ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, July 28, 2016

ሰልፍ ከወጣህ መድረሻ ግብ ይዘህ ውጣ! ህወሓት የህዝብን የተነሳሳ የአንድነት ስሜት በሰልፍ ማቀዝቀዝ ለምዷልና።



በአሁኑ ሰዓት የኢትዮጵያ ሕዝብ በህወሓት የ25 ዓመታት አድሏዊ፣ጎጥ ላይ የተመሰረተ እና ኢትዮጵያን የሚከፋፍል አመራር ለመላቀቅ ሰዓታት እረዝመውበታል።በርካታ የማታለል ተግባራት የተፈፀመበት ሕዝብ እየመሩት ያሉት መሪዎች በመጀመርያ ደረጃ ጎጠኞች መሆናቸውን ተረድቷል፣ በመቀጠል ለኢትዮጵያ አንዳች የዜግነት ስሜት የማይታይባቸው ይልቁንም ከባዕዳን እኩል ለኢትዮጵያ ስጋት እንደሆኑ እና ለግል ብልፅግና ሌት ከቀን የሚደክሙ መሪዎች መሆናቸውን በሚገባ ተረድቷል።

ከመጪው እሁድ ጀምሮ  በጎንደር፣ባህርዳር፣ደሴ እና ሰሜን ሸዋ እንዲሁም በኦሮምያ ከተሞች ሰልፍ እንደሚደረጉ በማኅበራዊ ድረ-ገፆች እየተገለፀ ነው።በተለይ በጎንደር የሚደረገው ሰልፍ ከትናንት በስትያ አቶ በረከት እና የስርዓቱ ቁልፍ ሰዎች በተገኙበት የተደረገው ስብሰባ ካለ አንዳች ፍሬ የህዝቡን ቁጣ በጨመረ መልክ ከተጠናቀቀ በኃላ የጎንደር እና የአካባቢው ሕዝብ በመጪው እሁድ ሰልፉ ተፈቀደም አልተፈቀደም ሰልፉ እንደሚካሄድ ህዝቡ በቁጣ እየገለፀ ነው። በኦሮምያ ከተሞች ይህንን ሳምንት የመረረ ተቃውሞ ሲደረግ ነው የሰነበተው።

እዚህ ላይ መስመር ያለበት ጉዳይ ሰልፍ ማድረግ በራሱ ግብ አለመሆኑን ነው። ህወሓት የህዝብ ስሜት በከባዱ ሲነሳ አንዱ የማብረጃ መንገድ ያደረገው ሰላማዊ ሰልፍ ነው። በሊብያ በአሸባሪው አይ ኤስ ኤስ በተገደሉት ወገኖቻችን ሳብያ የህወሓት ቸልተኝነት ያስቆጣው ሕዝብ በእራሱ ተነስቶ ሰልፍ ለማድረግ መቁረጡን ያወቀው ህወሓት የህዝብን ስሜት ያበረደው በሚቀጥለው ቀን ሰልፍ እንደሚደረግ በመፍቀድ ነበር። ሰው የቁጣው ስሜት ባየለበት ወቅት ስሜቱን በከፍተኛ ድምፅ ማውጣት ይፈልጋል።ይህ በእራሱ ችግር የለውም።ነገር ግን በአደባባይ በመውጣት በመጮህ እና ሰውነትን በላብ በመዝፈቅ ብቻ አምባገነኑ ስርዓት ይወገዳል ማለት አይደለም። ደግሞስ ያለውን ችግር አደባባይ መድገም ህወሓት ያላወቀውን እንዲያውቅ መረጃ ለመስጠት ነው? ህወሓት ማለት እኮ በሕዝብ እንባ ላይ እየተራመደ የሕፃናት እና የእርጉዞችን ሰቆቃ በጥይት ዝም እያስባለ በእየአውራ ጎዳናው አስከሬን ያስቆጠረ ስርዓት በሰላማዊ ሰልፍ ከስህተት ይማራል ተብሎ አይታሰብም።ይህ ማለት የተቃውሞ ሰልፍ አያስፈልግም እያልኩ አይደለም። ሰልፍ መድረሻ ግብ ይዞ ይነሳ ማለት ነው የፈልኩት።

በመጪው ዕሁድ የሚደረገው ሰልፍ በአደባባይ በመጮህ ስሜትን በመግለፅ ብቻ እርካታ አግኝቶ ወደ ቤት የሚገባበት ሳይሆን ነፃነት የሚታወጅበት ቀን መሆን አለበት።  ህወሓት በሰላማዊ የህዝብ ድምፅ የአገር ችግር እንደማይፈታ ባለፉት አመታት የታየ እውነታ ነው። ህወሓት በገዛበት የጭካኔ አገዛዝ ዘመኑ ሁሉ የደነገጠባቸው እና የስልጣን መንበሩን ያነቃነቁ የህዝብ እንቅስቃሴዎች የታዩት በኦሮምያ እና በጎንደር የተደረጉት ናቸው። ሁለቱም እንቅስቃሴዎች የሕወሀትን አምባገነናዊ እና ጎጥን  መሰረት ያደረጉ የአስተዳደር መዋቅሮቹ ተናግተዋል።ሁለቱም እንቅስቃሴዎች በአሁኑ ሰዓትም ያልተቆጣጠራቸው ከመሆናቸውም በላይ በመጪው ጊዜ ለማፈን ሌላ ስልት እያሰላሰለባቸው እንደሆነ ከእራሱ የሚወጡ መረጃዎች ያሳያሉ።

ስለሆነም በመጪው እሁድ የሚደረጉ የተቃውሞ ሰልፎች ምን መምሰል አለባቸው?

1/  ሕዝብ በአደባባይ የህወሃትን ስርዓት ለመጣል ቃል የሚገባበት  መሆን አለበት
የሃይማኖት አባቶች፣ሽማግሌዎች እና ታዋቂ ግለሰቦች በሰልፉ ላይ  የኢትዮጵያ ሕዝብ ሰቆቃ መቆም እንዳለበት፣በዘር እና በጎሳ መከፋፈል የህወሓት መርዘኛ ፖለቲካ ኢትዮጵያን እንደ አገር የማያስቀጥል መሆኑን ማስረዳት እና ከህወሓት ጋር የሚተባበር ሁሉ የተወገዘ እንዲሆን የሚያውጁበት መሆን አለበት።

2/ ተቃውሞው የትግራይን ሕዝብ ኢላማ ያደርገ ሳይሆን ህወሓትን እና የጥቅም ተካፋዮችን ብቻ እና ብቻ ያለመ መሆኑን ማሳየት አለበት


ህወሓት 25 ዓመታት ሙሉ ላፈሰሰው ደም የትግራይ ሕዝብ እንደ ሕዝብ እንዲጠየቅ ለማድረግ እና በትግራይ ሕዝብ ላይ ተንጠላጥሎ ከቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር በማጋጨት እና በማስበርገግ የስልጣን እድሜውን ማራዘም ይፈልጋል።ይህንን በተለይ ከ1997ዓም ምርጫ ጀምሮ አጠንክሮ ሲሰራበት የነበረ እና በሚቆጣጠራቸው የመገናኛ ብዙሃን በርካታ መርዛማ ፕሮግራሞችን ሲያስተላልፍ እንደነበር ሕዝብ ምስክር ነው።በእዚህም ሳብያ አንዳንድ የዋህ የትግርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን ይህንኑ ሲያስተጋቡ ይታያሉ። የእዚህ አይነቱ ሰልፍ ላይ ህወሓት ሕዝብ ከህዝብ ለማጋጨት የሚሞክርባቸውን መንገዶች ሁሉ ቀድሞ ማክሸፍ ያስፈልጋል።ለምሳሌ ከሰልፉ አላማ ውጭ የሆኑ የትግራይ ህዝብን የሚያጥላሉ መፈክሮች የሚያሰሙ ካድሬዎች በሕዝቡ ውስጥ ከማሰማራት ጀምሮ የእርስ በርስ ግጭት እንዲነሳ እና  አንዱ ሕዝብ በሌላው ላይ መሳርያ የመዘዘ አስመስሎ ሊያቀርብ ይችላል።ስለሆነም ሰልፎቹ እነኝህን እና የመሳሰሉትን የህወሓት ተንኮሎች የሚያከሽፉ መሆን አለባቸው።


3/ የኢትዮጵያን ጦር ኃይል እና ፖሊስ ሰራዊት የህወሓት የጎጥ ፖለቲካ አስፈፃሚ መሆኑን እንዲያቆም የሚያስጠነቅቅ መሆን አለበት


በኢትዮጵያ ዘመናዊ የጦር ኃይል አደረጃጀት ታሪክ ባልታየ መልኩ ከአንድ አካባቢ የመጡ ሰዎች የጦር  ኃይሉ ከፍተኛ መኮንኖች የሆኑበት ጊዜ በህወሓት ዘመን ብቻ ነው።ይህ ማለት ግን ተራው ወታደር በሙሉ እንደ ከፈተኛ መኮንኖች በጎጥ ፅንፍ ብቻ የሚያስብ ነው ማለት አይደለም።እንደማንኛውም ኢትዮጵያውያዊ የኢትዮጵያ ጉዳይ የሚያሳስበው የስርዓቱ  ጥቂት ቅምጥል ባለስልጣናት ዝርፍያ እና በትውልድ መንደራቸው የሚያስቡ ዘረኞች የስልጣን ጥማት ኢትዮጵያን ወደማትመለስበት  አደጋ እየመራት እንደሆነ ይረዳል።ይህ ሰልፍ ይህንን ሰራዊት ኃላፊነቱን እንዲወጣ የሚያሳስብ እና ይህንን ካላደረገ ግን ከህዝብ ፍርድ እንደማያመልጥ ግልፅ መልዕክት የሚያስተላልፍ መሆን አለበት።


ባጠቃላይ ከእንግዲህ ወዲህ በኢትዮጵያ የሚደረጉ የተቃውሞ ሰልፎች ከእዚህ በፊት ከሚደረጉት ሰልፎች የተለዩ እና የህወሓትን ባህሪ ከግንዛቤ መሆን አለባቸው።ሰልፍ ከወጣህ መድረሻ ግብ ይዘህ ውጣ! የህዝብን የተነሳሳ የአንድነት ስሜት ህወሓት በሰልፍ ማቀዝቀዝ ለምዷልና።

ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments: