ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, November 28, 2016

የኢትዮጵያ የውጭ ዕዳ ፣ ባለ እብነ በረዱ ህንፃ እና ኢትዮጵያን አጥፍቶ መጥፋት (የጉዳያችን አጭር ማስታወሻ)


ጉዳያችን/Gudayachn 
ህዳር 19፣2009 ዓም (ኖቬምበር 26፣2016)
==============================

የኢትዮጵያ የውጭ ዕዳ ጉዳይ 
====================
በ2016 እኤአ  ሰኔ ወር ላይ በተዘጋጀ ሪፖርት ኢትዮጵያ ከጠቅላላ ምርት  52% ለብድር ክፍያ እና ዋስትና የሚውል ሲሆን ከእዚህ ውስጥ 30% ለውጭ ብድር ዕዳ የሚከፈል ነው (ካፒታል ጋዜጣ፣ጥቅምት 17፣2016) የአሁኑ የኢትዮጵያ የውጭ ዕዳ በ2014 =16.59 ቢልዮን ዶላር ሲሆን በአንድ ዓመት ውስጥ በ2015=19.04 ቢልዮን ዶላር (ከ400 ቢልዮን ብር በላይ) ደርሷል (CIA world fact book report)  

እኤአ 2016 ሲጠናቀቅ ደግሞ ከ21 ቢልዮን ዶላር በላይ እንደሚሆን በእዚህ ዓመት የሰማናቸውን የብድር ስምምነቶች  ደምረን ማወቅ እንችላለን።በአንፃሩ የኢትዮጵያ ገንዘብ ንፁህ ወርቅ ሳይቀር (ባለፈው ሳምንት ህንድ ኒው ዴሊ የተያዘውን ወርቅ ጨምሮ) በባለስልጣናት እና ዘመዶቻቸው እየተመዘበረ ነው።

ባለ እብነ በረዱ ህንፃ
=============== 
ከእዚህ በታች የምታዩት ህንፃ አዲስ አበባ ከንግድ ሥራ ኮሌጅ ዝቅ ብሎ የሚገኘው የፀረ ሙስና ኮሚሽን ህንፃ ነው።አሁን መስርያ ቤቱ ጥርሱ ወልቆ ስለ ሙስና ማስተማር እንጂ መክሰስ አትችልም ተብሎ ተቀምጧል።አቶ ኃይለ ማርያም አንድ ሰሞን ስለ ሙስና ፉከራ ነገር ሲያሰሙ ነበር።ዛሬ አቶ ደብረ ፅዮን ባልተስተካከለ አማርኛ ስለ ጥልቅ ተሃድሶ እያሉ ኢትዮጵያ በአራቱም አቅጣጫ ስትዘረፍ ዜማ እያወጡላት ነው። የኢትዮጵያ የውጭ ዕዳ በታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ ጨምሮ ብዙዎች ባለስልጣናት በውጭ ሃገራት በሚልዮን ዶላር እያጋበሱ ነው።የባለስልጣናት ልጆች ከኢትዮጵያ በሚላክ የውጭ ምንዛሪ በሚል ቅለድ ውጭ ሀገር ይኖራሉ፣ይነግዳሉ።ኢትዮጵያ ግን በዕዳ ተዘፍቃ፣ተቆጣጣሪ የሌለባቸው የዘመኑ ባለስልጣናት ይንደላቀቃሉ ሲፈልጉ ከመኪና መኪና ያማርጣሉ።
















ኢትዮጵያን አጥፍቶ መጥፋት 
===================
የኢትዮጵያ ውጭ ዕዳ ለትውልድ በሚተርፍ መልኩ እየጨመረ ነው።አሁን ዝርፍያው በኮማንድ ፖስቱ ደረጃ ተደራጅቶ ወደ እያንዳንዱ ሰው ቤት እየወረደ ነው።የኢትዮጵያውያን ቤት ልክ ደርግ በ1960ዎቹ መጨረሻ እንደሚያደረገው ቤት በማንኛውም ጊዜ ይበረበራል። ፈታሹ ያገኘውን ዕቃ የመውሰድ መብት አለው።ብዙዎች ጥሬ ገንዘብ ሳይቀር ከቤታቸው በኮማንድ ፖስቱ ተዘርፎባቸዋል። የሚጠፋው የሰው ሕይወት እና የታሰረው ወጣት ቁጥር የትዬለሌ ነው።ይህ ሁሉ ሆኖ የኢትዮጵያ ንግድ ሚዛን ተዛብቶ ቀውስ ተባብሷል።ኩባንያዎች ሰራተኞች እያባረሩ ነው። ለስርዓቱ ቅርብ የሆኑት እንደ ተክለ ብርሃን አምባዬ ኮንስትራክሽን ሳይቀሩ 400 ሰራተኛ የቀነሱት በቅርቡ ነው። ቱሪዝም በአስደንጋጭ ደረጃ ቀንሷል።

የቡና አቅርቦት ለአንድ ዓመት ያህል በኦሮምያ በተነሳ ሕዝባዊ ማዕበል ቀንሷል።በርካታ ኩባንያዎች ኢትዮጵያን እየለቀቁ እየሄዱ ነው።በሰሜናዊ የኢትዮጵያ ክፍል ጦርነት መከፈቱ ከተነገረ ሰነበተ።ይህ ማለት ሕወሓት የመከላከያ እና ደህንነት በጀት የበለጠ ያወጣል ማለት ነው።ይህ በደከመው የኢትዮጵያ ምጣኔ ሀብት ላይ ድህነቱ እና የዋጋ ንረቱን ያብሰዋል።ለእዚህ ሁሉ ቀውስ መነሻው የሕወሓት የስልጣን ጥማት አለመርካት ነው።ኢትዮጵያን አጥፍቶ መጥፋት የሚለው የሕወሓት መንገድ አደገኛ ነው። የኢትዮጵያ ሕዝብ በጎሳ እና መንደር መከፋፈል ትቶ ለኢትዮጵያ በአንድ ልብ መነሳት ያለበት ጊዜ አሁን ነው።ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል እና ከአጥፍቶ ጠፊ ለመታደግ የእያንዳንዱ ሰው ኃላፊነት ነው።

ጉዳያችን GUDAYACHN

 www.gudayachn.com

No comments: