ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Sunday, September 23, 2018

ለበታኝ ኃይሎች የሽብርተኛ ድርጊቶች እና የስነ ልቦና ጦርነቶች ምቹ አንሁን።

ጉዳያችን/Gudayachn
መስከረም 14/2010 ዓም (ሴፕቴምበር 24/2018)
=========================================
  • ህወሓት ከትግራይ ሕዝብ እምነት ውስጥ የመሸርሸር አደጋው እየፈጠነ ስለሆነ የመጨረሻ ሙከራ ለማድረግ ያለ የሌለ ኃይሏን ተጠቅማ አዳዲስ ግጭቶች ለመፍጠር ተደጋጋሚ ሙከራ ላይ ነች።በሌላ በኩል እስካሁን ድብቅ ግብ እንዳለው የሚነገረው ሐጂ ጃዋር፣ ጊዜ በሄደ ቁጥር የቄሮ ወጣት በዶ/ር ዓብይ እና ለማ ላይ ያለው እምነት እየጠነከረ እንዳይሄድ እና የርሱን ስፍራ እና ድብቅ ግብ እንዳያሳጣው ከፍተኛ ስጋት ላይ ነው።

መጋቢት 24፣2010 ዓም የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን መንበር የተረከቡት ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ አህመድ ላለፉት አምስት ወራት በርካታ ለውጦች አምጥተዋል።የጦር ሰራዊቱ፣የደህንነት ቢሮ ጨምሮ ሌሎች ቁልፍ ቦታዎች ላይ የለውጥ ሂደቱ ተጀምሯል።ሆኖም ገና የሚቀሩ ለውጥ የሚጠብቁ ቦታዎች አሉ።ለምሳሌ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አንዱ ተጠቃሽ ነው።ከለውጥ ሂደቱ ውስጥ የታጠቁም ሆኑ ያልታጠቁ የተቃዋሚ ኃይሎች እና አክትቪስቶች ወደ ሀገር ቤት መምጣት የፈጠረው የፖለቲካ ውጥረት መላላት ለኢትዮጵያ ልዩ ስሜት ፈጥሮ ሰንብቷል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን የለውጥ ኃይሉን እና በለውጡ የተደሰቱ ኢትዮጵያውያን ላይ የስነ ልቦና ጦርነት፣ሽብር እና ተስፋ ለማስቆረጥ የመሞከር ሂደት በሁለት ጥምር በታኝ ኃይሎች እየተከናወነ ነው።እነኝህ ኃይሎች፣የመጀመርያው ተመልሶ ወደ ስልጣን እርከኑ ለመውጣት የሚመኘው የህወሓት ቡድን ሲሆን ሁለተኛው በታኝ ኃይል ደግሞ በኦሮሞ ማኅበረሰብ ስም የሚነግደው የሐጂ ጃዋር ቡድን ነው። ሁለቱም ኃይሎች በስልት ደረጃ ተመጋጋቢ ለመሆን ሥራ ለመጀመራቸው ምልክቶች ታይተዋል።ትግራይ ኦን ላይን በድረ ገፁ ላይ ''ዶ/ር ዓብይ ከስልጣን ይውረዱ'' የሚሉ ፅሁፎች በእንግሊዝኛ ጭምር የስም ማጥፋት ዘመቻ ላይ ተጠምዷል።የስም ማጥፋት ዘመቻዎቹ ዓላማ ተከታታይ የስነ ልቦናዊ እና ሽብር መንዛትን ስራዬ ብለው ይዘውታል።


በተመሳሳይ መንገድ የሐጂ ጃዋር ቡድንም ሕዝብ እና የመንግስት ኃይላት እንዲፈሩት ያልተሳካ የሽብር  እና የመከፋፈል ተግባር ላይ መሰማራቱ በግልጥ እየታየ ነው።አንዳንዶች ጃዋርን ከቄሮ እንቅስቃሴ ጋር ብቸኛ ፈጣሪ እና አድራጊ አድርገው የሚያስቡ አሉ። ሆኖም ግን ቄሮ በኦሮምያ ውስጥ የተነሳ የወጣቶች ንቅናቄ ሲሆን መነሻው በቀደመው ስርዓት የነበረው በደል የፈጠረው የብሶት ንቅናቄ ነው።ይህ ንቅናቄ እና አመፅ ግን የራሱ የሆነ አደረጃጀት እና ቅርፅ ስለሌለው ለአመፅ በሚንቀሳቀስበት ጊዜ አይነተኛ የመገናኛ እና የማስታወቂያ መንገድ ሲፈልግ የተገኘው የሐጂ ጃዋር ፌስ ቡክ ቀጥሎም ''የኦሮምያ ሚድያ ኔት ዎርክ'' ነበር።የቄሮ የመብት ትግል እና አሁን ሐጂ ጃዋር የሚነግረን የሁለት መንግስት ትርክት እና ግብረ አበሮቹ የሚተርኩልን የአዲስ አበባን ሕዝብ ''መጤ እና ሰፋሪ'' እያሉ የሚሰድቡበት እንዲሁም ኢትዮጵያን ከስሯ ለመንቀል የሚደረገው ሩጫ እና በአንድነት የሚኖረውን የኢትዮጵያ ሕዝብ እጅግ ከፋፋይ በሆነ መርዘኛ ፕሮፓጋንዳ የማናከስ ሥራ ሁሉ ቀጥተኛ ሽብር በሕዝቡ ውስጥ የመፍጠር እና የፍርሐት ስሜት የማስፈን ስልት የያዘ እኩይ ተግባር ነው።


ላለፉት አምስት ወራት የብሔር ግጭቶች ከደቡብ ኢትዮጵያ እስከ ቡራዩ በአዲስ መልክ ለማስፋፋት ያልተኬደበት መንገድ የለም።የአዲስ አበባን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ሌላውን ኢትዮጵያዊ ሀገር አልባ ለማድረግ ከሚደረገው የጥላቻ ዘመቻ በተጨማሪ በሻሸመኔ ከተማ  ሕዝብ በተሰበሰበሰበበት አንድ ወጣት ዘቅዝቆ የመስቀሉ የግፍ ተግባር እና በቡራዩ የተፈፀመው አሰቃቂ የንፁሃን እልቂት ሁሉ ሕዝቡን ለማሸበር እና የስነ ልቦናዊ ጦርነት ከፍቶ በፍርሃት ለመሸበብ በመቀጠል አምባገነናዊ ስርዓት መልሶ ለማምጣት የታቀደ እቅድ ነው። 


በኢትዮጵያ ላይ ከአምስት ወሮች የለውጥ ሂደት በኃላ የህወሓት ስርዓት ተስፈኛ ቡድን እና የሐጂ ጃዋር አድናቂ ቡድን በኢትዮጵያ ላይ የሽብር፣የስነ ልቦና ጦርነት እና ኢትዮጵያዊነትን ከስሩ ነቅሎ በምትኩ እንግዳ የሆነ ስውር የፅንፍ ፖለቲካ ከለየለት የአምባገነንነት ስርዓት ጋር በኢትዮጵያ ሕዝብ ጫንቃ ላይ ለመትከል ሩጫ ላይ ናቸው።ሐጂ ጃዋር ሻሸመኔ ባለፈው ወር ሲገባ በሻሸመኔ  አንድ ወጣት ላይ በሕዝብ ፊት በሐጂ ጃዋር ሳብያ ተዘቅዝቆ መሰቀል (ሐጂ ጃዋርን ለመግደል ቦንብ ይዞ አገኘነው የተባለው እና በኃላ ፖሊስ ውሸት ነው ለፍቶ አዳሪ ምስኪን ወጣት ያለው) ሲያወግዝ ያልተሰማው እና በቡራዩ በፅንፈኞች ሕዝብ ከተፈጀ በኃላ በሳምንቱ ሃሳብ የሰጠው ሐጂ ጃዋር ሁለቱም ድርጊቶች በሕዝብ ዘንድ ሽብር መፍጠራቸውን እንደ አንድ ''ፖለቲካዊ ካፒታል'' ስለተመልከተው ነበር።ሆኖም ግን የበለጠ በሕዝብ ዘንድ እንዲጠላ አደረገው እንጂ ያስገኘለት ትርፍ አልነበረም። ይሄውም በሽብር ሕዝብ የሚፈራው እና የነገ የፖለቲካ ግብን ለማሳካት ለስላሳ መሬት የፈጠረ መስሎት ይሆናል። 


የሐጂ ጃዋር  ህዝብን በማሸበር የተፈራ ሆኖ ለመውታይት የማሰብ ተመሳሳይ አስተሳሰብ በህወሓት የለውጥ ሂደቱን በሚቃወሙ እና ተመልሰው ወደ ስልጣን ለመምጣት የሚፈልጉት ኃይሎችም ዘንድ እንድ ስልት እና  አይነተኛ መንገድ ተይዟል።ባጭሩ ሁለቱም ኃይሎች ሕዝብ ከተሸበረ፣ስነ-ልቦናው ከታወከ የዶ/ር ዓብይ እና የለማ የለውጥ ሂደት ይጠላል፣ውሎ አድሮ ሕዝብ እንዲነሳበት ይረዳል ብለው ያስባሉ።ይህ ብቻ አይደለም በአዲስ አበባ የሚታፈሰው ወጣትም ከላይ በተጠቀሱት ሁለት የፀረ ለውጥ ኃይሎች የውስጥ ደጋፊዎች እየተከናወነ የሚገኝ ሴራ ነው።አሁን በኢትዮጵያ ከላይ በተጠቀሱት ኃይሎች ከግርግር የሚጠቀሙ ስለመሰላቸው በተቻለ መጠን የማተራመስ ሂደት ይዞ የሚመጣው የኃይል ክፍተት ይዞ ስለሚመጣ በእዚህ ወቅት ስልጣን ለመያዝ ይመቻል ብለው በማሰብ የሽብር እና የስነ ልቦና ዘመቻ በማድረግ የህዝብን የሞራል ልዕልና ለማድከም እየተሞከረ ነው።

ለማጠቃለል ህወሓት ከትግራይ ሕዝብ እምነት ውስጥ የመሸርሸር አደጋው እየፈጠነ ስለሆነ ወደ ስልጣን ተመልሶ ለመንተላጠል የመጨረሻ ሙከራ ለማድረግ ያለ የሌለ ኃይሏን ተጠቅማ አዳዲስ ግጭቶች ለመፍጠር ተደጋጋሚ ሙከራ ላይ ነች።በሌላ በኩል እስካሁን ድብቅ ግብ እንዳለው የሚነገረው ሐጂ ጃዋር፣ ጊዜ በሄደ ቁጥር የቄሮ ወጣት በዶ/ር ዓብይ እና ለማ ላይ ያለው እምነት እየጠነከረ እንዳይሄድ እና የርሱን ስፍራ እና ድብቅ ግብ እንዳያሳጣው ከፍተኛ ስጋት ላይ ነው።ስለሆነም አዳዲስ ግጭቶች በኦሮም ማኅበረሰብ እና በቀረው ሕዝብ መሐከል መፍጠር ብቸኛ አማራጭ አድርጎ ይዞታል።ውጥረቶቹ ደግሞ ከፍተኛ ደረጃ ላይ እንዲደርሱ በሕዝብ የመኖር ህልውና ላይ ሁሉ ያለመ አደገኛ መንገዶችን ይከተላል።በእነኝህ ግጭቶች የቄሮ ወጣት እረፍት እንዳያገኝ እና ከሰከነ አስተሳሰብ ወጥቶ ሁል ጊዜ በስሜት ውስጥ እንዲሄድ ይፈለጋል።በስሜት ውስጥ ያለ ወጣት ደግሞ ወደፈለክበት መስመር ለመውሰድ ይመቻል።በስሜት ውስጥ ያለ ወጣት ከገደለ በኃላ የሚያስብ እና የሚነቃ እንስሳዊ ፀባይ ስለሚኖረው ለድብቅ ፅንፈኛ የፖለቲካ አጀንዳ አመቺ ይሆናል።

 በየትኛውም ዓለም ግልጥ ያልሆነ ፍላጎት እና ግብ ላላቸው እንደ ሐጂ ጃዋር ላሉ ግለሰቦች እረፍት የለሽ እና ተረጋግጦ የማሰብያ ጊዜ ያጣ በተከታታይ የግጭት አጀንዳዎች ውስጥ የተጠመዱ ወጣቶች አመቺ ናቸው።ሐጂ ጃዋር እና ቡድኑ የኦሮሞ ማኅበረሰብ ሁል ጊዜ ከሌላው ኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር በማያባራ የግጭት አጀንዳ ውስጥ እንዲገባ ሁል ጊዜ አዳዲስ አጀንዳ የሚሰጡት ለእዚህ ነው።ከእነኝህ አጀንዳዎች ውስጥ የአዲስ አበባ ሕዝብን ለመንቀል የሚደረገው ዛቻ አንዱ  እና ተጠቃሽ ምሳሌ ነው።በጦርነት ጊዜ የፉከራ ዋናው ግብ ስሜትን ቀስቅሶ በቀጥታ ወደ ጦርነት የማስገባት እንጂ የሰላም አስፈላጊነት መስበክ  እና ሌሎች መንገዶች አሉ ወይ? ብሎ አንድ ሰው እንዳያስብ የማጣደፍ ሥራ ነው የሚባለው ለእዚህ ነው።

ስለሆነም አሁን በኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን ላይ በሁለት በታኝ ኃይሎች  የተከፈተውን የሽብር ተግባርን ለማክሸፍ የማረጋጋት፣ሕዝብ እንዳይፈራ የማድረግ፣ለበታኝ ኃይሎች በውስጥ እየሰሩ የአዲስ አበባን ወጣት የሚያሳስሩትና ሌሎች ደባ የሚሰሩትን ተከታትሎ ማጋለጥ እና ለዶ/ር ዓብይም ሆነ ለለውጥ ኃይሉ እራስ ምታት ላለመሆን የመንግስትን ሥራ በቀጥታ ማገዝ ተገቢ ነው። ዶ/ር ዓብይ የአዲስ አበባን ወጣት አሳሰረ ከማለት፣ያሳሰሩትን አጣርቶ ማጋለጥ እና እስከመጨረሻው ተከታትሎ ለፍርድ እንዲቀርቡ ማንንም ሳይጠብቁ የራስን ድርሻ እስከመጨረሻው ድረስ መወጣት ያስፈልጋል።ዶ/ር ዓብይ እያንዳንዱ ፖሊስ ጣብያ የሚሰራውን ስህተት ሊደርስበት አይችልም።ሕዝብ ግን ይችላል።ለበታኝ ኃይሎች የሽብርተኛ ድርጊቶች እና የስነ ልቦና ጦርነቶች ምቹ አንሁን። 


ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ ''አማን ይሁን'' (ቪድዮ)
ከስር የምታዩት የድምፃዊ ዳዊት ፅጌ ዜማ ከፅሁፉ ጋር ግንኙነት የለውም 
ምንጭ : - ሆፕ ሙዚቃ ኢትዮጵያ ዩቱብ  




ጉዳያችን GUDAYACHN

 www.gudayachn.com

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...