ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, August 23, 2016

ለኢትዮጵያ ድምፃውያን በሙሉ! አፋጣኝ መልዕክት


በአዲስ አበባ የኢትዮ-ፍራንስ አልያንስ በኢትዮጵያ ሙዚቃ ዙርያ በተለይ ባህላዊው ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ፅሁፎች እና ታዋቂ ድምፃውያንን እየጋበዘ ሽልማት ይሰጥ እንደነበር አስታውሳለሁ።በአንድ ወቅት ለምሳሌ ጋሽ መሐሙድ አህመድ የአንድ ዓመት እንግዳ ነበር።ከጥቂት አመታት በፊትም አሁን ዓመተ ምሕረቱን ባላስታውሰውም፣ በእዚሁ ዝግጅት ላይ አንዲት ፈረንሳዊት የኢትዮጵያ አዝማሪን በተመለከተ አንድ ፅሁፍ ማቅረቧን አስታውሳለሁ።በእዚህ ፅሁፍ ላይ ከጥንት ጀምሮ አዝማሪ በሕበረተሰቡ መልካም ግንኙነት ላይ ያለውን ሚና በዝርዝር ካቀረበች በኃላ አዝማሪን ስትገልፀው እንዲህ አለች።
      ´´ አዝማሪ በኢትዮጵያ በፖለቲካም ሆነ በተለያዩ ምክንያቶች የልዩነት ስፋቶች ሲመጡ ይህንን የልዩነት ክፍተት የሚሞሉት አዝማሪዎች ነበሩ´´ብላለች። አባባሉን በደንብ አስፍተን ብናየው ከብዙ አቅጣጫ በደንብ መፈተሽ ይቻላል።

ይህች ማስታወሻ ግን የኢትዮጵያ ድምፃውያን 
- የኢትዮጵያን ሕዝብ አንድነት፣
- የቀደመ እና አሁን መጉላት ያለባቸው የሕዝብ ፍቅር፣
- ኢትዮጵያዊነት፣ 
- በጎጥ መከፋፈል ያለውን አደጋ ወዘተ ላይ ያተኮሩ አዲሱን ትውልድ ሊያስተምሩ የሚችሉ የኪነት ስራዎች መስራት እንደሚጠበቅባቸው አበክሮ ለማሳሰብ ነው።ወጣቱ ትውልድ ሊሰማቸው እና ጎጠኝነትን እንዲጠላ ሕብረት፣ፍቅር እና በነፃነት መኖር  የነገ የኢትዮጵያን ሕይወት ብሩህ የሚያደርግ መሆኑን ሁሉ ማሳየት አሁንም ከከያንያኑ ይጠበቃል።በአገር ቤት ያሉ ከያንያን በተለይ አንጋፋዎቹም እንደገና ማይክ የምታነሱበት እና ስለ ኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነት የምታስተምሩበት ጊዜ ነው።ባለፈ ዘመን ጥሩነት እያሰቡ ከንፈር መምጠጥ አንዳች አይፈይድም።

ይህ ትውልድ በማህበራዊ ድረገፆች አንዴ ኦሮሞነትን ብቻ ሌላ ጊዜ አማራነት ብቻ፣በተደራጀ መንግስታዊ መልክ ደግሞ ትግራይነትን ብቻ በጆሮው ላይ እየጮሁበት ኢትዮጵያዊነት ሳይጎላ እየቀረ የታሪክም ሆነ የትውልድ ተጠያቂ እንዳትሆኑ አስቡበት።እኔ እንደማስበው ከላይ በተጠቀሱት ሃሳቦች ዙርያ አዳዲስ ነጠላ ስራዎችን ለማውጣት ስሜቱ፣ቁጭቱ እና ከጉዳዩ አጣዳፊነት አንፃር ሲታይ በቀናት ውስጥ ሰርታችሁ ማድረስ ያለባችሁ ይመሰልኛል።

በመጨረሻም አንዲት የቴዎድሮስ ካሳሁንን (ቴዲ አፍሮ)  የዜማ ስንኝ ብቻ በመምዘዝ ምን ያህል በሕዝብ ዘንድ ኃይለኛ እና አዎንታዊ ስሜት እንደፈጠረ በናሙናነት ላንሳ። 

´´ ተስማምቶ የሚኖረው እስላም ክርስቲያኑ፣
    ተዘነጋሽ እንዴ ኢትዮጵያ መሆኑ ´´

ይህ ስንኝ ቴዲ አፍሮ ከዘፈነው በኃላ አዲሱ ትውልድ ላይ እስልምና እና ክርስትና  ኢትዮጵያ ውስጥ ያላቸው ግንኙነት ከሌላው ዓለም የተለየ መሆኑን በማስተማር ደረጃ የእራሱን በጎ አሻራ ጥሎ አልፏል።ይህ ማለት ቀድሞ አይታወቅም ለማለት ሳይሆን የኪነት ሰዎች በጎ ግንኙነታችንንም አጉልተው እና አስፍተው ሲያሳዩ ሕዝብ በበጎ ግንኙነቱ ይበረታታል።በሌላ በኩል ሕዝቡን ሊለያዩ የሚፈልጉ በጎጥ ሲከፋፍሉት እና ከያንያን ይህንኑ ወቅሰው ስራቸውን ሲያቀርቡ አጥፊም እጁን ይሰበስባል። ስለሆነም የኪነት ሰዎች ከእናንተ ብዙ ይጠበቃል።ኢትዮጵያ መከራ ላይ ሆና አንዳች ሳትሰሩ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከእዚህ ፈተና የወጣ ጊዜ የድል አጥብያ አርበኛ ብትሆኑ ሕዝብ አይቀበላችሁም። 



ጉዳያችን GUDAYACHN www.gudayachn.com

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።