ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, July 17, 2023

ጳጳሳት ከቡድናዊ ስሜት ወጥተው በውጭ ያሉ አጥብያዎችን ምዕመናንን ሁሉንም እኩል በማየት ዝቅ ብለው ወርደው የአጥብያዎችን፣ የምዕመናንን እና የካህናትን ችግር እንዲፈቱ እራሱ ክርስቶስ ምሳሌ ሆኖ እንዳስተማራቸው ለአፍታም ሊዘነጉት አይገባም።


  • በውጭ ያለችው ቤተክርስቲያን የፍትሕ እጦት ብዙ መዘዝ እንዳያስከትል ያስፈራል።
  • ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ''እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመበት ለመንጋው ሁሉ (ሁሉ የሚለው ተሰምሮበት) እና ለራሳችሁ  ተጠንቀቁ! ያለው ሁልጊዜ መታወስ ያለበት ቅዱስ ቃል ነው።''

ይህ መልዕክት ነው።በእዚህ ዘመን በውጭ ሀገር ምዕመናን ተሳቀው፣ወጥተው ወርደው ያገኙትን ጥሪት አውጥተው የገዟቸውን አብያተክርስቲያናት መጥቶ የሚባርክላቸው፣በልጅነት ያጠፉትን እንደ አባት ወርዶ ይህ እንዲህ ይስተካከል፣ ያንን እንዲህ አድርጉት ብሎ አብሮ የሚመራቸው አባት እንጂ በቡድናዊ ስሜት ውስጥ ገብቶ አንዱን ልጅ ሌላው የእንጀራ ልጅ አድርገው እንዲያስተዳድሩ መንፈሳዊም ሆነ ምድራዊ ሕግ አይፈቅድም። አንዳንድ ድርጊቶች ግን ምዕመናን ቤተክርስቲያንን የሚያዩበት ዓይን ብቻ ሳይሆን እምነታቸው እስኪፈተን ድረስ አደገኛ አካሄድ እየተፈጠረ ነው። የእዚህ ዓይነት የአስተዳደራዊ በደሎች ሃይማኖትን ብቻ ሳይሆን ሀገርንና ትውልድን ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያን ስም የሚያጠለሽበት ደረጃ ደርሷል።

በውጭ ሀገር ባሉ አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ለመልካም ስራ ከሚያወጡት ይልቅ ለባዕዳኑ ፍርድ ቤት አንዱ አንዱን ለመክሰስ የሚያወጡት ገንዘብ በደንብ ተጠንቶ ቢቀርብ እጅግ ልብ የሚያደማ ነው። የክሶቹ መነሻዎች ደግሞ ተራ እልህ እና እንዲህ ብሎኝ እንዲያ አድርጎኝ የሚሉ ከመሆናቸው አልፎ ጳጳሳት ዝቅ ብለው የአብያተ ክርስቲያናትን ችግር ምዕመኑ ጋር ወርደው ለመፍታት ያደረጉት ጥረት እዚህ ግባ የማይባል የመሆኑ ውጤት ነው። ምዕመናንን ሁሉ እኩል አይቶ ማስተዳደር፣ ከአድመኝነትና እልህ ስሜት ወጥቶ ርቱዕ በሆነ መንገድ ቡድናዊነት በማይታይበት መልኩ ዝቅ ብሎ ወርዶ ምዕመኑን ማነጋገር ያስፈልጋል።በስማ በለው የሚሰራ ስራም ሆነ አገልግሎት የለም።አይደለም ስለ ብዙ ምዕመናን፣ስለ አንድ ምዕመን ህይወት መጠየቅ አለ። የምዕመናን እንባም አጥቦ ይወስዳል። ለአንድ ቡድን ወግኖ የቤተክርስቲያንን ጥቅም ሜዳ ላይ በትኖ እንዴት ለአንድ ቀንስ እንቅልፍ ይተኛል? በጎቼን ጠብቅ ብሎ አደራ የሰጠ አምላክ ስለ መንጋው አይደለም ስለ አንድ ምዕመን ሀዘን ይገደዋል።

ጆሮ ያለው ይስማ! መንገድ ላይ የሚጮህ ''እብድ '' አይደለም ህጻናት ሲጫወቱ እርስ በርስ የተነጋገሩትን ''ይህች ንግግር ለእኔ ነች  ወዮልኝ!'' ብለው እያነቡ ወደ ገዳም የሄዱ አባቶች ያሏት ቤተክርስቲያን በተራ እልህ እና  የአንድ ቡድን ስሜት ይዞ በመሄድ ቤተክርስቲያንን መጉዳት በእግዚአብሔር ዘንድ እንደሚያስጠይቅ ለማስረዳት ጥቅስ መደርደር አያስፈልግም።

ከሊቀ ካሕን ክርስቶስ የሚበልጥ ጳጳስ የለም። ካህኑ ዔሊ ከ40 ዓመታት በላይ ታቦተ ጽዮንን ማገልገሉ በኋላ ባሳየው ቸልተኛነትና ቡድናዊ ስሜት ከመቀጣት አላዳነውም። ምዕመናን መፍትሄ የሚሰጣቸው ቤተክህነት እና ሊቀ ጳጳስ ይፈልጋሉ። ችግሮች የሚፈቱት በባዕዳን ፍርድቤት የቤተክርስቲያንን አጀንዳ ይዞ በመዞር አይደለም።የምዕመናንን ገንዘብ በየባዕዳኑ ፍርድቤት እየበተኑ ኃላፊነት ባልተሰማ መንገድ ምዕመናን ሲበተኑ ቆሞ በማየት ሊሆን አይችልም።ስለእዚህ ጉዳይ የማይገደው ማንም ክርስቲያን የተባለ ሊኖር አይገባም።

ዝቅ ብሎ ምዕመኑ ጋር ቀርቦ ችግሩን መፍታት፣ሸክሙን መሸከም የተሰጠ አደራ ነው። እግዚአብሔር ከማደርያው ሆኖ የሚፈጸሙትን የግፍ እና የአድሏዊ አሰራሮች ይመለከታል። ተመልክቶ ግን ድንገት በቃ ብሎ ይነሳል። ይህንን መጠን ያለፈ መንጋውን በፍቅር ሳይሆን በኃይል ለምግዛት የመሞከር አካሄድን አለመናገር በራሱ በእግዚአብሔር ዘንድ ያስጠይቃል።መጽሐፍ ያስተማረው ጳጳሳት መንጋውን በኃይል ሳይሆን በፍቅር እንዲመሩ ነው። 

በውጭ እና በሀገር ውስጥ ያለው የሲኖዶስ መከፈል በኋላ ቀድሞ የነበሩ የአጥብያዎች የእርስ በርስ ችግሮች ውስጥ ስንት ችግሮች በውጭ ባሉ ጳጳሳት ተፈታ? ስንቶቹ አሁንም ድረስ ፍርድ ቤት ለፍርድ ቤት ሲሄዱ ጳጳሳት አንተም ተው! አንተም ተው! ብለው ሲሆን አልቅሰው እና ምዕመኑ መሃል ቀርበው ፈቱ? ስንቶቹ ጋር በአንዱ ቡድን ውስጥ እየገቡ ችግሮቹ ተባባሱ? በእዚህ ላይ እስኪ ቤተክህነት ጥናት ያጥና እና እነኝህን ችግሮች ይፍታ! ችግሩ ጣርያ ደርሶ ሀገር ሲታመስ ከመሮጥ ዛሬ ላይ ቀድሞ መፍትሄ መስጠት ያስፈልጋል። የቤተክርስቲያን ጉዳይ የጳጳሳት ጉዳይ ብቻ፣ወይንም የዲያቆናት ጉዳይ ብቻ አይደለም። ምዕመናን የራሳቸው ድርሻ አላቸው።መንጋውን በኃይል እንዲገዛ የተፈቀደለት እረኛ እንደሌለ መጽሐፍ ነግሮናል።በፍቅር፣ዝቅ ብሎ ምዕመናን እና ካህናቱ መሃል ቁጭ ብሎ የመነጋገር እና የመፍታት ለእዚህም የሚመጣ ማናቸውንም ፈተና ለመቋቋም የእያንዳንዱ እረኛ ግዴታ ነው።ቁራም ይጮሃል፣እብድም ይናገራል።ይህች ንግግር ለእኔ ነች ብሎ የሚሰማ ይስማት።የማይሰማ ንቆ ይተዋት። ይህ የሰማይ ደጅ ጉዳይ ነው።በሰማይ ደጅ ጉዳይ ነው።ምዕመኑ የሰማይ ደጁን ጉዳይ ጳጳሳት ዝቅ ብለው ወርደው እንዲፈቱ አሁንም ይለመናሉ።እግዚአብሔር ሳይነሳ ሰውም ሳያመር ትናንት የነበሩበትን አስታውሶ እንደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዝቅ ብለው ችግሮችን እንዲፈቱ ይለመናሉ።

''በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ!'' ሐዋ ስራ 20፣28

===============/////፟=============

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...