥ ወንዝ ጉዳይ ላይ ውሳኔ ማሳለፉ የሰሞኑ ዜና ነው። የኢትዮጵያ መንግስትም ዛሬ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል መግለጫ አውጥቷል። ከመግለጫው በላይ ግን ከዲፕሎማሲያዊ መፋዘዝ ወጥቶ መንግስት በፍጥነት ሊሰራቸው የሚገቡ አምስት ተግባራት አሉ።


የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ለአረብ ሊግ ውሳኔ ዛሬ የሰጠው ምላሽ

መንግስት በፍጥነት ሊሰራቸው የሚገቡት አምስት ወሳኝ ዲፕሎማሲያዊ ተግባራት:

1/ የአፍሪካ ሀገሮችን የውሳኔው አደገኛነት እንዲገባቸው ማድረግ፣ ጉዳዩን ወደ አፍሪካ ሕብረት መርቶ ተጻራሪ መግለጫ ማሰጠት እና የዲፕሎማሲ ጉዞ ወደ አፍሪካ ሀገሮች መላክ።በእዚህ አንጻር የሚከተሉት ተግባራት መንግስት መከወን ይችላል።
  • የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ልዩ መልዕክት የያዘ ደብዳቤ ለአፍሪካ ሀገራት የሚያደርስ ከፍተኛ ልዑክ መላክ እና የአረብ ሊግ ጣልቃ ገብነትን ኢትዮጵያ ፈጽሞ የማትቀበለው ብቻ ሳይሆን በአፍሪካውያን ላይ የተቃጣ የቅኝ ግዛታዊ መንፈስ መያዙን ማሳየት፣
  • ለአፍሪካ ቀንድ ቀጣይ የጸጥታ ስጋት መሆኑን በሚገባ ማስረዳት፣
  • የአፍሪካውያን ጉዳይ በራሳቸው በአፍሪካውያን በግብጽ እና ኢትዮጵያ መካከል የሚታይ እንጂ የሌሎች ጣልቃ ገብነትን እንደማይቀበሉ የአፍሪካ ሀገሮችን ማግባባት እና ይህንኑ እንዲገልጹ ሰፊ ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ማቀጣጠል፣
  • የአፍሪካ ሕብረት የአረብ ሊግን ውሳኔ እንዲቃወም ኢትዮጵያ ከፍተኛ ተጽዕኖዋን በድርጅቱ ላይ ማሳየት አለባት፣
  • ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መቀመጫ እንደመሆኗ መጠን የአፍሪካ ሕብረት ላይ በእዚህ ጉዳይ ከፍተኛ ተጽዕኖዋን ማሳየት አለባት። በሕብረቱ ስብሰባዎች ላይ የአረብ ሊግ የአፍሪካን ሉአላዊነት መዳፈሩን ደጋግማ መንገር አለባት።በመቀጠልም ኅብረቱ የአረብ ሊግን ውሳኔ በሌላ ውሳኔ እስኪሽር ድረስ ዲፕሎማሲዋን አጠናክራ መቀጠል አለባት።
2/ ኢትዮጵያ የአረብ ሊግን አካሄድ ለተመድ፣ የአውሮፓ፣የአሜሪካ፣ቻይና፣እስራኤልና ሩስያ መንግስታት እንዲቃወሙት የዲፕሎማሲ ዘመቻ ማጠናከር አለባት።
  • በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተላከ ልዩ መልዕክት ለሀገራቱ  እና ለተመድ ዋና ጸሐፊ በልዩ ልዑክ ተልኮ መስጠት እና ጉዳዩ የሉአላዊነት ጉዳይ መሆኑን ማስረዳት እና ሀገራት አቋም እንዲወስዱ መወትወት፣
  • አሁን በመካከለኛው ምሥራቅ አንጻር ያሉትን የሀገራቱን አሰላለፍ ተመልክቶ በበቂ ሁኔታ አስልቶ መንቀሳቀስ
3/ የአረብ ሊግ አባል ሀገር የሆኑ ጎረቤቶቻችን ጂቡቲ፣ሱማሊያና ሱዳን የድርጅቱን ውሳኔ በብርቱ እንዲቃወሙ የጠነከረ ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ማድረግ፣ ያሉትን የተጽዕኖ መንገዶች ሁሉ መጠቀም እና

4/ የአረብ ሊግ ውሳኔ ምን ያህል የኢትዮጵያን ሉአላዊነት የተጻረረ እንደሆነ ለኢትዮጵያ ህዝብ በሚገባ መግለጽ።
  • አስገራሚው ጉዳይ የአረብ ሊግ ውሳኔ በሚገባም የምሬት አቀራረብ የመንግስት መገናኛዎች ለኢትዮጵያ ህዝብ አልነገሩትም። ይህ መታረም ያለበት ነው።
  • የመንግስትም ሆኑ የግል መገናኛ ብዙሃን በሚገባ ጉዳዩ ምን ያህል የሉዓላዊነት ጥሰት እንደሆነ መግለጽ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጣውን እንዲገልጽ ሊደረግ ይገባል። ይህ በራሱ የዲፕሎማሲው አንዱ አካል ነው።
5/ የአረብ ሊግን ውሳኔ በመቃወም ኢትዮጵያውያን ዲያስፖራዎች በውጭ ሃገር አጠቃላይ የተቃውሞ ሰልፍ በመላው ዓለም ሊያደርጉ እና ለሚመለከታቸው ዓለም አቀፍ ድርጅቶችም ሆነ መንግስታት ማሳወቅ አለባቸው። በተመሳሳይ በሀገር ውስጥም ኢትዮጵያውያን አደባባይ ወጥተው ሊቃወሙትና የሉዐላዊነቱን አደጋ በሀገር ውስጥ ያለው ህዝብ በሚገባ እንዲረዳው መደረግ አለበት።

ባጠቃላይ የአረብ ሊግ ውሳኔ ኢትዮጵያ በብርቱ ልትቃወመው እና በቀላሉ ልታየው የሚገባ ጉዳይ አይደለም። ከመካከለኛው ምስራቅ ጋር ኢትዮጵያ ባላት ስልታዊ አቀማመጥ ብቻ ሳይሆን ባላት የህዝብ ብዛት እና ታሪካዊ ሃይማኖታዊ ዳራ ሳይቀር ኢትዮጵያን ለማጥፋት የሚፈልጉ አንዳንድ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች ኢትዮጵያ በአባይ ግድብ አንጻር የምታደርገውን መንሰራራት እንደ የራሳቸው ስጋት አያዩትም ማለት ሞኝነት ነው። ኢትዮጵያን ለማጥቃት ደግሞ እንደ አንድ ምክንያት ሊጠቀሙበት የሚፈልጉት በማይመለከታቸው የአባይ ጉዳይ እጃቸውን ለመንከር እንዳሰፈሰፉ በሚገባ እያሳዩን ነው። በቀጣይ ዓመታት የሚኖረው የዓለማችን የኃይል አሰላልፍ ደግሞ የአካባቢ ጉልበተኞች በአካባቢያቸው ያሉ ደካማ ሀገሮች የመውረር ስልት እንደሚይዝና የዓለምም የጸጥታ ስጋት እንደሚሆን የሚናገሩ ቀላል አይደሉም። ከመካከለኛው ሀገሮች ጋር ግብጽ የገባችው የወታደራዊ ስምምነቶች ደግሞ በአረብ ሊግ ስም አንዳንድ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች ኢትዮጵያን በወታደራዊ ኃይልም ጭምር ለማጥቃት አይቃዡም ማለት አይቻልም። ስለሆነም የኢትዮጵያ መንግስት የአረብ ሊግን ውሳኔ ከመግለጫ ባለፈ በጠነከረ የዲፕሎማሲ ምት መመለስና አስተማሪ እንዲሆን የማድረግ ስራውን ከላይ በተጠቀሱት አምስት መንገዶች ቢከውን ጠቃሚ ነው። ጉዳዩ ለኢትዮጵያ ህዝብ በሚገባ ጎልቶ ያልተገለጸበት ምክንያትና ዲፕሎማሲውን በሚገባ አድምቶ እንዳይሰራ በራሱ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ያዘናጉት ካሉም እራሱን ይፈትሽ። ጉዳዩ ግን በምንም መለኪያ አደገኛ የሉዐላዊነት ድፍረት ነው።

======================///////==================

Saturday, May 20, 2023

ጎሳንና የፖለቲካ ተጽዕኖን መሰረት ያደረገ የጵጵስና ሹመት በመስጠት ቤተክርስቲያን የሲሞን መሰሪን መንገድ አትከተልም።

  • ቤተክርስቲያን ጳጳሳትን የምትሾመው የፖለቲካው አውድ እንዲፈነጥዝ ወይንም ይህኛው ጎሳ ደስ እንዲለው ሌላው እንዲከፋው አይደለም።
=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

ሲሞን በሰማርያ ይኖር የነበረ አስማተኛ ሰው ነበር፡፡ ሕዝቡም የሚያደረገውን ምትሐት እያዩ ይከተሉት ነበር በኋላ ግን በፊልጶስ ትምህርት አምነው ሲጠመቁ እሱም ተጠመቀ፡፡ በኢየሩሳሌም የነበሩ ሐዋርያት በሰማርያ ያሉ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል መቀበላቸውን ሲያውቁ ቅዱስ ጴጥሮስንና ቅዱስ ዮሐንስን ላኩበቸው፡፡ እነርሱ እጃቸውን በመጫን በሕዝቡ ላይ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ አሳዳሩባቸው፡፡ ይህንን ያየ ሲሞን መሰሪንም ብዙ ገንዘብ አምጥቶ እኔም እጅን የሚጭንበት ሰው መንፈስ ቅዱስ እንዲያድርበት ይህንን ሥልጣን ስጡኝ አለቸው ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹የእግዚአብሔርን ሥጦታ በገንዘብ ልትገዛ አስበሃልና ገንዘብህ ከአንተ ጋር ይጥፋ›› አለው፡፡ ሙሉ ታሪኩ በመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያት ሥራ ምዕ 8፣18-23 ላይ ይገኛል።

ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ የሚያስተምረን ሁለት ቁምነገር አለ። አንዱ መንፈስ ቅዱስን ለማታለል የመሞከር ተግባር ሰይጣናዊ እንጂ መንፈስቅዱሳዊ እንዳልሆነ ሲሆን ሌላው ይህንኑ በገንዘብ እና በሌላ ጥቅማዊ መንገድ የእግዚአብሔርን ሹመት ለማግኘት መሞከር በሐዋርያት ዘመንም ታይቶ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ የሚመሩት ሐዋርያት እንዴት እንደተዋጉት ያሳየናል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የሚመራው በመንፈስ ቅዱስ ነው።ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዋለበት እየዋሉ እና ካደረበት እያደሩ የተማሩት ሐዋርያት የመጀመርያ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤያቸውን በ50 ዓም ካደረጉ ጀምሮ ከእዚያ ቀድሞም ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጴጥሮስ የሰጠው ስልጣነ ክህነት  መሰረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንም ሆነች ምስራቃውያን የኦርቶዶክስ አብያተክርስቲያናት በጳጳሳት ሹመት ሂደት ላይ የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ብቻ እንዲሆን እና ምንም ዓይነት የፖለቲካ፣የዘር፣የገንዘብ እና ሌላም  ተጽዕኖ እንዲኖረው አይፈቀድም። ይህ መንፈስ ቅዱስን በውጪያዊ ተጽዕኖ ለማግኘት የሚሞክር ሁሉ የሲሞን መሰሪያዊ መንገድ የተከተለ ተደርጎ ይወሰዳል።

ሰሞኑን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እያካሄደች ያለው የርክበካሕናት ጉባኤ ላይ ከቀረቡት አጀንዳዎች ውስጥ በጎሳዊ እና ፖለቲካዊ አድመኝነት የቤተክርስቲያኒቱን ቅዱስ ሲኖዶስ ለመክፈል የሞከሩ እና በኋላም በመግባባት ወደ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የተመለሱት ሶስቱ ጳጳሳት በሕገወጥ መንገድ የሾሟቸውን አሁን በቅዱስ ሲኖዶስ በሚገባ ሳይመረመሩ እና የሚገባቸውና የማይገባቸውን ቤተክርስቲያን ከሐዋርያት ጉባኤ ጀምሮ የምትመረምርባቸውን የመንፈስ ቅዱሳዊ መንገዶች በመግፋት እንዲሾሙ የሚገፉ ደፋሮች እያየን ያለበት ጊዜ ነው። ይህ ሲሞን መሰሪያዊነት ነው።ፈጽሞ ተቀባይነት የለውም።

ቤተክርስቲያን ጳጳሳትን የምትሾመው የፖለቲካው አውድ እንዲፈነጥዝ ወይንም ይህኛው ጎሳ ደስ እንዲለው ሌላው እንዲከፋው አይደለም።ማንም ማን ቢሆን መንፈስ ቅዱስ የሚሾመውን ከሁሉም የሀገሪቱ ክፍል በእኩል ዓይን አይታ፣መርምራ እና ጸሎት አድርጋ ትሾማለች እንጂ በሆያሆዬ እና የፖለቲካ ትኩሳት ለማብረድ የምትሾምበት የጳጳሳት አሿሿም መንገድ የለም።ይህንን ቤተክርስቲያኒቱን በቅርበት የማያውቁ ፖለቲከኞች ጠንቅቀው ሊያውቁት የሚገባ እና በእንቢተኝነት ቤተክርስቲያኒቱን ለማዋከብ ከሞከሩ የሲሞን መሰሪ የተሰጠ ቅጣት ለእነርሱም እንደሚተርፍ ሊረዱት ይገባል።


Thursday, May 4, 2023

በአማራ ክልል ያለው ወቅታዊ ሁኔታ በመመካከር፣በመግባባትና በሽምግልና ብቻ ነው የሚፈታው።በአማራ ክልል ጸብ ከምታባብሱ የመረጃ አዛቢዎች በላይ የአማራም ሆነ የመላዋ ኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት የለም።


 

በአማራ ክልል ያለው ወቅታዊ ሁኔታ ፈጽሞ ወደ የደም ማፋሰስ ሊያመራ የሚገባው ጉዳይ ሊሆን አይችልም። ህዝብም ሆነ መከላከያ ፈጽሞ ምንም ዓይነት ግጭት እንዲፈጠር ፍላጎት ብቻ ሳይሆን የሚያጋድል በቂ ምክንያት አለመኖሩንም ጭምር ያምኑበታል። ይህም ሆኖ ግን ከውጪ ሆነው በአማራ ህዝብ ላይ ጦርነት እንዲነሳ ግፋ በለው የሚሉ እና በሰራዊቱም ውስጥ መንግስት አላስፈላጊ እርምጃ እንዲወስድ እና ህዝብ በመከላከያ ላይ ቅሬታ እንዲኖረው የሚፈልጉ ይጠፋሉ ማለት አይቻልም። ከእዚህ በተጨማሪ የኢትዮጵያን የጸጥታ መደፍረስ ከሱዳን ጋር ተያይዞ ምስራቅ አፍሪካን ለማበጣበጥ የሚፈልጉ ደግሞ የራሳቸውን የቤት ሥራ አይሰሩም ማለት አይቻልም።

የመረጃ አዛቢዎች መከላከያን ሊያጠቅ የመጣ ታጣቂ እንዳለ ይነግሩታል። በሌላ በኩል ደግሞ መከላከያ የሆነ ብሔር ወክሎ የመጣ አድርገው የመከላከያን ቁመና ለማውረድ የሚሞክሩ ደግሞ ሕዝቡን በሌላ አቅጣጫ ለማስደንበር ይሞክራሉ።ከእዚህ ሁሉ ጋር ደግሞ እራሱ መንግስት ከመጀመርያው የልዩ ኃይልን ወደ መደበኛ ሰራዊት የማስኬድ ሂደት አስመልክቶ መንግስት ከአማራ ክልል ጋር ያደረገው የኮሚኒኬሽን መንገድ መልክ ባለው አካሄድ አለመሆኑ ሌላው አሁን ላሉት አለመግባባቶች ያደረሱ ናቸው።

ኢትዮጵያውያን የራሳቸውን መከላከያ አይገድሉም።መከላከያም ለሀገር ሕልውና የቆመን የመግደል ፍላጎት የለውም። ይህ በእንዲህ እያለ ግን የመረጃ አዛቢዎች በተለያዩ የማኅበራዊ ሚድያ ገጾች እየተጠቀሙ በተከታታይ የሚለቋቸው መረጃዎች የሰራዊቱን አመራሮችንም ሆነ ከህዝቡ የወጡ ታጣቂዎችን የማስደንበር ሥራ በመስራት ነገሮች ከሚገባ በላይ እንዲጋጋሉ የማድረግ እኩይ ተግባር ላይ ተጠምደዋል።

 አሁን የተጀመሩ የሽምግልና እና ወደ ሕጋዊ የመግባባት መስመር የመምጣት ሂደቶች በጎንደር በጥሩ ደረጃ ተጀምሯል። ነገ ጧትም ከመከላከያ ጄነራሎች እና የሕዝብ ታጣቂዎች መሃል ቀጠሮ ተይዟል። ዛሬ ከቀትር በኋላም የመከላከያ ጄነራሎችም ሆኑ ታጣቂዎች በተማመነ መንገድ መነጋገራቸው ነው የተሰማው። ከእዚህ በፊትም በሰሜን ወሎ ተመሳሳይ መነጋገር ተደርጎ ጉዳዩ በመግባባት ካለቀ በኋላ አሁንም የመረጃ አዛቢዎች የተወሰኑትን ለማስደንበር መሞከራቸው ይታወቃል።

የአማራ ክልል የጦርነት አውድማ እንዲሆን የሚፈልጉ የተለያዩ ፍላጎት ያላቸው የውስጥም ሆነ የውጭ ኃይሎች መኖራቸው የታወቀ ነው። ሆኖም ግን አማራን እንወክላለን የሚሉም ሆኑ የአማራ ህዝብ እንደተቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ በ21ኛው ክ/ዘመን ወደ የተሻለ እድገት እንዲሻገር ይህ እርባና የለሽ እና የራስ የሆነ የቀኝ እጅ መከላከያን በመቁረጥ የአማራ ክልልም ሆነ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያተርፈው አንዳች ነገር የለም። ስለሆነም በሁሉም አካባቢዎች ያሉ የሀገር ሽማግሌዎች፣የኃይማኖት አባቶች እና የንግዱ ማኅበረሰብም ጭምር በታጣቂዎች እና በመከላከያ መሃል በመሸምገል እና ሁሉንም ጉዳይ በህጋዊነት መልኩ እንዲያልቅ በማድረግ ሰላም የግድ መምጣት አለበት። በመንግስት በኩልም የሕዝብ ባሕላዊ ዕሴቶችን የማወቅ እና የማክበር ጉዳይም በአሁኑ የአማራ ክልል በተነሳው አለመግባባት ውስጥ መኖሩን ማመን አለበት። የወታደራዊ መንግስት እስከወደቀበት ጊዜ ድረስ የወልቃይት ህዝብ፣የቦረና የቀድሞ ሲዳማ፣አፋር እና የሱማሌ ቆላማ ቦታዎችን ላይ መሳርያ የመግፈፍ ሥራ ሙሉ በሙሉ ያልፈጸመው ይህንኑ የአንዳንዳ አካባቢዎች የባሕላዊ ዕሴቶች ዋጋ ስለሚያውቅ መሆኑም መረዳት ያስፈልጋል። በአማራ ክልልም ያለው ሁኔታም በደንብ መታየት ያለበት እና በሀገሪቱ ሕግ የመሳርያ ማስመዝገብ ሕግ ላይ አጥብቆ መስራት እና ሌሎች የጸጥታ ህጎች ላይ መስራት ይገባል። የነፍስ ወከፍ መሳርያዎች በተመለከተ ግን በኢትዮጵያ ሕግ መሰረት መመዝገባቸው በቂ መሆኑን ቢያንስ በእዚህ ጊዜ በደንብ መረዳት ያስፈልጋል። አሁንም ግን በአማራ ክልል ጸብ ከምታባብሱ የመረጃ አዛቢዎች በላይ የአማራም ሆነ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት የለም። ሰላም፣መረጋጋት እና መከላከያን በጋራ ማጠናከር የአማራ ክልልም ሆነ የሁሉም ኢትዮጵያውያን የውዴታ ግዴታ ነው። በመከላከያም ሆነ በህዝቡ መሃል ሆነው የመረጃ መዛባት የሚፈጥሩ ቢያንስ የህዝብ ስቃይ እንዲታያችሁ ወደ ህሊናችሁ ተመለሱ።

==============/////===========
 

Wednesday, May 3, 2023

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን አንዳንዶች ለማጣጣል በምትሞክሩት ደረጃ ዕውን ሀገር አጥፍቷል? እናንተ ጠቅላይ ሚንስትር ብትሆኑ ኢትዮጵያ የገጠሟትን ችግሮች እንዴት ነበር የምትፈቷቸው?



==========
ጉዳያችን ምጥን
==========

ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ ለኢትዮጵያ በመስራት፣በማሰብ እና አዳዲስ ሀሳቦችን በማፍለቅ ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ የሔደችባቸው መንገዶች የፈተና እና የችግር ብቻ እንዳይሆኑ ትልቅ ድርሻ ተወጥተዋል። ይህንን ዕውነታ መጋረድ ምን ያህል አሳዛኝ እና ኢፍትሃዊነት እንደሆነ አይገባኝም። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ገና ለፓርላማ ንግግር ሳያደርጉ ጀምሮ ከኋላ ታሪካቸው በመነሳት በከፍተኛ ተስፋ ከደገፉት ውስጥ ነኝ። ጠቅላይ ሚኒስትሩን በዓይን ፊት ለፊት ያየኋቸው በኦስሎ የኖቤል ሽልማት ለመቀበል በተገኙበት የኦስሎ ማዘጋጃቤት አዳራሽ ተገኝቼ ሽልማታቸውን ሲቀበሉም ሆነ ታሪካዊ ንግግራቸውን ሲያደርጉ በዝግጅቱ ለመታደም በገጠመኝ ዕድል ጊዜ ነው። ከእዚህ ውጪ የማያቸውም የምሰማቸውም በመገናኛ ብዙኃን ነው። 

ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደማንም ሰው ከስህተት ነጻ እንደማይሆኑ አምናለሁ። በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ የሆነውን ሁሉ ለእኔ አዎን! ለእኔ መለኪያዬ እርሳቸው  በዘር እና በጎሳ ፖለቲካ እንዲሁም ለ27 ዓመታት በነቀዘ አስተዳደር የተጎሳቆለች ኢትዮጵያን መረከባቸው እና እርሳቸው ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ይህች በተቋማቷ ብቻ ሳይሆን በአካቢያችን እና በአፍሪካ ደረጃ የተጎሳቆለ ጥግ ላይ የቆመች ሃገር እንዴት ከግራ እና ከቀኝ የነበረውን መጓተት  አንዴ ወደ አንዱ ሌላ ጊዜ ወደሌላው እየተጎተተ ሃገር ሲንገላታ እርሳቸው ያንንም ያንንም ለመያያዝ እየደከሙ የሄዱበት አስቸጋሪ መንገድ ሁሉ ሲታሰብ በእርሳቸው ቦታ ብንሆን ምን ነበር የምናደርገው? የሚለው ከማሰብ በመነሳት ነው።

አዎን! ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕግ ማስከበር ላይ ችግሮች እስኪያድጉ የመጠበቅ እና አንዳንድ ጉዳዮች ለምሳሌ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሲኖዶስ የመክፈል ሙከራ ላይ መጀመርያ የያዙበት አያያዝ እና ሌሎች ላይ የፈጠሩት ክፍተት በደንብ ይገባኛል። ለእኔ አልገባህ ያለኝ አንዳንዶች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሆን ብለው ሀገር የማፍረስ ዓላማ ያላቸው አድርገው የሚያቀርቡት ብቻ ሳይሆን መንገዳቸው የጎሳ ፖለቲካ አዋጪ ነው ብለው የሚያምኑ አድርገው የሚያቀርቡት ኢተአማኔ የሆነው ጉዳይ ነው። የጻፏቸው የመደመር መጽሐፍ ላይ የጎሳ ፖለቲካ እንደማያዋጣ ብቻ ሳይሆን መደመር ብቻ አማራጭ እንደሆነ በሚገባ ተንትነው ገልጸው ጽፈውታል። አንድ ሰው ያላመነበትን በእዚህን ያህል የተብራራ እና ከውስጥ ፈንቅሎ በወጣ ስሜት ስለ መደመር እንዴት ይጽፋል?

ለኢትዮጵያ አንድነት ቤተመንግስቱ ትቶ ዘመቻ ለሔደ፣ የኢትዮጵያን ቤተመንግስት ለማደስ ለሰራ ብቻ ሳይሆን የቀደሙትን ነገስታት ሙዜም ላስቀመጠ፣ በጦርነት ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን ካቆመ ብሎ ለሰላም ደም ከተቃባቸው ጋር በሰላም አብሮ ገበታ ለተቀመጠ፣ የዓባይ ግድብ ብቻ ሳይሆን መከላከያ፣አየር ኃይል፣የትምሕርት ፖሊሲን፣የወደቀውን የልማት ባንክ፣ የተዳከመው የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እና ሌሎችን የኢትዮጵያ ተቋማት መልሶ ለማቆም ሥራዎችን በመስራት ዓይነተኛ ለውጥ ላመጣ መሪ የምንሰጠው የማጥላላት ደረጃ ዕውን ሰውየውን የሚመጥን ነው? ዐቢይ ዕውን ማኅበራዊ ሚድያው ብቻ ሳይሆን አንዳንድ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ሃሳባቸውን የሚሰጡ ፖለቲከኞች እንደሚሉት ነው? ነው ወይንስ ለእኔ የማይታየኝ ለሌላው የሚታየው ሌላ ዓለም አለ? 

እዚህ ላይ አሁንም እደግመዋለሁ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሸኔ አንጻር እና የሸኔ ጽንፈኛ በኦሮምያ የስልጣን መዋቅር ውስጥ ገብተው እንደፈለጉ ሲሆን ወሳኝ እርምጃ አለመውሰዳቸው በተመለከተ አሁንም የእኔም ቅሬታ ነው። ይህም ሆኖ ግን ይህንን በዓላማ እና በተንኮል ኢትዮጵያን ለመጉዳት ብለው ነው ብዬ ሳይሆን እሳቸው ችግር ይፈታል የሚሉበት የራሳቸው ዓለም ውስጥ የገቡ ሆኖ ይሰማኛል።በእዚህ ሁሉ ሂደት ላይ ከወለጋ በተፈናቀሉት አንጻር እና አሁንም የኦሮምያ ክልል በአዲስ አበባ ዙርያ እና በአዲስ አበባ ነዋሪዎች ላይ እያደረሰ ያለው ግፍ ዙርያ የወሰዱት እርምጃ አለመኖሩ ሌላው ተጠቃሽ የመንግስታቸው ተአማኒነት ብቻ ሳይሆን ብዙ ሕዝብ ተስፋ እንዲቆርጥ ያደረገው ነው። 

ይህ በእንዲህ እያለ፣
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደስልጣን ባይመጡ ኖሮ ወደኋላ አምስት ዓመት እንሂድ እና በኦሮምያ እና በአማራ መካከል የነበረው የዚያን ጊዜ ውጥረት ወዴት ይደርስ ነበር? እዚህ ላይ የዛሬ አምስት ዓመት የነበረውን የለውጡ ሂደት ሲጀመር የነበረውን አውዳሚ አካሄዶች ሁሉ እናስታውስ።
  •  እርሳቸው በሔዱበት ደረጃ በደረጃ ስልጣን የመረከብ አካሄድ ባይኬድበት ኖሮ ህወሓት ስልጣኑን ይለቅ ነበር?
  • የዓባይ ግድብ በተዝረከረከበት ሁኔታ አሁን ያለበት ደረጃ ይደርስ ነበር?
  • ተዳክመው የነበሩት የኢትዮጵያ ቁልፍ ተቋማት መከላከያ፣አየር ኃይል፣የልማት ባንክ፣የትምሕርት ፖሊሲ፣ የክክሎች የፌድራል መንግስት አካል መሆን፣ የሱማሌ የአብዲኤሊ የመገንጠል ሙከራ አደጋ፣ ከኤርትራ ጋር የተሻሻለው ግንኙነት፣የህወሃት የዙር ጦርነት እና የሃገር ህልውና አደጋው፣ቆይቶም ወደ እርቁ ለመምጣት የተሄደበት ሂደት ሁሉ የመሪው የነገሮችን አጠቃላይ ሁኔታ የመረዳት አቅም ውጤት አይደለም?
በመጨረሻ ባለፉት አምስት ዓመታት ኢትዮጵያ የገጠሟትን ፈተናዎች ሁሉ እኛ ጠቅላይ ሚኒስትር ብንሆን የቱን አስቀድመን የቱን እናስከትል ነበር? እስኪ እራሳችንን እንጠይቅ። ፈተናዎች ነበሩ። አዎን! እጅግ የሚያሳዝኑ ፈተናዎች አልፈናል። እነኝህ ፈተናዎች ግን እኔ እስከሚገባኝ ድረስ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ ስልጣን ባይመጡም የሚቀሩ ፈተናዎች አይደሉም።ይልቁንም ክልሎች አሁን ከምናየው በላይ የተመሳቀለ አደጋዎች ውስጥ እንገባ እንደ ነበር ነው የሚገባኝ። በትንሹ የሱማሌን የአብዲ ዔሊ የመገንጠል ሙከራ በራሱ ለኢትዮጵያ ትልቅ አደጋ ይዞ ይመጣል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በአቅም፣በርዕይ እና በአፈጻጸም ፍጥነት እና ጥራት እንዲሁም ክትትል የሚታማ መሪ አይደለም። ሰውየው አንድ ነው። አስር አይደለም። በብዙ ችግር በታጠረች እና ሀገሪቱን ለማጥፋት የ24 ሰዓት ጊዜ ወስደው በሚሰሩ የውጭ እና የአካባቢ ሀገሮች ውስብስብ መንገድ ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከውስጥ ሆነን የሚሰራውን ብቻ ሳይሆን ሲያነጥስ ሁሉ ተንኮል አለበት እያልን ነገር በመጎንጎን የማናሰራው ሁሉ ተደምረን እና እነኝህን ሁሉ ተቋቁሞ መስራት በራሱ አንድ እራሱን የቻለ ፕሮጀክት ነው። እስኪ ከመተቸት እና ከማብጠልጠል በላይ ይህ የኢትዮጵያ የጋራ ጉዳያችን ነው ብለን ያገዝነው ሥራ ምንድን ነው? በህልውናው ዘመቻ የነበረውን ተሳትፎ ሳንጨምር ማለት ነው። በህልውና ዘመቻ የብዙዎች ርብርብ ስለነበር።

አሁንም በአዕምሮዬ ያለው ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን አንዳንዶች በእዚህ ደረጃ ለማጣጣል የምትሞክሩትን ያህል ሀገር አጥፍቷል? እናንተ ጠቅላይ ሚንስትር ብትሆኑ እነኝህን ችግሮች እንዴት ነበር የምትፈቱት? የሚለው ነው።
አንዳንዴ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ ወጥ ሲጨልፍ ስናየው፣መንገድ ሲጠርግ ስንመለከት ሌላው ቀርቶ በመሪ ደረጃ ዝናብ ሲመጣ ዣንጥላ ሳያስይዝ እራሱ ይዞ እና ዝቅ ብሎ ስናየው እንደፈለግን ለመተቸት ተመቸን መሰለኝ። ስንወቅስ እና ስንተችም ኢትዮጵያዊ ጨዋነት የሚባል ነገር አንርሳ እንጂ! የሰፈራችንን የዕድር ሊቀመንበር የምናከብርበትን ክብር ሰጥተን ከእዝያ የሚሰማንን መውቀስ የወግ ነው። ሰውየው ግን በማኅበራዊ ሚድያ በሚሉት ደረጃ የሀገር አጥፊ ነው ብሎ ማመን ከቀላል አመክንዮ የመራቅ ችግር ብቻ ነው።ለሁሉም ጊዜ እና ታሪክ ያሳየናል። ይህም ሁላችንም ዕድሜ ካደለን ነው።ባጭሩ የአንዳንዶቻችን አወቃቀስ መሰረተ ቢስነቱ ቢብስብኝ ነው ይህንን ለማለት የተገደድኩት።
=========================////===========

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...