ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, November 11, 2014

ሰበር ዜና-የኢትዮጵያ ብሔራዊ መዛግብት እና መፃህፍት ቤት በስሩ ለረጅም ጊዜ የነበሩትን በፈረንሳይኛ፣ስፓኒሽ፣ፖላንድ፣ጀርመንኛ ወዘተ ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ የተፃፉትን መፃህፍት ሊሸጣቸው ነው ኢትዮጵያን ያላችሁ መፃሕፍቱን አድኑ!!! ምናለ ኢትዮጵያን መጥላታችሁን በልኩ ብታደርጉልን?


የኢትዮጵያ ብሔራዊ መዛግብት እና መፃህፍት ቤት መፃሕፍቱን የሚሸጠው  በጨረታ ጭምርም ነው።ዛሬ ህዳር 2/2007 ዓም  ሸገር ራድዮ በምሽቱ ዜና ላይእንደዘገበው ብሔራዊ በተመዛግብት እና መፃህፍት ቤቱ መፃሕፍቱን ለመሸጡ  የተሰጠው ምክንያት ''ቦታ ስለጠበበን ሌሎች ቅጂዎች ማስቀመጫ ስላጣን ለመሸጥ ወስነናል ሌላ ምክንያት  የለም''  ማለታቸውን ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመስርያቤቱ ሰራተኛ በቀጥታ ለራድዮ ጣብያው ሲናገሩ አስደምጧል።

ስለኢትዮጵያ ታሪክ  የተጻፉት እነኝህ መፃህፍት በሌላው ዓለም በቀላሉ የማይገኙ እና የተፃፉትም ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ ብቻ መሆኑን እያወቁ ''ቦታ አጣበቡ'' ተብለው ሽያጭ ላይ ናቸው። በጣም የሚገርም ነው።ቦታ ጠበበን ተብሎ ለዘመናት የተከማቹ መፃህፍት እንዲሸጡ የወሰነው ኃላፊ  ኢትዮጵያዊ ነው? አሁን በጨረታ ለመግዛት የአንዱ ሀገር ሙዝየም ወይንም መፃህፍት ቤት በጅምላ ሊገዛው እንደሚችል ትልቅ ስጋት ፈጥሯል።ይህ ማለት ነገ ለምርምር ኢትዮጵያውያን ወደ ገዛው ሀገር ብዙ የውጭ ምንዛሪ እየከፈሉ ይሄዳሉ ማለት ነው።ዛሬ የብሔራዊ መዛግብት ሰራተኞች ስፓኒሽ፣ፖላንድኛ፣ጀርመንኛ ባይችሉ ነገ እነኝህን ቋንቋዎች የሚችል ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያ አታፈራም?  ወይንም ነገ የሚችል ትውልድ አይነሳም? በምን መለክያ ነው የሀገር እና የህዝብ ሀብት ለጨረታ የሚቀርቡት?

እዚህ አውሮፓ ለምሳሌ ስዊድን እና ኖርዌይ ውስጥ ያሉ ብሔራዊ መዛግብት እና ትልቁ የህዝብ መፃህፍት ቤት በየትኛውም ሀገር የታተሙ መፃህፍት፣መፅሄቶች እና ጋዜጦች በየትኛውም ቋንቋ ቢታተሙ በጀት መድበው ይገዛሉ። ለምሳሌ ኢትዮጵያ የሚታተም ማናቸውም መፅሐፍ እና ጋዜጣ አዲስ ዘመንን ጨምሮ ከወር ወር ተከታትለው ይገዛሉ ያስቀምጣሉ።ያንን ቋንቋ የሚናገር ኖረ፣ አለኖረ የሚል ጥያቄ የለም።

አሁን በተለይ ጋዜጦቹ ዲጂታል ከሆኑ ቀን በቀን እየቀዱ ፋይል ያደርጋሉ።እነኝህ ፅሁፎች ነገ ገንዘብ ብቻ ሳይሆኑ ትልቅ የመመራመርያ መሳርያም ናቸው። ኢትዮጵያ ግን ያውም ስለራሷ የተፃፉትን መፃህፍት ''ቦታ ጠበበኝ'' የሚሉ ከንቱዎች ለጨረታ አቀረቡት።ምናለ ቢያንስ ለዩንቨርስቲዎች በአደራ ቢሰጡ? የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የኢትዮጵያ ጥናት እና ምርምር ኢንስቲትዩት እነኝህን መፃህፍት መያዝ አንዱ የስራው አካል አይደለም? ለምን እንዲሸጡ ተወሰነ? 

ምናለ ኢትዮጵያን መጥላታችሁን በልኩ ብታደርጉልን? በነገራችን ላይ መፃሕፍቱን ለረጅም ጊዜ ሲያከማች የነበረው ይሄው ዛሬ ለመሸጥ የሚያስማማው መስርያቤት መሆኑን ይታወቃል።ኢትዮጵያን ያላችሁ መፃሕፍቱን አድኑ!!!

ጉዳያችን
ህዳር 3/2007 ዓም (ኖቬምበር 12/2014)

No comments: