ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, November 18, 2021

ኢትዮጵያ አንገት ላይ እንዲጠመጠም በህወሓት ታቅዶ የተጻፈው አንቀጽ 39 አድፍጦ ቆይቶ ህወሃት አንገት ላይ ይጠመጠማል ብሎ ማን ገመተ?

ከንቲባ አዳነች አቤቤ 

===============
ጉዳያችን / Gudayachn
===============
''ፅድቅና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም፣
ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም።'' ታላቁ ፀሐፊ ከበደ ሚካኤል 

በሀገራችን የሚባል አባባል አለ።''ጉድጓድ አርቀህ አትቆፍር።ከቆፈርክ ደግሞ አታርቀው።ማን ኢንደሚገባበት አይታወቅምና'' ይላል።
ዘንድሮ አለመሳቅ አይቻልም።አንዷ የጁንታው ደጋፊ በፈረደበት ማኅበራዊ ሚድያ ላይ ብቅ ብላ እንዲህ አለች '' የኢትዮጵያ አንድነት የሚሉት አንቀጽ 39 ይፈልጉታል።ምክያቱም ትግራይ እንድትገነጠልላቸው'' ብላው አረፈች። እርሷ የተነገረችውን እንደ ቧንቧ ማስተላለፍ ነው። እንድታስተላልፍ የተነገራት ግን አንድ የሚያሳየው ስዕል አለ።  ኢትዮጵያ አንገት ላይ እንዲጠመጠም ታቅዶ የተጻፈው አንቀጽ 39 አድፍጦ ቆይቶ እራሱ ህወሃት አንገት ላይ ተጠምጥሟል።

ትግራይ በሪፈረንደም መገጠሉን እያሰበችበት መሆኑን የሚገልጥ መግለጫ ደብረፅዮንና ጌታቸው ባለፉት ሦስት ወራት ብቻ ስንቴ በትግራይ ቴሌቭዥን፣ሮይተርና ቢቢሲ ላይ እንደተናገሩ ገባ ብሎ መቁጠር ነው::መገንጠል በሕገመንግስቱ አስገብቶ አትንኩብኝ ያለውስ ማነው? እራሱ ህወሓት ነው::የኢትዮጵያ ህዝብ ደግሞ ኢትዮጵያን የሚገነጣጥለው አንቀጽ 39 እንዲወገድ ብዙ ለፍቷል። ይህንኑ አንቀጽ በመቃወም ሰዎች ታስረዋል፣ተገድለዋል፣ተሰደዋል። አንቀጹ ኢትዮጵያን ለማፈንዳት በሰዓት ተሞልቶ የተቀመጠ ''የጊዜ ቦንብ '' ነው በሚል ኢትዮጵያውያን ተቃውመዋል። ህወሃት ግን አንቀጹ ዋስትናዬ ነው እያለ ሲቀልድ ነበር። የኢትዮጵያውያን ጥያቄ ግን አንቀጹ ለትግራይም አደጋ ስላለው ለማንም አይበጅም ብለው በቅንነት ነበር ሲቃወሙት የኖሩት።

ሰሞኑን የአዲስ አበባ ከንቲባ ክብርት ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ''ቀይ መስመር'' በተሰኘው የኢቲቪ መርሃግብር ላይ ቀርበው ይህንኑ አንቀጽ 39 አንስተው ነበር።ከንቲባዋ የጠየቁት ህጋዊ ጥያቄ ነው። ጥያቄያቸው ህወሃት ለዘመናት ሲያቀነቅነው የነበረው በኋላ ስዩም መስፍንና አባይ ጸሃዪ በቴሌቭዥን መስኮት ቀርበው ሲያስፈራሩበት የነበረው።ከላይ እንደተገለጠው ደግሞ ደብረጽዮን፣ጌታቸው ረዳ እና ጻድቃን በትግራይ ቴሌቭዥን፣ቢቢሲ እና ሮይተርስ ላይ የትግራይ ህዝብ ለመገንጠል ድምጽ እንዲሰጥ እንደሚያስገድዱት ደጋግመው ገልጠዋል።እንደሚያስገድዱት ያልኩት ህዝቡ ፈቅዶ እና ወዶ አያደርገም የሚለውን ሃሳብ መነሻ በማድረግ ነው።

ይህንን በአደባባይ የተነገረ በህገ መንግስቱ ውስጥ እንዲገባ ህወሃት የተሟሟተበት አንቀጽ 39 ተከትሎ የክብርት ከንቲባዋ ጥያቄ  ትግራይ መገንጠል ከፈለገች ለምን ከ20 ዓመታት በላይ አብሯቸው የተጋደለው መከላከያን በሌሊት መግደል ለምን አስፈለገ? በህጋዊ መንገድ ጠይቀው ጉዳያቸው መታየት አይችልም ወይ? የሚል አጭር እና ግልጥ ነበር። ይህንን መሰረታዊ ጥያቄ የጁንታው አፈቀላጤዎች መመለስ አልቻሉም።ዝም ብለው አድበስብሰው ሊያልፉት ይሞክራሉ። 

እውነታው ግልጥ ነው። ህወሃት አንቀጽ 39 ያስቀመጠችው ለመገንጠል አቅዳ ነው። ነገር ግን መገንጠሉ የታሰበው እስከ ቤኒሻንጉል ያለውን ቦታ ከሱዳን አዋሳኝ ግዛቶች ከአማራ ክልል ቆርሶ ትልቋ ትግራይ የሚሏትን ከፈጠሩ በኋላ የታቀደ ነበር።የሰሞኑ ወደ አማራ እና አፋር የተደረገው ዘመቻም የተወሰኑ የአማራ እና የአፋር እንዲሁም የቤኒሻንጉል ክልል መሬት ከያዙ በኋላ በመደራደር አሜሪካንን ከጀርባ አሰልፎ መገንጠሉን ለማሳካት ነበር።ሆኖም ጉድጓድ አጥልቀህ አትቆፍር ማን እንደሚገባበት አይታወቅምና።አሁን ህወሃት በአፋር እና አማራ ክልል ተመትቶ ለመገንጠል ከሆነ ለምን በህጋዊ መንገድ አትጠይቁም? ይሄ ሁሉ ህዝብ ለምን እንዲያልቅ ተደረገ? የሚለው ጥያቄ አሁንም መላሽ ካለ እንጠይቃለን።

 የከንቲባ አዳነችን መሰረታዊ አና ተገቢ ጥያቄ ተከትሎ የህወሓት ዩቱበሮች እጃቸውን እያወራጩ ሰሞኑን እንደማበድም ሲያደርጋቸው ታይቷል። ስታሊን ለመቀወስ እሩብ ጉዳይ በሆነ መልኩ ቃል በቃል '' እናቷ ሆድ ብትገባ አታመልጠንም'' የሚል ቃል ተናግሮ ስሜቱን መቆጣጠር አንዳቃተው እያሳየ በከንቲባዋ ላይ ዝቷል።የርዮት ሚድያ ቴዎድሮስ እርሱም ቃል በቃል '' ኢትዮጵያዊነት በቅጂ የደረሰው ሁሉ፣ ኢትዮጵያዊነት በደብዳቤ የደረሰው ሁሉ'' እያለ ለመዝለፍ ሞክሯል። ኢትዮጵያ ልጆቿን ታውቃለች። የክብርት ከንቲባዋን ኢትዮጵያዊነት የህወሓት ግልገሎች ዛሬም ለክተው ሊሰጧት ይፈልጋሉ።አዳነች ብዙ ጊዜ ተናግራለች።ስለ ኢትዮጵያዊነቷ የምትመሰክርላት እራሷ ኢትዮጵያ እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው።የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህንን ጀግንነቷን ለኢትዮጵያ ያላትን ጥልቅ ፍቅር አይቶ ነው ዳግማዊት ጣይቱ ያላት።የጣይቱ እና የኢትዮጵያ አባቶች እነ ፊታውራሪ ገበየሁ፣ጀነራል ጃጋማ ኬሎ እና ኮለኔል አብዲሳ አጋ ደማቸውን አፍስሰው ባቆዩት ሀገር ስታሊን እና ቴዎድሮስ ዛሬም ኢትዮጵያዊነት በችርቻሮ ሊሰጡን ይፈልጋሉ።

ለማንኛውም  ኢትዮጵያ አንገት ላይ እንዲጠመጠም በህወሓት ታቅዶ የተጻፈው አንቀጽ 39 አድፍጦ ቆይቶ ህወሃት አንገት ላይ ይጠመጠማል ብሎ ማን ገመተ? ሆኗል!

 ===================///========


 


No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...