ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, March 24, 2014

የኑሮ ውድነቱ እና የትናንቱ የኢህአዲግ ስብሰባ አስገራሚ ድምዳሜ

የኑሮ ውድነት መድረሻው አይታወቅም 

ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የኑሮ ውድነት በብርሃን ፍጥነት እየተመነጠቀ ነው። አንዲት ፌስ ቡክ ፀሐፊ እንዳለችው እኛም ከሶስት እና አራት ዓመታት በፊት የነበረውን ዋጋ እየጠቀስን ለዛሬ ልጆች ''በእኛ ጊዜ እኮ በ 90 ሳንቲም የ 45 ሳንቲም መሄጃ 45 ሳንቲም መመለሻ ታክሲ እንጠቀም ነበር፣በእኛ ጊዜ እኮ አንድ ኪሎ ስጋ በ 22 ብር እንገዛ ነበር፣በ እኛ ጊዜ እኮ አንድ ብር ካለን በ 75 ሳንቲም እስክርቢቶ ገዝተን በ 25 ሳንቲም ጀላቲ ገዝተን ዘነጥ ብለን ጀላትያችንን እየመጠጥን ወደ ቤት እንመጣ ነበር።'' ልንል ነው ያለችውን ያነበብኩት ዛሬ ነው።

የኑሮ በብርሃን ፍጥነት ደረጃ መወደዱን ለማስረዳት ደግሞ ይህንን ስሌት ማሳየት ተገቢ ይመስለኛል።

1/ ዘመን= 1983 ዓ ም የአንድ ምሩቅ ደሞዝ 500 ብር (ከእዚህ ላይ የመንግስት ግብር እና የጡረታ ይቀነሳል)

በ1983 ዓም  1 ዶላር = 2.07  ሲሆን የአንድ ምሩቅ ደሞዝ 500 ብር  ወደ ዶላር ሲቀየር 250 ዶላር ይሆናል።
በእዚህ ዘመን ኑሮ እርካሽ ነበር። ለምሳሌ፣ የአንድ ኪሎ ስጋ ዋጋ 5 ብር ነበር። አዲስ አበባ የሸዋ ዳቦ ቤት አንድ ዳቦ በ 10 ሳንቲም ይሸጣል። በ 1 ብር ከ 50ሳንቲም  ሽሮ ወጥ ከተሰነገ ቃርያ ጋር አዲስ አበባ ይሸጥ ነበር። አንድ ሊስትሮ ፓስታ በስጎ ከዳቦ ጋር በ 1 ብር መመገብ ይችላል።ለእዚህ ብዙዎች ምስክር ናቸው።
በወቅቱ አንድ 200 ብር የሚያገኝ ጡረተኛ  በትንሹ የቤት ኪራይ ከፍሎ 5 የቤተሰብ አባላት ያስተዳድራል።ይህ ማለት ከወር ወር የጤፍ እንጀራ እየበሉ ማለት ነው።

2/ ዘመን 2006 ዓም የአንድ ተመራቂ ደሞዝ 1,400 (ከእዚህ ላይ የመንግስት ግብር እና የጡረታ ይቀነሳል)

ዛሬ አንድ ዶላር =19.37ሳንቲም ይመነዘራል።ዛሬ የአንድ ተመራቂ ደሞዝ ካልተጋነነ 1,400 ብር(መንግስታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች) ከእዚህ ላይ የመንግስት ግብር እና የጡረታ ይቀነሳል።ይህ  በዶላር 72  ይሆናል ማለት ነው። ይህ ማለት አንድ ምሩቅ የዛሬ 23 ዓመት ያገኝ የነበረው 250 ዶላር የነበረ ሲሆን አሁን እያገኘ ያለው ግን 72 ዶላር ብቻ ነው።ይህ ማለት አንድ ምሩቅ ከዩንቨርስቲ እንደወጣ ማግኘት ያለበት 4,840 ብር ነበር ማለት ነው።ይህም የኑሮ ውድነቱን የሚያግዝ ሳይሆን በልቶ ለማደር ብቻ ነው።ዛሬ የሸቀጦች ዋጋ ስንት ነው? ጤፍ ኩንታል 1,400፣ስጋ 90 ብር፣ወዘተ

በኑሮ ውድነቱ ላይ የትናንቱ አስገራሚው የኢህአዲግ ድምዳሜ

''የኑሮ መወደዱን ኢህአዲግ በስብሰባው ላይ አንስቶት ነበር'' ያለው የዛሬ ሰኞ መጋቢት 15/2006 ዓም የኢቲቪ ዜና ኢህአዲግ ''መፍትሄው ምርትን ማሳደግ ነው ብሏል '' ሲል ተናግሯል።ለመሆኑ -

- 'ማክሮ ኢኮኖሚክስ' ለዋጋ መናር መፍትሄውምርት ማሳደግ ብቻ ነው ይላል?
- የወለድ መጠን፣የብሔራዊ ባንክ የገንዘብ አቅርቦት፣የውጭ ምንዛሪ ከሀገር ውስጥ ገንዘብ ጋር ያለው ተመን፣የስራ      ዕድል ፈጠራ፣የግል ዘርፉ ተሳትፎ፣ ባጠቃላይ የ'ሞነተሪ እና የፊዚካል' ፖሊሲው ተፈትሿል?
- መንግስት ከአቅም በላይ የገባበት ፕሮጀክት ለምሳሌ በኢንፍራስትራክቸር ላይ እስከ 60 በመቶ በጀት እየበላ መሆኑ (ምንም እንኩዋን ኢንፍራ ስትራክቸር አስፈላጊ ቢሆንም በሕዝብ የኑሮ ጉሮሮ ላይ መምጣት አይገባውም) እና ሌሎች ጉዳዮች ለኑሮ ውድነቱ መንስኤ መሆናቸውን ኢህአዲግ አያውቃቸውም?
- ቅጥ ያጣው ሙስና የገበያ ስርዓቱን አላናጋውም?
- በምግብ ላይ የተጣለው የ ቫት ቀረጥ ድሃው በሀገሩ የሚመረተውን የጤፍ እንጀራ እንዲናፍቅ አላደረገውም?

ጠቅላይ ሚኒስትሩን የከበቡት ወደ ደርዘን የሚጠጉ አማካሪዎች 'ማክሮ ኢኮኖሚውን' መፈተሽ አልቻሉም? ለማንኛውም ኢህአዲግ ''የኑሮ ውድነቱን ለማሸነፍ ምርትን ማሳደግ ነው'' ብሏል። በቃ ብሏል።ኢህአዲግ ያለውን ደግሞ ማን ይሽረዋል? ''ማክሮ ኢኮኖሚው ይፈተሽ'' ብሎ የሚከራከር ደግሞ ፀረ-ልማት ሊባል ይችላል።የገንዘብ እና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትሩ አቶ ሶፍያን አህመድ ስብሰባው ላይ እጃቸውን እንዳጣመሩ ተቀምጠው ይታያሉ።ከአንድም ሁለት ጊዜ በኢኮኖሚ ጉዳይ ላይ ትንታኔ ሲሰጡ  አይቻቸዋለሁ።ምንም አይነት ወረቀት ሳይመለከቱ የሚሰጡትን ትንታኔ ስመለከት የአቅም ችግር እንደሌለባቸው በአቅሜ ተረድቻቸዋለሁ።ጥያቄው ግን እሳቸውስ ይደመጣሉ ወይ? ነው።እሳቸውም ማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲው ይፈተሽ ብለው ተናግረው ተቆጥተዋቸው ይሆን እንዴ?

ጉዳያችን
መጋቢት 16/2006 ዓም 

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...