ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, January 23, 2018

ለቤተ መንግሥቱም ሆነ ለቤተ ክህነቱ አልቅሱለት! ጥቁሩ ሰማይ እየመጣ ነው (የጉዳያችን ማስታወሻ)

በጽሁፉ መጨረሻ ላይ የቴዲ አፍሮ የባህር ዳር ኮንሰርት ቪድዮ ይገኛል።
ጉዳያችን /Gudayachn
ጥር 17፣2010 (ጃንዋሪ 24/ 2018 ዓም )

የኢትዮጵያ ፖለቲካ መዳረሻ ብዙዎቻችን እንደምንመኘው አለመሆኑ ግልጥ እየሆነ ነው።ብዙዎች የስርዓቱ አቀያየር የሰውም ሆነ የንብረት ጥፋት ከሁሉም በላይ ደግሞ የነበረውን ማኅበራዊ አንድነት በማይነካ መልክ ወይንም ጉዳቱ በቀነሰ መልክ ቢሆን የሚል ምኞት ነበራቸው።ህወሓት ግን በጥላቻ በተመረዘ ልቡ አስከሬን ከወለጋ እስከ ወልዲያ እያነጠፉ በመምጣት ብቻ ስልጣን ለማስጠበቅ ወስኗል።ሕዝብም የህልውና ጉዳይ ነው እና እራሱን ከመከላከል ከተሞቹን እና ገጠሩን ከህወሓት በዘር ጥላቻ ከተወጋ ሰራዊት ማፅዳት ብቸኛ መንገድ መሆኑን እያመነ የመጣበት ወቅት ነው።

በኢትዮጵያ የትኛውም መንግስታዊም ሆነ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ የህወሓት የመንደር ልጅ መሆን እንደ መስፈርት እየተወሰደ ድርጅቶቹን መቆጣጠር ከተጀመረ ሁለት አስር ዓመቶች አልፈውታል።ይህም በመሆኑ ከአሁን በኃላ የሥርዓት አካሄዶች እና ስለ ኢትዮጵያ ሲባል የነበሩ ጨዋነቶች ሁሉ የመጨረሻ እንጥፍጣፊ ደረጃ ላይ ደርሷል።

"ህወሓት እና የትግራይ ሕዝብ አንድ ነው" የሚለው አባባል ቀድመው የነገሩን ደጋግመው በየመድረኩ ላይ የሚዘፍኑልን የህወሓት ሲቪል እና ወታደራዊ አመራሮች ናቸው።እነርሱ ያሉትን ሌላው ሕዝብ ካነሳው ደግሞ "ዘረኛ" ይባላል።እሺ! ህወሓት እና የትግራይ ሕዝብ አንድ አይደለም ሲባል ደግሞ ሕዝቡን ከድርጅቱ ለመለየት ነው የሚል ነጠላ ዜማ ይለቀቃል።እውነታው ግን በኢትዮጵያ የሰፈነው የህወሓት የአፓርታይድ (የዘረኘንት) ስርዓት ከመቼውም በላይ የፋሽሽት ባህሪውን እየተፋ ነው።በቅርቡ በመቀሌ የተደረጉ የህውሓት ስብሰባዎች በስልጣን ለመቆየት በጅምላ መፍጀት የሚል እንደሆነ ያፈተለኩ መረጃዎች እንደደረሷቸው የሚናገሩ የመብዛታቸውን ያህል ከእሬቻ እስከ ነቀምት፣ከአምቦ እስከ ወልዲያ በህወሓት የተፈፀሙት የጅምላ ፍጅቶች ቤተ መንግሥቱም ቤተ ክህነቱም እንደማይተርፉ እና ጥቁሩ ደመና እየመጣ መሆኑን አመላካች ነው።

 ለቤተ መንግሥቱም ሆነ ለቤተ ክህነቱም አልቅሱለት! 

ላለፉት ዓመታት ለተፈፀሙት ግድያዎች ሀዘኑን በቅጡ መግለጥ ያቃታቸው ቤተ መንግስት እና ቤተ ክህነት ጥቁሩ ሰማይ እየመጣ መሆኑን መረዳት አለባቸው።የቤተ መንግሥቱም ሆነ የቤተ ክህነቱ ችግር እንደ ሸረሪት ድር ያደራባቸው የህወሓት ጎሳዊ መዋቅር እንጂ በእራሳቸው ያመነጩት እኩይ ባህሪ እንደሌለ ግልጥ ነው። ቤተ መንግስቱ ውስጥ ከምዕራብ አፍሪካ የፕሮቴስታንት ነቢይ ነን የሚሉ ግለሰቦች እያስመጡ ያስባረቁበት አቶ ሃይለማርያም እና አባ ዱላ ስለ እውነት ሊናገሩ ቀርቶ እበላ ባይ አንደበታቸውን ስርዓቱን ለማቆየት የውሸት ክምር ሲከምሩ በሃይማኖት ስም የቆሙ የአጋንንት ልጆች መሆናቸውን ነው በአደባባይ ያስመሰከሩት።

በሌላ በኩል በቤተ ክህነቱ በኩል ከፓትርያሪክ እስከ አጥብያ አስተዳዳሪ ከህወሓት መወለድ ብቻ እንደመስፈርት ተቆጥሮ ለሺህ ዓመታት ሕዝብ ከመንግስት እየዳኘች፣የፍትህ ምንጭ ሆና መሪዎችን በስነ ምግባር ብቻ ሳይሆን በአስተዳደር ጥበብ ሁሉ ስታንፅ የኖረች የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ልጆቿ ታቦተ ሕጉን በጥምቀት በዓል አጅበው ሲወጡ በመትረጌስ ሲፈጁ ድርጊቱን መቃወም አይደለም የፍትሐት ጸሎት የማያደርጉ ፓትርያሪክ እየመሯት መሆናቸው የታሪክ ቁስል ነው።ቤተ ክህነቱ እንደ አየር መንገዱ ተርሚናል ፈታሾች የስራ ቋንቋ ትግርኛ እስኪመስል ድረስ ከአጥብያ አጥብያ እየዞሩ የቤተ ክርስቲያን ገንዘብ መተዳደሪያቸው የሆኑ ህወሐታውያን ተግባር አሁን ላይ የመረረ ምላሽ ከህዝብ ሊያገኝ ጫፍ ላይ ደርሷል። የሚነሳውን ማዕበል የታንክ እና የመትረጌስ ጋጋታ አያድነውም።ቁስሉ የተዘጠዘው ሕዝብ ምንም አይነት ምድራዊ ኃይል አይመልሰውም።ህወሓትም ሕዝብ የሚያታልልበት ቃላትም ሆነ ሃሳብ አልቀውበት ባዶ አዳራሽ የሚንገላወድ ሰካራም ሆኖ ከወዲያ ወዲህ መንቆራጠጥ ብቻ ስራው ሆኗል።

ጥቁሩ ዳመና እየመጣ ነው

አሁን ለቤተ መንግሥቱም ለቤተ ክህነቱም አልቅሱለት።ሁኔታው ያስፈራል።ማስፈራት ብቻ ሳይሆን በስሜት የሚወሰደው የህዝብ እርምጃ ታሪካችንንም እንዳያጠለሽ ማሰብ ያስፈልጋል።በማሰብ ብቻ ግን የሚያስቀረው አንዳችም ነገር ያለ አይመስልም።አንድ ቀን ጧት ወይንም ቀትር ላይ አልያም ምሽት ላይ ፍልጥ የያዙ እናቶች፣አባቶች፣ወጣቶች እና ሕፃናት ሳይቀሩ በድንገት ቤተ ክህነቱም ሆነ ቤተ መንግስቱ በር ላይ ይደርሳሉ። ያን ጊዜ የሚፈልጉትን ሰው ያውቃሉ።በቤተ ክርስቲያን ገንዘብ መተዳደሪያቸው አድርገው  ቅምጥል ኑሮ እየኖሩ በነፃ ደፋ ቀና የሚሉትን የቤተ ክርስቲያኗን አገልጋዮች የምያስለቅሱት የት ናቸው ብሎ ግቢውን ይወረዋል።ያን ቀን የጥቁሩ ደመና ቀን ተብሎ ይጠራል።በእዚህ ቀን ፈድራል ፖሊስ ሆነ ህወሃታዊነት አይድንም። ያን ጊዜ የአቶ መለስን ፎቶ ከአቡነ ሺኖዳ እና አቡነ ጳውሎስ ጋር  የሰቀልኩ  ባለ ውለታ እኔ ነኝ ብሎ ማሽቃበጥ የለም።ያን ጊዜ በጠቆረ ሰማይ ስር አመልጣለሁ ማለት የለም። ይህ ቀን ያስፈራል።ፍትህ ሳያገኙ ሕዝብ እጅ የሚወድቁ ሊኖሩ ይችላሉ።

በተመሳሳይ ቤተ መንግሥቱም እንዲህ እንዳስፈራ አይኖርም።ሴቷ ማማሰያ ወንዱ ፍልጡን ይዞ ከመርካቶ ከኮተቤ ከእንጦጦ  እና ከተቀረው ክፍል ሕዝብ ይተማል። ያን ጊዜ የምዕራብ አፍሪካ የፕሮቴስታንት ነቢይ ተብዬዎች አያስጥሉም ። ፍትህ በሕዝብ እጅ በመውደቅ ምቾት እንደተሰማት በግልፅ ታውጃለች። በእርግጥ አሁንም ያስፈራል።ሆኖም ግን ስላላወራነው ይቀራል ማለት አይቻልም።ህወሓት በወልዲያ፣በአምቦ፣በሐረር ፣በሕር ዳር እና በጎንደር  ያደረገው ግድያ እና የጅምላ ጭፍጨፋ ይዘው የሚመጡት ይህንኑ ነው።ያን ጊዜ ለቤተ መንግሥቱም ሆነ ለቤተ ክህነቱ ግፈኞች አልቅሱላቸው። እውነታውን ከአሁኑ አውቆ መስመሩን የሚያስተካክል ቢኖር በአለቀ ሰዓትም ቢሆን እራሱን ያወጣል።ፍልጥ ግን ለቤተ መንግሥቱም ቤተ ክህነቱም ያሰጋዋል።ከእዚህ በፊት በጉዳያችን ላይ የተባሉት ነገሮች የማይደርሱ ሕልም የሜመስሏቸው ብዙዎች ነበሩ።ዛሬ ላይ ሆነው ሲመለከቱት ግን አይወቅሱም።የቤተ መንግሥቱም ሆነ የቤተ ክህነቱ ፍልጥ በያዘ ሕዝብ መከበቡ እና መመንጠሩ የማይቀር የቅርብ ጊዜ ክስተት አይሆንም ለማለት አያስደፍርም።

አዲስ ላይ ተከልክሎ ባህር ዳር ላይ የተፈቀደው የቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) የባህር ዳር ኮንሰርት  
ማስታወሻ : -ከላይ የቀረበው ፅሁፍ ከቴዲ አፍሮ ኮንሰርት  ጋር የተገናኘ አይደለም።


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments: