ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, July 9, 2015

Ethiopia - Out of over Hundred thousands of political prisnors less than ten of them are released. Doese it give sence to Ethiopians and International Community? ''በኢትዮጵያ በስድስት የፌድራል፣በአንድ መቶ ሃያ የክልል እና በአያሌ ድብቅ እስር ቤቶች ውስጥ ከመቶ ሺህ በላይ እስረኞች ይገኛሉ'' ዓለም አቀፍ የእስረኞች ጥናት ማዕከል።ከእነዚህ ውስጥ ከአስር ያነሱትን መፍታት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ምን አይነት ስሜት ይሰጠዋል? የእስረኞቹስ ጥያቄዎች ተመለሱ?






ኢትዮጵያ በስነ-መንግስት ታሪክ ፍርድ እና ፍትህ አዋቂ መሪዎች የምታውቅ ሀገር ነበረች።የቀደመውን በሙሉ ጥላሸት ቀብቶ የመኖር ስልት የሚከተለው በስልጣን ላይ የሚገኘው ጎጥን መሰረት ያደረገ መንግስት ወደ ስልጣን ሳይመጣ  በፊት በነበሩት ዘመናት ውስጥ ሁለት አይነት ዘመናትን ማሳለፋችንን ለማወቅ ይቻላል።አንደኛው የዘመናዊው የፍትህ ስርዓት ሳይተዋወቅ ሲሆን ሁለተኛው ዘመናዊው የፍትህ ስርዓት ከተዋወቀ በኃላ ያለው ነው።እዚህ ላይ ''ዘመናዊ'' ምን ማለት ነው? ''ዘመነ'' ለማለት መስፈርያዎቹ ምን ምን ናቸው? የሚሉትን ጥያቄዎች ለጊዜው አቆይተናቸው ነው። 

በቀደሙቱ እንበል እስከ ሃያኛው ክ/ዘመን መግቢያ ድረስ የፍትህ ስርዓት መሰረት የሚያደርገው ሶስት ነገሮችን  ነው።እነርሱም  ሃይማኖታዊ መሰረት፣ የስልጣን መዋቅር እና የተፈጥሮ ክህሎት ናቸው።ሕዝብ ፍርድ ሲፈልግ ወደ ሃገረ ገዢው፣የሃይማኖት አባት ወይንም ወደ ተፈጥሮ ክህሎት  ወደታደሉት የሀገር ሽማግሌዎች ይሄዳል።ከእነኝህ ውስጥ ግን የማሰር እና የመፍታት ስልጣን ያለው የአካባቢው ሀገረ ገዢው ሲሆን ሃገረ ገዢው የፈረደው ፍርድ ያልተስማማው ወደ ወረዳ ሃገረ ገዢው ከዝያም ማለፍ ከፈለገ ቀን ጠብቆ እስከ ንጉሡ ድረስ  አቤቱታውን የማድረስ ሁኔታ ነበር።ይህ ማለት ወቅቱ ፍርድ ያልተገመደለበት ነው አልያም ጥቂቶች በገዛ ስልጣናቸው ፍርድ አላጣመሙም ማለት አይደለም።አሁን ኢህአዴግ/ወያኔ ከሚሰራው የማን አለብኝነት ተግባር ጋር ስናነፃፅረው ግን የህሊና ዳኝነትን እና ይሉኝታን  ፈፅሞ ከግንዛቤ ያላስገባ የፍትህ ሂደት ያየነው በእዚሁ ስርዓት ነው።

ለምን እንደታሰሩ ያላወቁት እንዴት እንደተፈቱም አልተነገራቸውም 

ለምን እንደታሰሩ ያላወቁ፣በድንገት ሲፈቱም እንዲሁ ለምን እንደተፈቱ ያልተነገራቸው፣ከእድሜያቸው አስፈላጊ የነበረውን
 የወጣትነት ጊዚያቸውን አሳልፈው ከእስር የተፈቱት ኤዶም ካሳዬ፣ ዘላለም ክብረት፣ አስማማው ሃይለጊዮርጊስ፣ ተስፋለም ወልደየስ
 አራጌ ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣ ርዕዮት ዓለሙ እና ምናልባትም ከሰሞኑ ለሚፈቱት ሁሉ ደስታን ለመግለፅ የግድ በእስር ቤት ውስጥ 
ማለፍን አያስፈልግም።ለቤተሰብ እና ለወዳጅ ዘመድ ቀርቶ ለማንም ኢትዮጵያዊ የተፈፀመባቸው ግፍ ልብ ያደማል።ኢህአዴግ/ወያኔ
 ሀገር ሲያሸብሩ፣በውጭ ሀገር መሰረታቸውን ካደረጉ ኃይሎች ጋር ሲፃፃፉ አገኘሁ፣ኢ-ሜይላቸውን ስከፍተው እገሌን ሰላም አሉ እና 
የመሳሰሉትን እያነሳ ፍርድ ቤት አንገላታቸው።ለምሳሌ የዞን 9 ጦማሪዎችን ከ30 ጊዜ በላይ ፍርድ ቤት አመላልሷቸዋል።

