ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, October 1, 2014

የዋሽግተኑ ጉዳይ ከዓለም አቀፍ ሕግ አንፃር ሲታይ።የኢህአዲግ አድናቂዎች ይህንን ማስታወሻ አንብበው ሲጨርሱ ከፅሁፉ ጋር እንደሚስማሙ ይጠበቃል-የጉዳያችን ማስታወሻ

 ሰለሞን የተሰኘው በዋሽግተን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰራተኛ ለጥያቄ በመጡ ተቃዋሚዎች ላይ ሽጉጥ ደግኖ 
(ፎቶ ''አሶሰትድ ፕሬስ'' ከኢሳት ቲቪ መውሰዱን ገልፆ ካወጣው እና የእንግሊዝ ''ዴይሊ ሜይል'' በድረ ገፁ ላይ ''በካሜራ የተያዘ ድራማዊ እንቅስቃሴ'' በሚል ርዕስ ስር ከለቀቀው ዜና የተወሰደ) 

''ዓለም አቀፍ ሕግ፣ዓለም አቀፍ ሕግ'' የምትል ቃል በእየቦታው ትሰማ ጀመር።እሰይ! እንዴት ደስ ይላል።ይህንን ሰሞኑን በማኅበራዊ ድረ-ገፅ ላይ የሚጠቅሱት ደግሞ የስርዓቱ አድናቂዎች ናቸው።ጉዳዩን የሚያነሱትደግሞ  በዋሽግተን ኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በተደረገው ተቃውሞ ሳብያ ነው።እስኪ ለህሊናችን መጀመርያ በሀገር ውስጥ እራሱ ላወጣው ሕግ መገዛት ቢያቅተው ለዓለም አቀፍ ሕግ እንዲገዛ ስርዓቱን እንምከረው።እንዲህም እንጠይቅ-


  • ለመሆኑ ዓለም አቀፍ ሕግን እንደ ዓለም ዋንጫ ቅሪላ በእግሩ የሚያጦዛት ማን ነው? 
  • ማን ነው የኖርዌይ ዜግነት ያላቸውን የጋምቤላ አስተዳዳሪ ከደቡብ ሱዳን ጠልፎ ወስዶ ያሰረው? ዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ቁጥር ስንት እንበለው?
  • ማን ነው የእንግሊዝ ፓስፖርት የያዙትን አቶ አንዳርጋቸውን ከየመን ጠልፎ ያሰረው? ዓለም አቀፍ ሕግ ቁጥር ስንት እንበለው?
ዓለም አቀፍ ሕግ የአፍ ማሟሻ አደለም! በተግባር ለእራስ ሲሉ የሚያከብሩት ነው።ዛሬ የዋሽግተን ኤምባሲ ሲደናገጥ ''ሕግ ምናምን'' አትበሉ።የዋሽግተኑን ጉዳይ በዓለም አቀፍ ሕግ አንፃር ካየነው የኤምባሲው የሕግ ከለላ ከባዕዳን ነው እንጂ ከሀገሩ ተወላጆች አይደለም! አንድ ትውልደ ኢትዮጵያዊ በሀገሩ ጉዳይ በሰላማዊ መንገድ አራት ኪሎ ቤተ መንግስት ውስጥ ገብቶ የመቃወምም ሆነ ዋሽግተን ላይ ባለው በሀገሩ ኢምባሲ ውስጥ ገብቶ የመቃወም መብቱን ዓለም ዓቀፍ ሕግ አይገድበውም።የሰንደቅ አላማው ጉዳይም ሰንደቅ አላማው በሌላ ሰንደቅ አላማ ተተክቶ ቢሆን ነበር የሚያሳዝነው።ይህ ቢሆን ኖሮ በሕግም አከራካሪ ይሆን ነበር።የሉዓላዊነት ጥያቄም አብሮ ሊነሳ ይችል ነበር።የሆነው ግን ለሕግ ወቀሳም አይበቃም። ተቃዋሚዎቹ የተኩት ቀድሞ የኢህአዲግ አርማ ያለበትን  በእራሷ በኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ ነው።

አንድ ሀገር የውጭ ቆንስላ ወይንም ኤምባሲን የመጠበቅ ኃላፊነት አለበት።ይህ የሚያደርገው ግን ከእዛ ሀገር ዜጎች የበለጠ ኃላፊ ሆኖ አይደለም።የኤምባሲው ሀገር ተወላጅን ወደ ኤምባሲው 'ግባ አትግባ' ማለት ሌላ ሳይሆን አንድን ኢትዮጵያዊ ወደ እራሱ ሀገር 'ግባ አትግባ' ንትርክ ውስጥ መግባት ማለት ነው።የዋሽግተኑ የኢትዮጵያ ኤምባሲም ጉዳይ ይሄው ነው።ኢትዮጵያውያን በኤምባሲያቸው ቅጥር ግቢ ሆነው የሚያደርጉት ሁሉ በኢትዮጵያ ምድር ላይ እንዳደርጉ ነው የሚቆጠረው።የኢምባሲ ግቢ ማለት የታፈረ የተከበረ ኢምባሲው የተጠራበት ሀገር ምድር ማለት ነው።ለእዚህ ነው አንድ ስደተኛ ወደ አንዱ ሀገር ኤምባሲ ገብቶ ጥገኘነት ቢጠይቅ ኤምባሲው ሀገር እንደገባ የሚቆጠረው እና ኤምባሲው ያለበት ሀገር ፖሊስ ዘሎ ሊገባ የማይችለው።ኢህአዲግ አዲስ አበባ ሲገባ ጣልያን ኤምባሲ እጃቸውን የሰጡ ባለስልጣን የፌድራል ፖሊስ መያዝ ያልቻለው ለእዚህ ነው።ግቢው ሃገሩ ነው።ተቃዋሚዎችም ዋሽግተን ውስጥ ያለው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ግቢ ሀገራቸው ነው።የመቃውም መብታቸው ላይ አሜሪካን አይመለከታትም።ጉዳዩ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ነው።አሜሪካ የሚመለከታት በምድሯ ላይ የማይፈቀደው የመግደል ሙከራ፣ማስፈራራት እና ድምፁ በግቢው ውስጥ መወሰን ያልቻለው አካብቢውን ያሸበረው የተኩስ ድምፅ ነው። 

ባጭሩ አሜሪካ ኃላፊነት ያለባት የጦር መሳርያ ይዘው ወይንም የሚያሸብር ነገር ይዘው ወደ ኢምባሲ የመጡትን የመጠበቅ እንጂ በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ለመቃወም ሰንደቅ ዓላማ እና የታሰሩ እስረኞች ፎቶ ይዘው ለመጡ አይደለም። እንዲያውም አሜሪካ በእንዲህ አይነቱ ጉዳይ ከገባች አሁንምበኢትዮጵያ የሀገር የውስጥ ጉዳይ እንደገባች ነው የሚቆጠረው።በነገራችን ላይ ከእዚህ በፊት ለአመታት ኢትዮጵያውያን በዋሽግተንም ሆነ ሌሎች ኢምባሲዎች ፊት ሰልፍ ካደረጉ በኃላ የሰልፋቸውን ጥያቄ የያዘ ደብዳቤ ለአምባሳደሩ ለመስጠት ሲጠይቁ የኢህአዲግ የኤምባሲ ሰራተኞች ከፎቅ ላይ ሆነው ቪድዮ ማንሳት እንጂ ደብዳቤ አይቀበሉም።እናም ዜጎች እንዴት ሃሳባቸውን ይግለፁ? ተቃዋሚዎቹ ሌላ አማራጭ ነበራቸው ወይ? የሚለውን የአሜሪካ መንግስትም የሚመለከተው ነው። በሰልፍ ሲወጡ ፖሊስ እንዲጠራ ይደረጋል።በፅሁፍ ሲያቀርቡ ኤምባሲው ለፎርማልቲም ቢሆን አይቀበልም።ልክ 'ምናምን' እንደነካው እንጨት ይጠየፋል።

ይህ ትልቅ የኢምባሲዎቹ የትዕቢት መገለጫ ነው።አንድ ዜጋ የፈለገው ጉዳይ ላይ የመቃወም ሃሳቡን በቃልም ሆነ በፅሁፍ የማቅረብ መብት አለው።ኢምባሲው እዝያ በተሰለፈው ሕዝብ እና በቤተሰቡ ገንዘብ ደሞዙን እንደሚያገኝ ዘንግቶ የተቃውሞ ደብዳቤ አለመቀበሉን በምን እንግለፀው? አዲስ አበባ ላይ ሆኖ ''እሰይ ደግ አደረካቸው'' እያሉ መፎከር አይደለም።አሰራርን መፈተሽ፣ትዕቢትን መቀነስ ነው የሚያስፈልገው። መጨረሻ ምን ሆነ ዜጎች ''ስሙን!!! ኡ ኡ ኡ !!'' እያሉ ወደ ኤምባስያቸው ገቡ።አሳፋሪው ድርጊት ግን የሀገራቸው ኤምባሲ ተኮሰባቸው።ይህ ነው አሳፋሪ ተግባር የሚባለው።ዓለም የገረመው ይህ ነው።ኢትዮጵያውያን ምን አይነት አሳፋሪ አገዛዝ ስር እንደወደቁ የተረዳው እዚህ ላይ ነው።በሀገራቸው የፖለቲካ ጉዳይ የተናደዱ፣ያዘኑ ዜጎች ዋሽግተን ላይ ሃሳባቸውን መግለፅ ካልቻሉ በሃገራቸውማ ቢሆን በታንክ ነው የሚሏቸው ብሎ የደመደመው ለእዚህ ነው።የአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት ቶሎ መግለጫ አላወጣም።ጉዳዩን የሚመለከተው ከላይ ከተጠቀሱት ነጥቦች አንፃር እንደሚሆን ይታወቃል።የውጭ መገነኛ ብዙሃን በተቃዋሚዎች ላይ የመተኮሱን ጉዳዩን ከገለፁበት ቃላት ውስጥ ''በካሜራ የተያዘ ድራማዊ እንቅስቃሴ'' ብሎ የዘገበው የእንግሊዝን ''ዴይሊ ሜይል'' ይጠቀሳል።

ከሰሞኑ ዋሽግተን ላይ ከተከሰተው ክስተት አንፃር ኢትዮጵያውያንም ለሁሉም ወገን ማስረዳት ያለባቸው ከላይ ከተጠቀሱት የአፈና ደረጃዎች አንፃር መሆን ይገባዋል።ፀሐፊዎች፣ጋዜጠኞች፣በውጭ ሀገር በልዩ ልዩ ኃላፊነት ላይ ያሉ ሁሉ ለዓለም (ለአሜርካኖችም ጭምር) ማስረዳት በእንግሊዝኛም መፃፍ ይጠበቅባቸዋል።የኢህአዲግ አድናቂዎችም ከህሊናችሁ ጋር ኑሩ! እውነታውን መርምሩ።መንግስታችሁ እንዴት ወዴት እየሄደ እንዳለ እና በውስጡ የተሰገሰጉት የትዕቢት አባቶች አደብ እስካልገዙ ድረስ ከትርፍ ይልቅ ኪሳራው እየበዛ መሄዱ አይቀርም።ዓለም አቀፍ ሕግን ግን ለቀቅ አድርጉት።


ጉዳያችን
መስከረም 21/2007 ዓም (ኦክቶበር 1/2014)


No comments: