ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, February 12, 2016

''አርጋኖን'' እና ''ኦርጋን'' ምን አገናኛቸው? ሰውን እንፈር፣እግዚአብሔርንም እንፍራ! (የጉዳያችን ማስታወሻ)

ኦርጋን የሙዚቃ መሳርያ 
   
   
       የአባ ዘጊዮርጊስ ድርሰት መፅሐፈ አርጋኖን  


ባለፈው ሰሞን ከወደ አሜሪካ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አውደ ምህረት ላይ ''በኦርጋን መዘመር ይቻላል''።የሚል እንግዳ ንግግር ተሰምቷል።የምንኖረው በምዕራቡ ዓለም ነው እና ማንም የመሰለውን ሃሳብ መስጠት ይችላል።ሆኖም ግን አሁንም የምንኖረው በምዕራቡ ዓለምም ነውና ማንም ግን ካለማንም ፍላጎት የግል ሃሳቡን በሌላ ላይ መጫን አይችልም። ስለ ኦርጋን የተነገረው  ከግል አስተያየትነት አያልፍም።ይህ ማለት ግን ትክክል ነው ማለት ግን አይደለም።ስንት የሚሰራ ሥራ ያላትን ቤተ ክርስቲያን ከስርዓቷ ውጭ የሆነ ተግባር እንድትፈፅም ለመጫን መሞከር መዘዙ ብዙ ነው።

አገረ አሜሪካ፣ ይሄው ሃሳብ የተሰነዘረባት አገር በርካታ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት የሚገኙባት ነች።በተለይ በስደት የሚገኙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ፓትርያሪክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ከሁለት አስርተ ዓመታት በላይ በስደት የሚገኙት አሁንም አሜሪካ ነው።አቡነ መርቆርዮስም ሆኑ በስደት የሚገኘው ሲኖዶስ ኦርጋን በየቤተ ክርስቲያን ይግባ የሚል ውሳኔ አላሳለፈም። በአገር ቤት የሚገኘው ሲኖዶስ ይልቁንም ከሃያ አመታት በፊት የቤተ ክርስቲያኒቱ የመዝሙር መሣርያዎች ምን ምን እንደሆኑ ለይቶ በቀኖና (ህገ ቤተክርስቲያንነት)  ወስኗል። በሁለቱ ማለትም በውጭ እና በአገር ቤት በሚገኙ አባቶቻችን መካከል ምንም አይነት የሃይማኖታዊ ዶግማዊም ሆነ ቀኖናዊ ልዩነት የለም።በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንም መሰረታዊ የሆነ የልዩነት ነጥብ አልተከሰተም።በእርግጥ በአንዳንድ አጥብያዎች ስርዓተ ቤተ ክርስቲያን ከሚፈቅደው ውጭ የሚታዩ ማዘንበሎች የአገር ቤቱንም ሆነ በውጭ በስደት የሚገኘውን ሲኖዶስ መገለጫ ሊሆኑ አይችሉም።

እውነታው እንግዲህ ይህ ሆኖ ሳለ በአሜሪካን አገር ስለ ኦርጋን በአውደ ምሕረት አንድ አባት ተናገሩ ተብሎ እንደ ስርዓት የተደነገገ ያክል የሚናገሩ  እና  አልፈው ተርፈውም ኦርጋንን ከአባ ዘጊዎርጊስ ድርሰት ጋር እያመሳሰሉ የሚፅፉ ግለሰቦች ሰው ይታዘበናል አለማለታቸው እየገረመኝ ነው።

ከሁሉ በፊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስርዓት ቀኖና በአስተያየት፣በአውደ ምህረት ላይ ንግግር ወይንም አንድ አባት ስለፃፈ ሕግ ይሆናል ማለት አይደለም።በአገራችን አንድ ባህታዊ ከቤተ ክርስቲያን ደጅ ላይ ከወገቡ በላይ እራቁቱን ሆኖ እራሱን በሰንሰለት እየገረፈ የሚናገረውን እንደ ሲኖዶስ ውሳኔ የሚወሰድበት አጋጣሚ መኖሩ በእራሱ አሳዛኝ ሆኖ ሳለ በውጭ የሚኖረው ምዕመን ሕግ እና ስርዓት ቤተ ክርስቲያኒቱ በማን እና እንዴት እንደምታወጣ የማያውቅ ይመስል ኦርጋን እና አርጋኖን እየተባለ ሲወናበድ ማየት አሳዛኝ ነው።አሁን አሁን  የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን አርጋኖን የተሰኘውን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚያመሰግነውን መፅሐፍ  ኦርጋን ከተባለው የሙዚቃ መሳርያ ጋር እያመሳሰሉ የሚፅፉ ሰዎች ለህሊና የሚከብድ ውሸት ሲዋሹ መመልከት ተለምዷል።

ይህንን ፅሁፍ እንድፅፍ ያነሳሳኝ ዛሬ በማኅበራዊ ድረ-ገፅ ላይ ያነበብኩት አንድ ፅሁፍ  በርካታ በተረታ ተረቶች  የተሞሉ ፅሁፎች ታጭቆበት ስለተመለከትኩ ነው።ለነገሩ ተረት ብቻ ሳይሆን ''አይን ያወጣ'' በሚባል ደረጃ በውሸት የተሞላ ነው። ከፅሁፉ ውስጥ ሶስቱን ውሸቶች ብቻ ልጥቀስ:-

ውሸት አንድ - ''ኦርጋን የመዝሙር መምነሽነሽያ ነበር''

ውሸት ሁለት -''ኦርጋን ከአባይ ዳር ነው የተገኘው''

ውሸት ሶስት -''ቅዱስ ያሬድ ቅዱስ ኤፍሬም እና አባ ሕርያቆስ ኦርጋን ይጠቀሙ ነበር።ቅዱስ ያሬድ ኦርጋን ብሏል።'' የሚሉ ይገኙበታል።

እዚህ ላይ ኦርጋን የተባለውን የሙዚቃ መሳርያ ከአሥራ አራተኛው ክ/ዘመን ኢትዮጵያዊው ሊቅ እና ቅዱስ አባ ዘጊዮርጊስ ዘጋስጫ ድርሰት የሆነው ''አርጋኖን'' ጋር አንድ ነው የሚለው አባባል ሌላው አስቂኝ የማሞኛ ግን ደግሞ ምንም የማያውቁ ምዕመናንን ለማሳሳት የሚሞከረው ሙከራ  አደገኛ መሆኑን መግለጡ ተገቢ ነው።ለመሆኑ ኦርጋን የሙዚቃ መሳርያ ከሆነ አርጋኖን ምንድነው? 

ስለ አርጋኖን እና አባ ጊዮርጊስ የተፃፈው ፅሁፍ እንዲህ ይነግረናል:-

''የአባ ዘጊዮርጊስ ዘጋስጫ የመጀመርያው ድርሰቱ አርጋኖን  የተሰኘውና በቅኔ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የሚያመሰግነው መጽሐፉ ነው፡፡ ስለ አርጋኖን ድርሰቱ ገድሉ በሚከተለው መንገድ ይገልጠዋል «ወሰመዮ በሠለስቱ አስማት ዘውእቶሙ አርጋኖነ ውዳሴ፣ ወመሰንቆ መዝሙር ወእንዚራ ስብሐት - በሦስት ስሞችም ሰየማቸው እነርሱም አርጋኖነ ውዳሴ፣ መሰንቆ መዝሙርና እንዚራ ስብሐት  ይባላሉ፡፡» ይህ አገላለጥ አንድ ነገር እንድናስተውል ያደርገናል፡፡ ይሄውም ስለ አርጋኖን መጽሐፍ ይዘት ነው፡፡ በገድሉ ላይ አርጋኖን መጽሐፍ አንድ ሆኖ ሦስት ክፍሎች ያሉት ነው፡፡ .... አርጋኖን ከሰኞ እስከ ዓርብ ላሉት ዕለታት ተከፋፍሎ የተዘጋጀ ሲሆን፣ እንዚራ ስብሐት ግን ከ«ሀ » እስከ «ፖ» ያሉትን ፊደላት በመክፈያነት በመጠቀም የተዘጋጀ ነው፡፡ ይህም አርጋኖንን አባ ጊዮርጊስ ሲያዘጋጀው አንድ ሆኖ በኋላ ግን በየክፍሉ እየተጻፈ የተባዛ ይመስላል፡፡እመቤታችን አርጋኖንን ስለ ወደደችለት ዚማት  በሚባለው ሀገር በነበረ ጊዜ «ከድርሰቶችህ ሁሉ እንደ አርጋኖን የምወደው የለም»  ብላዋለች፡፡ ዐፄ ዳዊትም ድርሰቱን በጣም ከመውደዱ የተነሣ በወርቅ ቀለም እንዳጻፈው ገድሉ ይገልጣል፡፡አባ ጊዮርጊስ የተወለደው በ1357 ዓም ነው።ወላጆቹ ልጅ ስለሌላቸው ዘወትር እያዘኑ ይኖሩ ነበር።አባ ጊዮርጊስ የተወለደው በቅዱስ ዑራኤል ብስራት መሆኑን ድርሳነ ዑራኤል ይተርክልናል።'' +


ኢትዮጵያዊ ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ 

ስለዚህ አርጋኖን ድርሰት ነው።ኦርጋን ደግሞ የሙዚቃ መሳርያ ነው። አሁን በ21ኛው ክ/ዘመን ሰዎች እንዲህ የማይገናኙ ነገሮችን አምታተው ፅፈው ሕዝብ ያታልላሉ ብሎ ማን ይጠብቃል? እየሆነ ያለው ግን ይህ ነው።

የኦርጋንን የሙዚቃ መሳርያ በተመለከተ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር አያይዞ የተሰጠው አስተያየት ጋር ተዛምዶ በማኅበራዊ ድረ-ገፅ የሚፃፉትን በተመለከተ መታወቅ ያለባቸው ሶስት ነጥቦችን አንስቼ ፅሁፌን ልደምድም።

1/ ቤተ ክርስቲያን መድረክ ላይ በሚሰጡ የግል ሃሳቦች ቀኖና አትቀንንም 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የምትመራባቸው መሰረታዊ መመርያዎች ምንጮች ሁለት ናቸው።አንዱ መሰረተ እምነቷ የሆነው ዶግማ ሲሆን ሁለተኛው አባቶች የሰሩላት ሥርዓቷ ወይንም ቀኖና ነው።

ዶግማን ሐዋርያውቅዱስ ጳውሎስም “ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥ ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥ የተረገመ ይሁን።አስቀድመን እንዳልን እንዲሁ አሁን ሁለተኛ እላለሁ፥ ከተቀበላችሁት የተለየውን ማንም ቢሰብክላችሁ የተረገመ ይሁን። ” በማለት እንዳወገዘው (ገላ፩፣  -) ማንም ማን ቢሆን የማይቀይረው መሰረተ ዕምነት ነው።ለምሳሌ የክርስቶስ ፍፁም አምላክነት ዶግማ ነው።ቀኖና  ግን የቤተ ክርስቲያኒቱን መሰረተ ዕምነት፣የመፅሐፍ ቅዱስ ትዕዛዛትን እና ቀደም ያሉ የቅዱሳን አበው ድንጋጌዎችን መሰረት አድርጎ የተሰራ ነው። ቀኖና በአውደ ምሕረት ላይ አንድ አባት ሃሳብ ስለሰጡ ''አይሻሻልም'' አሁንም የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ይፈልጋል።ቅዱስ ሲኖዶስ ደግሞ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ስለሚመራ የሚወስናቸው ውሳኔዎች በዘፈቀደ አይደለም።

በመሆኑም የኦርጋን ጉዳይ በውጭ ባለው ሲኖዶስም ሆነ በአገር ቤቱ ሲኖዶስ  የቤተ ክርስቲያን መሳርያ ነው የሚል ነገር የለም።ይልቁንም በአገር ቤት ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ መሳርያነት ተቀባይነት አላገኘም።በአገር ቤት እና በውጭ ባለው ሲኖዶስ መካከል ደግሞ የዶግማም ሆነ የቀኖና ልዩነት የለም።ይህንን በሁለቱም በኩል ያሉ አባቶች ደጋግመው ተናግረዋል።

2/ ኦርጋንን የሚከለክለው ማኅበረ ቅዱሳን ነውን ?

አሁን አሁን የተያዘው ፈሊጥ ኦርጋንን የሚከለክለው ማኅበረ ቅዱሳን ነው የሚል ነው።እንግዲህ ይህንን ለመረዳት በተራ ቁጥር አንድ ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንዴት ስርዓት እንደምታወጣ ከተመለከትን ከቤተ ክርስቲያን መዋቅር ስር በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ ስር የሚገኘው ማኅበረ ቅዱሳን በምን ስልጣኑ ነው ስለ ቀኖና መቀነን ሥራ ገባ የተባለው።ደግሞስ በእዚህ ዘመን ስንት ያላመኑ ለማሳመን እንደመጣር በእየጭፈራ ቤት ማድመቅያ የሆነውን የሙዚቃ መሳርያ ከቤተ ክርስቲያን ካልገባ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ ምን የሚሉት ፈሊጥ ነው? በእዚህም ሳብያ የቤተ ክርስቲያን ሌላ እራስ ምታት ለመሆን መሮጥ ምን አይነት አለመታደል ነው?

3/ ለምን ኦርጋን ተፈለገ?

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋኅዶ ቤተ ክርስቲያን ኦርጋን እንድትጠቀም የሚወተወትበት በተለይ በባእዳን በኩልም ጭምር የሚቀነቀነው ከሶስት ፍላጎቶች አንፃር ነው።
አንደኛው የቤተ ክርስቲያንም ሆነ የኢትዮጵያ መለያ እና ብቸኛ ባለቤት የሆነው የያሬዳዊ ዜማን ለማስጣል እና አገሪቱን ካለ አንዳች መለያ ማስቀረት፣ 
ሁለተኛ፣ በእዚህ ሳብያ የኢትዮጵያ ታሪክን በዋናነት የያዘችው ቤተ ክርስቲያንን መሰረታዊ መለያ መበረዝ የኢትዮጵያን ህልውና ማሽመድመድ ነው ከሚል እሳቤ አፍሪቃዊቷን ቤተ ክርስቲያን አውሮፓዊ ካባ ለማልበስ የሚደረግ እሩጫ እና 
ሶሥተኛው ምክንያት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከፍተኛ መተራመስ ለመፍጠር የሚንቀሳቀሰው ለባዕዳን በማደር እና ጧት ማታ ባዕዳንን በማድነቅ የቤተ ክርስቲያንን እና አባቶች ያቆዩትን ስርዓት ለመናድ የሚጣጣረው እና  ባለፈው ሰኔ/2007 በርካታ ገፆች አትሞ በድብቅ የነበረውን ስራውን በይፋ ማውጣቱን የገለፀው ''የተሃድሶ እንቅስቃሴ'' በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ልዩነት የመፍጠርያ ነጥብ ያገኘ መስሎት ስለሚያራግበው ነው።

ከእዚህ በታች ''አንድ አድርገን'' ድረ-ገፅ ላይ የያረዳዊ የቤተ ክርስቲያናችንን ዜማ በባዕዳን መቀየር የሚመክሩትን አስመልክቶ ከሁለት ዓመት በፊት የወጣ ፅሁፍ የድርጊቱን እኩይ አላማ ስለሚያሳይ እንዳለ አቀርበዋለሁ።



''ከአበው ከወረስናቸው በርካታ መንፈሳዊ ርስቶቻችን አንዱ መንፈሳዊው ዜማ ነው።ይህ መንፈሳዊ ዜማ አባቶቻችን ከእግዚአብሔር የተቀበሉትና ከእርሱ ጋር የተገናኙበትእኛም ተግተን ብንጠብቀው ወደ ሰማያዊ ኅብረት የምንነጠቅበት መሰላል ነው። መንፈሳዊው ዜማ በዓለም ካሉት ሀገራት ይልቅ ለኢትዮጵያ ተለይተው ከተሰጡሃብታት አንዱ ነው። ኢትዮጵያ ከታላቁ አባት ከቅዱስ ያሬድ የተቀበለችው የዜማርስትም ጣዕሙን ለሚያውቀው በጦር መወጋትን እንኳን  ህመሙን ያስረሳ ነው (በቅዱስ ያሬድ ዜማ የተመሰጡት አፄ ገብረ መስቀል በጦር  የቅዱስ ያሬድ እግር ላይ በትረ መስቀላቸውን መትከላቸው እና  ሁለቱም ተመስጠው ሲነቁ መመልከታቸው) ፡፡ይህን የዜማ ርስት ግንበዚህ ዘመን አልሰጥም ብሎ እንደ ናቡቴ የሚጠብቅ አልተገኘም ፤ ንጉሥ አክዓብለናቡቴ ያቀረባቸውን ሁለት አማራጮችም በዘመናችን ትውልዱ በደስታ ተቀብሎትይገኛል፡፡
ለናቡቴ የቀረበው የመጀመሪያው ምርጫ የአባቶችን ርስት ወስጄ ሌላ ርስትንልስጥህ › የሚል ነበር።በዚህ ዘመንም ከአባታችሁ ከቅዱስ ያሬድየተቀበላችሁትን ዜማ ትታችሁ ሌላ ያሬዳዊ ያልሆነ ዜማን እናሰማችሁ ባዩ በዝቷል።ይህንንም ጥሪ ተቀብሎ ያሬዳዊ ያልሆነን ዜማ ማድመጥና ማድነቅ የተለመደ ሆኗል፡፡
ሁለተኛው የናቡቴ ምርጫ ደግሞ ‹ገንዘብ ልስጥህ ርስትህን ስጠኝ› ነበር።ይህን አይነቱንም መንገድ ዛሬ ብዙዎች የቀደመውን የዜማ ርስታችንን ለመጣላችን መንስኤነው።የናቡቴና የእኛ ዘመን ነገር ልዩነቱ ናቡቴ በንጉሥተገድዶም እንኳን ርስቱን ሳይሰጥ የሞተ ሲሆን ይህ ትውልድ ደግሞ በራሱ ፍላጎትርስቱን እየሸጠና እየለወጠ መሆኑ ነው።ያሬዳዊ ዜማ የአንድ ወገን ባሕል ሳይሆን እግዚአብሔር በቀጥታ ለቤተ ክርስቲያን ዘኢትዮጵያ የሰጠው መንሳዊ ጸጋ ነው።ያሬዳዊውን ዜማ ማጣጣልና መቃወም ቤተ ክርስቲያኒቱን መቃወም እንጂ የተወሰኑግለሰቦችን መቃወም አይደለም፡፡'' 

በመጨረሻም ፅሁፌን ለመደምደም የምፈልገው በአንድ አረፍተ ነገር ነው።ሰውን መውደድ፣ አባትን መውደድ ወይንም ማድነቅ አንድ ነገር ነው።የሚወዱትን አባት የሚለውን ሁሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖና አስመስሎ ለምዕመናን ማቅረብ ግን የቤተ ክርስቲያንን ስርዓት አለማወቅ ነው።አርጋኖን እና ኦርጋን ምን አገናኛቸው? ሰውን እንፈር፣እግዚአብሔርንም እንፍራ!

ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

የካቲት 5/2008 ዓም  (ፈብሯሪ 13/2016)

ማጣቀሻ 

+  አንድ አድርገን ድረ-ገፅ 2006 ዓም 
+  መፅሐፍ ቅዱስ 
+  አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ልዩ መርሐ ግብር ግንቦት 10 እስከ 12 www.danielkibret.com 



No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...