ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, September 15, 2017

በቅማንት ስም የታቀደው የድምፅ መስጠት ተንኮል እንዳይሳካ ማድረግ ትውልድን ከእልቂት መታደግ ነው።


ጉዳያችን / Gudayachn 
መስከረም 6፣2010 ዓም (ሴፕቴምበር 16፣2017 ዓም)


የጎንደር አብያተ መንግሥታት 

የእንግሊዝ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ቢቢሲ) መስከረም 5፣2010 ዓም በድረ ገፁ ላይ ''ከኦሮሞ እና ሱማሌ ክልል ግጭት ጀርባ ምን አለ?'' (What is behind clashes in Ethiopia's Oromia and Somali regions) በሚል ርዕስ በዘገበው ዜና ላይ ከግጭቱ ጀርባ የሚጠቀሰው አንዱ እና አይነተኛ ምክንያት እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2004 ዓም በ420 ቀበሌዎች በተደረገ የሕዝብ ውሳኔ ድምፅ መሰረት 80% የሚሆነው ቀበሌ ወደ ኦሮምያ መከለሉን እና እስከ አሁን ድረስ ለ10 ዓመት ወደ ተግባር አለመተርጎሙን ይገልጣል። ቢቢሲ እንደምክንያት ያደረገው ተግባራዊ አለምሆኑን ይበል እንጂ  የችግሩ መንስኤ ግን በህወሓት አስተባባሪነት በኦህዴድ እና አቻ የህወሓት ሸሪክ ድርጅቶች አማካይነት ህዝብን ከህዝብ ለማጋጨት የስርዓቱ አንዱ መንገድ ሆኖ እያገለገለ ያለው በአዋሳኝ ድንበሮች እየተፈለገ የድምፅ መስጠት ስርዓት አንዱ የግጭት ማስነሻ  የተለመደ ሥራ መሆኑን አመላካች ነው። የድምፅ መስጠቱ ተግባር በኦሮምኛ እና ሱማልኝ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን መካከል የግጭት ሰበብ ተደርጎ አንዱ የማጣያ መንገድ ከሆነ በመጪው እሁድ በጎንደር ቅማንት እና ዐማራን ለመለያየት በተሸረበ ተንኮል ድምፅ እንዲሰጥ የመወሰኑ አንዱ እና ዋና ዓላማ በኦሮምኛ እና ሱማልኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን መሃከል እንደተፈጠረው ያለ ግጭት መፍጠር እና ሕዝብ ደም እንዲቃባ ማድረግ እንደሆነ በሚገባ መረዳት ይቻላል። 

በጎንደር ሕዝብ መካከል ግጭት ፈጥሮ ሕዝቡን ወደማያባራ ግጭት ለመምራት የታቀደውን ድምፅ የመስጠት ሂደት በአሁኑ ጊዜ በጎንደር ሁሉም አካባቢ የሚኖር ሕዝብ በከፍተኛ ደረጃ ተቃውሞታል። ሕዝብ አንለያይም ህወሓት ደግሞ ተለያዩ ሙግት ጎንደርን በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ ከቷታል። እዚህ ላይ መገንዘብ የሚገባው በጎንደር የነበረው ቅራኔ የወልቃይት ጠገዴ አካባቢ ያለውን መሬት ወደ ትግራይ የመከለል እና ያለመከለል ጉዳይ እና የዐማራ ማንነት ይከበርልኝ ጥያቄ እንጂ የቅማንት እና ዐማራ ጉዳይ የሚል የግጭት አርዕስት ፈፅሞ የአካባቢው የልዩነት መነሻ እንዳልነበር ነው።ሆኖም ግን ህወሓት የሰሜን ጎንደርን ለሶስት ለመክፈል እና ቅማንት ከዐማራ እንዲለያይ የሚሰራ ድምፅ ሕዝብ እንዲሰጥ የሚል አጀንዳ የቀረፀው ከእዚህ በፊት በሁለቱ መካከል ልዩነት ለመፍጠር  ከማኅበራዊ ሚድያ እስከ ገጠር ወረዳ የሚገኙ ካድሬዎች በኩል ሙከራ አድርጎ ከከሸፈ በኃላ ነው። 

በጎንደር በመጪው እሁድ ህወሓት ያቀደው ህዝብን ከህዝብ የመለያየት እና የማያባራ ግጭት የመፍጠርያ እኩይ ተግባር ማሳካት ማለት ለአሁኑ ብቻ ሳይሆን ለመጪው ትውልድ መቃብር መቆፈር ማለት ነው። ይህ ማለት ቅማንት በቅማንትነቱ የእራሱ መብት እና ባህል የመጠበቅ መብት የለውም ማለት አይደለም። ሆኖም ግን ህዝቡ በሀገር ሽማግሌ እና ለሺህ ዓመታት በኖረበት ዘይቤ የሚያስፈልገውን መብት ከወንድሙ እና ባህሉን መለየት ከማይቻለው የዐማራ ሕዝብ ጋር በተመቸው መንገድ እና በሰከነ ሁኔታ የሚመክርበት እንጂ የህወሓት አደገኛ የዘር ፍጅት መንዣ መሳርያ ለመሆን አይፈቅድም። በቅማንት ስም የታቀደው የድምፅ መስጠት ተንኮል እንዳይሳካ ማድረግ ትውልድን ከእልቂት መታደግ ነው።በመጨረሻም የጎንደር ኅብረት የህወሓትን የመለያየት ድምፅ ውሳኔ አስመልክቶ የጎንደር ሕዝብ እንዲደርሰው በላከው አስራ ሶስተኛ መልዕክት ''የፋሽሽቱ ወያኔ ጎንደርን የመከፋፈል አደገኛ ዘመቻ ኢትዮጵያን የማፈራረስ የመጨረሻው ደወል ነው'' በሚል ርዕስ ስር ባስተላለፈው መልዕክት የድርጊቱ መክሸፍ ትውልድን መታደግ መሆኑን አበክሮ ባስነበበት አንቀፅ ማስታወሻዬን እገታልሁ።እንዲህ ይነበባል : -

''ህዝቡ መከፋፈልን አንሻም ብሎ የተቃወመዉን ሕዝባዊ አቋም ወያኔ ከቁም ነገር ሳይቆጥር፤ አብዛኛዉን የክልል ተወካዮችን ተቃዉሞ ድምጽ ቀልብሶ በማስፈራራት የሃይል የበላይነቱን ለማሳየት በፌደራል ስም ጎንደርን ለመከፋፈል የሚያካሂደዉ ዘመቻ የመጨረሻ የስራቱ መቃብር ሊሆን እንደሚችል እና እራሱን በራሱ ለማጥፋት እያፋጠነ መሆኑን እንደገና የሞት መርዶ እርሙን እንዲያወጣ በጥብቅ እናሳስባለን። ጎንደርን ሕዝብ ታሪካዊ አንድነት ጠምዝዞ በጉልበት ለማንበርከክ የሚፈጸም ተደጋጋሚ ሥልጣንን ተገን ያደረገ የጥፋት ዘመቻ ለትግራይ ነጻ አዉጭ ግንባር የሞት ከፈን ከመሆን ሌላ የጥፋት ሴራዉን ሊያሳካ አይችልም''' የጎንደር ኅብረት  ለጎንደር ሕዝብ ያስተላለፈው ቁጥር 13 መልዕክት (የፋሽሽቱ ወያኔ ጎንደርን የመከፋፈል አደገኛ ዘመቻ ኢትዮጵያን የማፈራረስ የመጨረሻው ደወል ነው። ይድረስ ለጎንደር ህዝብ ቁጥር 13)

ሕፃን ሳዶር የነገው ትውልድን ስሜት ታሳያለች 


ጉዳያችን GUDAYACHN 

 www.gudayachn.com

No comments: