ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, April 17, 2014

ሰበር ዜና - በኢትዮጵያ በግብረ ሰዶማዊነት ጉዳይ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን ተቃውሞ፣ሊደረግ የነበረው ፀረ ግብረ ሰዶማዊነት ሰልፍ መቅረት፣ የመንግስት ሁኔታውን አቅልሎ ለማየት የሚያደርገው ሙከራ ለ2007ዓም ምርጫ ለምዕራባውያን የቀረበ ማባበያ ይሆንን?



ፎቶ ደብረ አሚን አቡነ ተ/ኃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አዲስ አበባ መርካቶ (ፎቶ ከማ/ቅ/ መልቲ ሚድያ የተገኘ) 

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የግብረ ሰዶም ጉዳይ ከማኅበራዊ የቀውስ ጉዳይ ወደ ዓለም አቀፍ ፖለቲካዊ ጉዳይ እየተሸጋገረ መምጣቱ ይታወቃል።ድርጊቱን የሚደግፉት ምዕራባውያን የኃይማኖታዊ እና ማኅበራዊ ጥያቄዎችን ወደጎን በመተው  ''ከሰው ልጆች መብት'' ጋር ብቻ በማያይዝ ሃገራት ፀረ-ግብረ ሰዶማዊነት ሕግ እንዳያፀድቁ ካፀደቁም እንዳይተገብሩ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተፅኖ ለመፍጠር ሲሞክሩ ተስተውሏል።

ግብረ ሰዶማዊነትን ፖለቲካዊ መልክ አላብሳ ሀገሮችን የመጎንተያ መሳርያ ካደረጉት ሃገራት ውስጥ ለምሳሌ አሜሪካ ሩስያን እና  በርካታ የአፍሪካ ሃገራት ዑጋንዳ እና ናይጄሪያን ጨምሮ ያወጡትን ፀረ-ግብረ ሰዶማዊነት ሕግ ስትኮንን መሰንበቷ ይታወቃል።በተለይ የዑጋንዳው መሪ ዩዌሪ ሙሰቨኒ  ''አውሮፓውያን በፖለቲካ ጉዳያችን እንደገባችሁ በማኅበራዊ እና ባህላዊ ጉዳያችን አትግቡብን'' በሚል ኃይለ ቃል  ፀረ ግብረ ሰዶማዊነት ሕጉን ጋዜጠኞች ጠርተው በአደባባይ መፈረማቸው  ይታወሳል።

ወደ ኢትዮጵያ ስንመጣ በጉዳዩ ላይ ጠንካራ ተቃውሞ የሚያሰማ አንድም የኢህአዲግ ባለስልጣን እስካሁን አልተሰማም።ይህ ብቻ አይደለም  በርካታ አፍሪካውያን በጠቅላይ ሚኒስትራቸው ደረጃ በተቃውሞ መግለጫ ሲሰጡበት ሁለቱን የዓለም ታላላቅ ኃይማኖቶች በመቀበል ከዓለም ቀደምት የሆነች ኢትዮጵያ በጉዳዩ ላይ ምንም አለማለቷ ብዙ ኢትዮጵያውያንን ብቻ ሳይሆን አፍሪካውያንን ያሳዘነ ጉዳይ ነው።

ይልቁንም ከዓመት በፊት በአዲስ አበባ በተደረገ አንድ የዓለም አቀፍ የጤና ጉባኤ አስታከው ከተለያዩ ሃገራት የተውጣጡ ግብረ ሰዶማውያን በአፍሪካ ህብረት አዳራሽ ስብሰባ ሊያደርጉ ነው የሚለው ዜና እንደተሰማ በርካታ ኢትዮጵያውያንን ከማስቆጣቱም በላይ የሃይማኖት አባቶች ተሰብስበው የተቃውሞ መግለጫ ለማውጣት በዝግጅት ላይ እንዳሉ በወቅቱ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር የነበሩት የአሁኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የሃይማኖት አባቶችን ሰብስበው ተቃውሞ እንዳያወጡ ተፅኖ ማድረጋቸው እና ስብሰባው አዲስ አበባ ላይ ሊደረግ መቻሉ ይታወቃል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰሞኑን አዲስ አበባ ላይ ግብረ ሰዶማዊነትን በመቃወም ሊደረግ የነበረው ሰልፍ መቅረቱ እየተሰማ ነው ።ሰልፉ በአዲስ አበባ ወጣቶች ''ፎረም'' እና ''ወይንዬ'' በተሰኘ የኢትዮጵያ ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን የምዕ  መናን  ማኅበር አማካይነት እንደሚካሄድ ሲነገር ነበር።ሰልፉ የሚደረግ ለመሆኑ እና ፈቃድ ከመንግስት ያገኘ መሆኑን አዲስ አበባ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ በመግለጫው ላይ ያረጋገጠ ከመሆኑም በላይ ዕሁድ ሚያዝያ 19/2006 ዓም ሊደረግ መታሰቡን ከመንግስት ፈቃድ ማግኘቱን መግለጫው ስያብራራ '' ሚያዝያ 26/2014 ዓም የሚደረገው ሰልፍ ''ፀረ-ግብረ ሰዶማዊነት ሲሆን ሰልፉ በአዲስ አበባ እንዲደረግ ከመንግስት ማረጋገጫ አግኝቷል''  ይላል።

ዘግይተው የወጡ ዘገባዎች ደግሞ ሰልፉ እንደማይደረግ እና መንግስት ያላዘጋጀው ሰልፍ መሆኑን ይገልፃሉ።ቀድሞውንም መንግስት ያዘጋጀው ሰልፍ ነው የሚለው ግምት ያሰጠው ''የአዲስ አበባ ወጣቶች ፎረም'' በኢህአዲግ የሚደገፍ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ እንጂ መንግስት እስካሁን በግልፅ ጉዳዩን አምርሮ ሲቃወም አልተሰማም።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተ/ቤተክርስቲያን ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ለቪኦኤ የአማርኛው አገልግሎት ላይ በተሰማ የ 2006 ዓም የትንሣኤ መልካም ምኞት መግለጫ ላይ ግብረ ሰዶማዊነትን በእጅጉ ኮንነው መግለጫ ሰጥተዋል።በመግለጫቸው ላይም “በአገራችን ላይ ልማትና ዕድገት ሳይሆን መቅሰፍትና ውርደት እንዳያስከትልብን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ግብረ-ሰዶምን በፅናት መመከት አለበት” ብለዋል።

ባጠቃላይ የግብረ ሰዶማዊነት ጉዳይ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ቀድማ መናገር የሚገባት ሆና ሳለ በተገቢ መንገድ መንግስቷ አለመናገሩ ብዙ አፍሪካውያን ያሳዘነ ጉዳይ እንደሆነ በሚሰማበት ወቅት ይደረጋል የተባለው ሰልፍ እርግጠኝነት አለመታወቁ እና መንግስት ተገቢውን ድጋፍ አለማድረጉ ብዙ ኢትዮጵያውያንን መንግስት ከምዕራባውያን የሚያገኘው እርጥባን እንዳይቀርበት ብሎ የሚያደርገው ነው ሲሉ ይተቻሉ።በተጨማሪም ጉዳዩን ለ 2007 ዓም ምርጫ ከምዕራባውያን ለማግኘት የሚፈልገውን ድጋፍ ማግኛ ካርድ ያደርገው ይሆን እንዴ? የብዙዎች ጥያቄ ነው።

ጉዳያችን
ሚያዝያ 10/2006 ዓም 

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።