በወጣቶቹ ላይ ከተፈፀሙት ግፎች ውስጥ ማህሌት ፋንታሁንን  በእኩለ ሌሊት እየጠሩ  እራቁቷን ሆና አይኗ ተሸፍኖ እያሸማቀቁ እና ፀያፍ ስድብ እየሰደቡ ያልሰራችውን በግድ እንድትፈርም አድርገዋታል።ርዕዮት አለሙ ከደረሰባት የእስር ቤት ስቃይ በተጨማሪ የይቅርታ ደብዳቤ እንድትፈርም ብዙ ፈተና ደርሶባታል፣የጡት ህመም ገጥሟት ሕክምናውን እንዳታገኝ ተደርጋለች።የእስር  ጊዜዋ ባለፈው ጥቅምት ላይ ያለቀ ቢሆንም በእስር እንድትቆይ ቤተሰብ እንዳይጎበኛት ተደርጋ ቆይታለች።

ፍርድ ቤት ነፃ ያለውን ከመንገድ ጠብቀው ያስሩታል።አንድ ቀን የጦርነት ፊልም በአግባቡ አይቶ የማያውቅ የዋህን  ቦንብ ሊያፈነዳ ሲል ያዝነው ብለው እስር ቤት ይወረውሩታል።ሲታሰሩ ያማያውቁ፣ለምን እንደታሰሩ ያልተነገራቸው፣ሲፈቱም ድንገት ተጠርተው ''ዕቃህን ሰብስበህ ወደ ቤት ሂድ'' ተብለው በግልምጫ የሚነገርባት ምድር ኢትዮጵያ ነች።የወጣትነት ጊዜውን በእስር ቤት ያቃጠለ፣ለምን መጀመርያ በሐሰት ከሰሳቹህኝ? ብሎ መጠየቅ የማይቻልባት ሀገር ነች ኢትዮጵያ። ቤተሰብ እንዳትመጣ ሲባል የሚቀርባት፣ና! ሲባል የሚሄድባት፣ለዓመታት በእስር ቤት ልጁ ሲሰቃይ ኖሮ በድንገት ልጅህን ውሰድ ሲባል የሚወስድባት ነች ኢትዮጵያ።

እንደ ዓለም አቀፍ የእስረኞች ጥናት መረጃ  (http://www.prisonstudies.org) መሰረት ኢትዮጵያ ብዙ ሺዎች አሁንም በእስር ቤት የሚማቅቁባት ነች። እዚህ ላይ ስለ እስረኞች ስናወራ የፖለቲካ እስረኞችን እንጂ በወንጀል ምክንያት የታሰሩትን እያወሳሁ አለመሆኑን ልብ በሉልኝ።ከእዚህ በታች በኢትዮጵያ የሚታወቁ  (በርካታ የድብቅ እስር ቤቶች መኖራቸውን መረጃውም ይጠቅሳልና) የእስረኞችን ቁጥር ያስቀምጣል።መረጃው በእራሱ ደግሞ ውሱንነት እንደሚኖርበት ስናስብ የእስረኞች ቁጥር ከእዚህ በእጅጉ የበለጠ መሆኑን እንረዳለን።ይህ በእንዲህ እንዳለ ይህ ፅሁፍ ሲፃፍ በእስር ላይ የሚገኙ የፖለቲካ እስረኞችን በመጠኑ ለመዘርዘር ልሞክር።እዚህ ላይ ከአምቦ ግጭት እሰከ ወልቃይጥ፣ከግምቢ ወለጋ እሰከ ኡጋዴን እና አፋር አያሌዎች በእስር ላይ መሆናቸውን መዘንጋት አይገባም።በመሆኑም ከእዚህ በታች የተዘረዘሩት ከማህበራዊ ድረ-ገፅ አበበ ቶላ ላይ የተወሰደ ብቻ መሆኑን አንባቢ ሊገነዘብ ይገባል።

1 - ተመስገን ደሳለኝ 
2- እስክንድር ነጋ 
3- ናትናኤል መኮንን 
4- አንዳለም አራጌ
5- ውብሽት ታዬ
6- አበበ ቀስቶ
7- ሃብታሙ አያሌው
8- ዳንኤል ሺበሺ
9- አብርሃ ደስታ
10- የሽዋስ አሰፋ
11- ዘላለም ወርቅአገኘሁ
12- አቤል ዋበላ
13- ናትናኤል ፈለቀ
14- በፍቃዱ ሃይሉ
15- አጥናፍ ብርሃኔ
16- ፍቅረማርያም አስማማው
17- እየሩሳሌም ተስፋው
18- ብርሃኑ ተክለያሬድ
19- ኦልባና ለሌሳ
20- ቴድሮስ አስፋው
21- ማትያስ መኩርያ
22- ብሌን መስፍን
23- ተዋቸው ደምሴ
24- ንግስት ወንዳፈራሁ
25- ሜሮን አለማየሁ
26- ደሴ ካህሳይ
27- ናትናኤል ያለምዘውድ
28- ሰንታየሁ ቸኮል
29- ማስተዋል ፈለቀ
30- ንግስት ወንድይፍራው
31- ሂሩት ክፍሌ
32- እማዋይሽ አለሙ
33- ሰለሞን ከበደ
34- የሱፍ ጌታቸው
35- አቡበከር አህመድ
36- አህመዲን ጀበል
37- ያሲን ኑር
38- ካሚል ሸምሱ
39- በድሩ ሁሴን
40- ሼህ መከተ ሙሄ
41- ሳቢር ይርጉ
42- መሐመድ አባተ
43- አህመድ ሙስጠፋ
44- አቡቡከር አለሙ
45- ሼህ ሙኒር ሁሴን
46- ሰኢድ አሊ ጁሃር
47- ሙባረክ አደም
48- ካሊድ ኢብራሂም
49- ሙራድ ሽኩር
50- ኑር ቱርኪ
51- ሼህ ባህሩ ኡመር
52- አንዳርጋቸው ጽጌ
53- ጀነራል ተፈራ ማሞ
54- ጀነራል አሳምነው ጽጌ
55- ኮነሬል አለሙ መኮንን


በኢትዮጵያ ያሉት እስረኞች ብዛት በመቶ ሺዎች የሚቆጠር መሆኑን እና በኢህአዴግ/ወያኔ ዘመን እንዴት እያደገ እንደመጣ የዓለም አቀፍ እስረኞች ጥናት ማዕከል ኢትዮጵያ ውስጥ እስከ አለፈው ዓመት ድረስ የሚገኙ እስረኞችን ቁጥር ያወጣበት ዘገባ  ዓለም አቀፍ የእስረኞች ጥናት ማዕከል International  Center for Prisnors Study (ICPS) ይመልከቱ።

በመጨረሻም ለማጠቃለል ማንም የኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባኝ የሚል ሰው ሊገነዘበው የሚገባው።ከእስረኞች መታሰር እና መፈታት ባለፈ እስረኞቹ እና የኢትዮጵያ ሕዝብ የጠየቁት ጥያቄ ምላሽ አገኘ ወይ? የሚለው ቁልፍ ጥያቄ ነው ሊሰመርበት የሚገባው።ስርዓቱ የስልጣን መቆያ መንገድ ያደረገው የጎሳ ፖለቲካ ፖሊሲ ተቀየረ? ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል አለ? የዲሞክራሲ ጥያቄው ተመለሰ? በምርጫ መንግስት መቀየር እንችላለን? ወይንስ ዛሬም 100% እየተባለ እየተቀለደ ነው? የፍትህ ስርዓቱ ምን ያህል ነፃ ነው? አንድ ዜጋ ምን ያህል የፍትህ ስርዓቱ ላይ ይተማመናል? ምጣኔ ሃብቱ፣የፖለቲካ ስልጣኑ፣የወታደራዊ አመራሩ ሁሉ በአንድ ጎጥ ስር ነው ወይንስ ሁሉም ኢትዮጵያዊ እኩል ያሳትፋል? እና ሌሎች ቁልፍ ጥያቄዎች ከእስረኛ መፍታት እና ማሰር ሂደት በላይ የገዘፉ እና ለእስሩ ዋነኛ እና ቁልፍ ምክንያቶች ናቸው።ርትዮት የታሰረችው፣እስክንድር ወህኒ የወረደው ሌሎች አያሌዎች ፍዳ የሚቀበሉበት ጉዳይ ከላይ በመጠኑ የተጠቀሱት እና ሌሎች ጉዳዮች ናቸው።

ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG
ሐምሌ 2/2005 ዓም (ጁላይ 9/2015)

No comments: