ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, October 8, 2018

በኖርዌይ ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የኢትዮጵያ ኤምባሲ በአይነቱ ልዩ ስብሰባ ጠራ።ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ከሁለት ሳምንት በኃላ ወደ አውሮፓ ይመጣሉ (ጉዳያችን ዜና)

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር  ዋና መስርያ ቤት 
ጉዳያችን/ Gudayachn
መስከረም 28/2010 ዓም (ኦክቶበር 8/2018 ዓም)

የለውጡ ነፋስ ወደ አውሮጳ እየደረሰ ነው

በኢትዮጵያ በ2010 ዓም አጋማሽ በኃላ በተፈጠረው የለውጥ ነፋስ ወደ አውሮፓ እየደረሰ ነው።ላለፉት ሀያ ስምንት ዓመታት በኢትዮጵያ ጉዳይ ግንባር ቀደም በመሆን የኢትዮጵያን ጉዳይ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ከብራሰልስ እስከ ለንደን፣ከጀኔቭ እስከ ኦስሎ ድምፁን  ከማሰማት አልፎ በተለያዩ ሀገራዊ ጉዳዮች ተሳትፎ ሲያደርግ የነበረው በአውሮጳ የሚኖረው ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊ በቅርቡ በሀገራችን በተከሰተው ለውጥ ደስተኛ መሆኑን ባደረጋቸው ሰልፎች እና ሕዝባዊ ስብሰባዎች መግለጡ ይታወሳል።

አሁን ደግሞ የመደመር እና የሀገራዊ አንድነት ሂደት አካል የሆነው ከኢትዮጵያ ኤምባሲዎች ጋር የፊት ለፊት ስብሰባዎች ከኢትዮጵያዊው ማኅበረሰብ ጋር መደረግ ተጀምሯል።በእዚህም መሰረት በመጪው ቅዳሜ ጥቅምት 3/2011 ዓም (ኦክቶበር 13/2018 ዓም) መቀመጫውን ስቶኮልም ያደረገው በኖርዲክ ሀገሮች የኢትዮጵያ ኤምባሲ በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ  ኢትዮጵያውያንን ጠርቷል።ኤምባሲው ለኢትዮጵያውያን ጥሪ ያደረገው በኢትዮጵያ ማኅበረሰብ (ኮምዩንቲ) በኖርዌይ በኩል ሲሆን ኮሚኒቲው መልዕክቱን በቫይበር ለአባላት ማሳወቁን ለማወቅ ተችሏል።

በብዙ ሀገሮች ላለፉት ሀያ ስምንት ዓመታት ያህል በኢትዮጵያዊው ማኅበረሰብ እና በኢትዮጵያ ኤምባሲዎች እና ቆንስላዎች መካከል የነበረው የደፈረሰ ግንኙነት እንደነበረ ሁሉ በኖርዌይም ተመሳሳይ ገፅታ ነበረው። ስለሆነም የመጪው ቅዳሜ ስብሰባ ልዩ የሚያደርገው ኢትዮጵያዊው በእኔነት መልክ የሚገኝበት የለውጥ ሂደቱን መደገፉን የምገልጥበት ብቻ ሳይሆን ከአሁን በኃላ ኤምባሲው የአገልጋይነት፣ኢትዮጵያዊውን ካለምንም ማዳላት የሚወክልበት  መድረክ እንዲሆን ሀሳቡን የሚገልጥበት እና ለሀገሩ ሰላም፣የዲሞክራሲያዊ ሽግግር እና መዋለ ንዋይ ማፍሰስ ላይ ሁሉ የሚኖረውን ሚና የሚያጎላበት አንዱ እና አይነተኛ መድረክ እንደሚሆን ይጠበቃል።የእዚህ አይነት መድረክ ከረጅም ጊዜ በኃላ የሚደረግ የጋራ ስብሰባ ከመሆኑ አንፃር ከፍተኛ ትዕግስት፣ጨዋነት እና ኃላፊነት በተሰማው መንገድ የኤምባሲው ልዑክም ሆነ  የስብሰባው ተሳታፊ በጋራ ሊያካህዱት ይገባል።




በቅዳሜው የኦስሎ ስብሰባ ላይ በኖርዲክ ሀገሮች የኢትዮጵያ አምባሳደር ፕሮፌሰር መርጋ በቃና እንደሚገኙ ተሰምቷል።ፕሮፌሰር መርጋ በቃና በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የእንስሳት ሕክምና ፋክልቲ ዲን፣ በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የባህል አካዳሚ የቦርድ አባል፣ የብሔራዊ የእንስሳት ሕክምና ኢንስቲትዩት የቦርድ አባል እና የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሆነው አገልግለዋል።ፕሮፌሰር መርጋ ከአማርኛ፣እንግሊዝኛ  እና ኦሮምኛ   በተጨማሪ ስፓኒሽ እና የፖርቹጋል ቋንቋ እንደሚናገሩ በተለይ የስፓኒሽ ችሎታቸው ከፍተኛ እንደሆነ ይነገራል። በመጪው ቅዳሜ ጥቅምት 3/2011 ዓም (ኦክቶበር 13/2018 ዓም) ኦስሎ የሚደረገው ስብሰባ አድራሻ  Norges Idrettshogslole, Sognsveien 220, 0863 Oslo ሲሆን ሰዓቱ  ከቀትር በኃላ  ከ14 - 18 ባለው ጊዜ ውስጥ ነው።

በሌላ በኩል እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ኦክቶበር 31/2018 ዓም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ አህመድ ወደ ጀርመን እንደሚመጡ ለማወቅ ተችሏል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጀርመን ጉብኝታቸው ከጀርመኗ ቻንስለር  ወ/ሮ አንጌላ ሜርክል እና ሌሎች ከፍተኛ የጀርመን ባለስልጣናት እና በተለይ ከአውሮፓ ከተለያዩ ከተሞች የሚመጡ ኢትዮጵያውያን ጋር ይገናኛሉ።በእዚሁም መሰረት በጀርመን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከመላው አውሮፓ ወደ  ጀርመን በመሄድ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩን ለማግኘት ለሚመጡ ቀድመው መመዝገብ እንዲችሉ  የኦን ላይን የመመዝገብያ ገፅ አዘጋጅቷል።

በመሆኑም ወደጀርመን ተጉዘው ከጠቅላይ ሚኒስትር  ጋር መገናኘት ለሚፈልጉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚያደርጉት የጋራ ስብሰባ ቀን፣ሰዓት እና የስብሰባው ስፍራ እና የመመዝገብያ ሊንክ ከእዚህ በታች ይመልከቱ።


የስብሰባ ቀን Date: 31st October 2018
የስብሰባ መጀመርያ ሰዓት Time: 13:00 (1:00pm)
የስብሰባው ቦታ እና አድራሻ Venue: Commerzbank Arena, Morfelder Landstrasse 362, 60528 Frankfurt am Main, Germany
በስብሰባው ላይ ለመገኘት ለመመዝገብ ይህንን ይጫኑ። ሆኖም ግን አለመመዝገብ በህዝባዊ ስብሰባ ላይ ከመገኘት የሚያግድ ጉዳይ አይደለም። የአውሮፓ ማዕከል በሆነችው ጀርመን ኢትዮጵያውያን በብዛት እንደሚገኙ ይጠበቃል።
ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ የተገጠመ ድንቅ ግጥም በገጣሚት ሳባ መኩርያ የግጥም ስብስብ ምረቃ ላይ የቀረበ ድንቅ ግጥም (ቪድዮ) 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...