ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, October 10, 2014

የዶ/ር ሽፈራው ''የአንገታችሁን ማዕተብ እንዲወልቅ ይደረጋል'' ንግግር ላይ የአይን እና የጆሮ እማኝ ቃሉን ሰጠ፣የፈድራል ጉዳዮች ቃል አቀባይ እና ዶ/ር አረጋዊ በርሄ በጉዳዩ ላይ የሰጡት ቃል (የጉዳያችን አጭር ጥንቅር)



ባለፈው ቅዳሜ መስከረም 24/2007 ዓም ሐራዘተዋህዶ በድረ-ገፁ ላይ የፌድራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ‹መንግሥታችን ሴኩላር ነው›› ሲሉ በጠያቂዋ የተጠቀሰውን ዐይነት አለባበስ የተቹት ሚኒስትሩ፣ ‹‹እርሱም [ማተቡም] ቢኾን የጊዜ ጉዳይ ነው፤ እንደ የሃይማኖት መለያ እስካገለገለ ድረስ አደረጃጀታችንን ስንጨርስ ማተብም ቢኾን መውለቁ አይቀርም፤›› የሚል ምላሽ መስጠታቸው ተገልጧል፡፡'' ሲል ሰፊ ዘገባ አስነበበ።ዘገባውን ተከትሎ በርካቶች ሃሳባቸውን ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ተቃውሟቸውን ገልፀዋል።ጉዳዩን አስመልክቶ ማክሰኞ መስከረም 27/2007 ዓም ኢሳት ራድዮ ሶስት ግለሰቦችን አነጋግሯል።የአይን እና ጆሮ እማኝ፣ዶ/ር አረጋዊ በርሄ እና አቶ አበበ ወርቁን።

1ኛ/ የአይን እና የጆሮ እማኝ 

ከሀገር ቤት በስብሰባው ላይ የነበረ ተሳታፊ በስልክ የሚከተለውን ተናግሯል።ግለሰቡ በሰጠው ቃል ''ነገሩ እውነት ነው የተሰበሰብንበት ርዕስ 'ልማታዊ ዲሞክራስያዊ መንግስት ግንባታ' የሚል ሲሆን ወደ 800 ይምንጠጋ የመካከለኛ አመራር አካላት የተሳተፍንበት ነው።የነገሩ መነሻ ጥያቄ ነበር .....ጥያቄው ለዶ/ር ሽፈራው የቀረበ ነበር እና እሳቸው በምላሻቸው 'የጊዜ ጉዳይ ነው፤ እንደ የሃይማኖት መለያ እስካገለገለ ድረስ አደረጃጀታችንን ስንጨርስ ማተብም ቢኾን መውለቁ አይቀርም፤' ነበር ያሉት እና በወቅቱ በጣም አሳዛኝ ጉዳይ ፈጥሯል.....እኔ እንደማስበው በቅርቡ ተግባራዊ እንደሚያደርጉት ነው የማስበው።''
ጋዜጠኛ መሳይ መኮንን -'' ቀደም ብዬ የፌድራል ጉዳዮች ሚኒስትር ቃል አቀባይን አነጋግሬ ነበር እና እሳቸው 'በሬ ወለደ' ነው ያሉት እስኪ ያሉትን ቃል በቃል ተናገር''
የስብሰባው ተሳታፊ '' ይህንን ነገር ቃል በቃል ብለውታል በትክክል ብለውታል ! እየተሰራበት ነው መመርያውን እያዘጋጁ ነው ----በትክክል የምነግርህ ነገር በቅርብ ጊዜ በቅርብ ጊዜ ምናልባት ምርጫውን ይጠብቁ ይሆናል ---ዕውነትን ተናግሬ መሞት ስለምፈልግ ነው ---ለእናንተማ መረጃ ይሰጣሉ ብዬ አላስብም ----''
ጋዜጠኛ መሳይ -''በቃል ነው እንጂ በወረቀት ደረጃ የተቀመጠ አለ?"
የስብሰባው ተሳታፊ - ''በፓወር ፖይንት የታገዘ ነው ከእዝያ ላይ ሲያብራሩ ነው የተጠየቁት''


2ኛ/ ዶ/ር አረጋዊ በርሄ የመጀመርያው የህወሓት ሊቀመንበር እና መስራች 


ዶ/ር አረጋዊ በርሄ   ''መንግስት የእዚህ አይነት እርምጃ ሊወስድ ይችላል ብለው ያስባሉ ወይ ?'' ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ - ''ይሄ መንግስት በጠበንጃ የመጣ መንግስት ነው የተለያየ ሕዝቡን የሚቆጣጠርበት መዋቅር መመስረት አለበት----አሁን አስር እና አስራ አምስት እያደራጀ ለመቆጣጠር ይፈልጋል።ሃይማኖትን ከፋፍሎ አክራሪ እንዲፈጠር እያረገ ነው----ይህ እራሱ መንግስት የሚፈጥረው ሕዝብ ከህዝብ በማጋጨት የሚኖር ነው----የማዕተቡን ጉዳይ ሊያደርገው ይችላል።ሕዝቡን አፍኖ ለመያዝ እንደ ስልት የሚጠቀምበት ነው።ይህም አንዱን በአንዱ ላይ ለማነሳሳት ይች ለበሰች ያች አለበሰችም እያለ ለመክፈል ነው።---ፖሊሲው አይታወቅም ተገላባባጭ ፖሊሲ ነው ያለው የሃይማኖት ድርጅቶችን በሙሉ መቆጣጠርይፈልጋል።ይህ ሕዝብ ድሮ ተቻችሎ የኖረ ሕዝብ ነበር።ይህ መንግስት ለመቆጣጠር የሚሰራው ነው።ይህ መንግስት አይታመንም።የስለላ መዋቅሩን ብትመለከት የሃይማኖት ድርጅቶች ውስጥ እየገባ ነው የሚሰራው----ሃይማኖቶችን ለመቆጣጠር እስከ ማሰር፣መግደል የሚደርስ ነው እነ አስገደ የትኛውን ጥይት ተኩሰው ነው የታሰሩት? ይህ በወታደር እና በስለላ መቆጣጠር ስለሚፈልግ ነው ይህንን ጠንቅቀን ድሮም እናውቀዋለን'' ብለዋል።በመጨረሻም ዶ/ር አረጋዊ ሃይማኖትን በተመለከተ እንዲህ አሉ '' አፄ ኃይለ ስላሴ ያሉት አንድ ነገር አለ።ኃይማኖት የግል ነው ሀገር የጋራ ነው -----የኢትዮጵያ ሕዝብ ችግሩን የጋራ ስርዓት ፈጥረን ለመፍታት ሜዳ ላይ ወርደን መፍታት አለብን'' ብለዋል፣

3ኛ/ የፌድራል ጉዳዮች ሚንስቴር ቃል አቀባይ አቶ አበበ ወርቁ 

አቶ አበበ  ''ጉዳዩ የፈጠራ ነው።የግለሰብ መብት ጉዳይ ነው።መስራበታችን ሴራ ነው የሚለው''
ጋዜጠኛ መሳይ - '' ወሬው ከምን መነሻነት ነው የተነገረው።አልተናገሩም ከተባለ።ጉዳዩ በቀጥታ ተወስኗል ሳይሆን ወደፊት ሊተገበር ይችላል ነው።''
አቶ አበበ ''መነሻው የሐሰት ፕሮፓጋንዳ ነው።ስለዚህ አነሳሱ የተለያየ አቅጣጫ ይኖረዋል።መስራቤታችን ግን ይህንን አልወሰነም----
የሙስሊሞች ሂጃብም አልተከለከለም።ሙሉ በሙሉ ሰውነትን የሚሸፍነው አለባበስ ነው የተከለከለው'' 
ጋዜጠኛ መሳይ -''ማዕተብ በጥሱ የሚለው ጉዳይ እራሳቸው የመንግስት ደጋፊ የሆኑ ሁሉ ስብሰባው ላይ እንደተከራከሩ እኛም ለመረዳት ችለናል።ነገር ግን ጉዳዩ የመንግስት አቅዋም አለመሆኑን ነበር ለማወቅ የጠየኩት እርስዎ ደግሞ የመንግስት ውሳኔ አደለም የሚል ምላሽ ነው የሰጡት።የፌድራል ጉዳዮች ሚንስቴር ቃል አቀባይ አቶ አበበ ወርቁ ስለሰጡኝ ጊዜ አመሰግናለሁ።''


በእዚህ አጋጣሚ ኢሳት ይህን የመሰለ ሚዛናዊ ዘገባ በማቅረቡ ትልቅ ምስጋና ሊቸረው ይገባል።የፌድራል ጉዳዮች ሚኒስትር ቃል አቀባይን አቅርቦ ማናገሩ በራሱ ሚዛናዊ እና ዘመናዊ የጋዜጠኝነት ሙያ ነው።ኢቲቪ ለምሳሌ ዋሽግተን ደውሎ አንዳንድ ዜና ቀጥታ ባለጉዳዮችን እያናገረ ለሕዝብ መዘገብ መቼ ይለምዳል? ምኞት አይከለከልም።

ጉዳያችን
መስከረም 30/2007 ዓም (ኦክቶበር 10/2014)


No comments: