ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, March 24, 2014

‹‹ግዕዝ እንደ አንድ ቋንቋ መነጋገሪያ እስኪሆን ድረስ ወደኋላ አልልም›› መምህርት ኑኃሚን ዋቅጅራ


መምህርት ኑኃሚን ዋቅጅራ 28 ዓመቷ ሲሆን ተወልዳ ያደገችው በአዲስ አበባ መሳለሚያ አካባቢ ነው፡፡ ዕድገቷ በቤተ ክርስቲያን አካባቢ በመሆኑ ለግዕዝ ትምህርቷ መነሻ ሆኗታል፡፡

በደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል ካቴድራል ቅፅር ግቢ በቄስ ትምህርት የተጀመረው ትምህርቷ ዛሬ የግዕዝ መምህርት እንደትሆን አድርጓታል፡፡ የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት በሚሰጥበት አቡነ ጐርጐርዮስ ትምህርት ቤት ከአንደኛ እስከ 10 ክፍል የሚያገለግል የመማርያ መጻሕፍት ከዚህ ቀደም አዘጋጅታ አበርክታለች፡፡ የካቲት 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ደግሞ ማንኛውም የግዕዝ ቋንቋን ማወቅ የሚፈልግ የሚማርበት ‹‹ማህቶተ ጥበብ ዘልሣነ ግዕዝ›› የመጀመሪያ ክፍል መጽሐፍ አስመርቃለች፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ግዕዝን የሚያመሰጥሩ የሚያስተምሩና እንደ እማሆይ ገላነሽ ዓይነት ሴቶች ቢኖሩም ከግዕዝ መምህርነቷ በተጨማሪ በመጽሐፍ ከትባ ለማስቀመጥ የመጀመርያዋ ሴት መሆኗን መጽሐፉ በተመረቀበት ዕለት የተገኙት የግዕዝ መምህሩ ዜና እንዳለው ተናግረዋል፡፡ መምህርት ኑኃሚን በአማርኛ እንግሊዝኛ ቋንቋ ከቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ ዲፕሎማ፣ በሥነ መለኮት ከቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ ዲፕሎማዋን አግኝታለች፡፡ በግዕዝ ሥራዎቿ ዙርያ ምሕረት ሞገስ አነጋግራታለች፡፡

ሪፖርተር፡- ወደ ግዕዝ ትምህርት እንዴት ገባሽ?

መምህርት ኑኃሚን፡- ልጅ ሆኜ ፊደል የቆጠርኩት መሳለሚያ አማኑኤለ ቤተክርስቲያን ውስጥ በሚገኘው ቄስ ትምህርት ቤት ነው፡፡ እስከ ዳዊት ድረስ እንደተማርኩ ግብረሰናይ ድርጅት መጥቶ ለችግረኛ ተማሪዎች ትምህርት ቤት አቋቋመ፡፡ አማኑኤለ ግቢ የነበርነውን የቄስ ትምህርት ቤት ተማሪዎች በሙሉ የመጀመርያ ተማሪ አድርጐ ተቀበለንና አንደኛ ክፍል ገባን፡፡ የመደበኛውን ትምህርት እስከ 9፡30 እየተማርን የግዕዝ ትምህርቱን የምንፈልግ በግላችን ከ9፡30 አስከ 11፡00 ሰዓት መማር ጀመርን፡፡  

ሪፖርተር፡- ግዕዝ ያስተማሯችሁ ማን ናቸው?

መምህርት ኑኃሚን፡-  በጠልሰም ሥራ የአርት ፕሮፌሰር መጋቢ ሚስጥር ጌድዮን መኰንን ናቸው፡፡ ዛሬ ለደረስኩበት የግዕዝ ዕውቀት መሠረቱን ያስያዙኝ እሳቸው ናቸው፡፡ ከሕፃንነት ጀምሮ ግዕዝ አስተምረውኛል፡፡ 11ኛ ክፍል እስክደርስ ድረስ ግዕዙን ከእሳቸው እየተማርኩ ነበር፡፡ 11ኛ ክፍል እያለሁ እሳቸው በማረፋቸው ሊቀ ህሩያን መሃሪ አስተምረውኛል፡፡ እሳቸውም ብዙም ሳይቆዩ ነው ያረፉት፡፡

ሪፖርተር፡- ምን ያሀል ተማሪዎች ነበራችሁ?

መምህርት ኑኃሚን፡-  መደበኛ ትምህርት ላይ ብዙ ሆነን ነው የተማርነው፡፡ ግዕዙን በተጨማሪ የተማርነው ግን ጥቂት ነን፡፡ መምህራችን የሥነ ምግባር ጉዳይ ላይ ጠንካራ ናቸው፡፡ ግዕዙን ስንማር መሳሳት ያስቀጣል፡፡ ኃይለኛ ስለነበሩ ወላጆች ልጆቻቸውን ከትምህርት ቤት ማስቀረትን መርጠው ነበር፡፡

ሪፖርተር፡- እንዴት ልትቀጥይ ቻልሽ?

መምህርት ኑኃሚን፡- በትምህርቱ እንድገፋ ከጐኔ የነበሩት እናቴና ወንድሜ ናቸው ፡፡ ሐረር ያለው ወንድሜ የግእዝ ዕውቀት ብዙም ባይኖረውም ደብዳቤ ስጽፍለት በግዕዝና በአማርኛ እንዲሆን ያዘኝ ነበር፡፡ የፈተና ውጤት ይዤ ስገባም ቤተሰቦቼ አስቀድመው የሚያዩት የግዕዝና የሥነ ምግባር ውጤቶቼን ነበር፡፡ የግዕዝ ትምህርቴን እንድተው የአካባቢው ሰዎች እናቴን ቢወተውቷትም ፈቃደኛ አልነበረችም፡፡ ተገረፍኩኝ ብላ የምትቀር ከሆነ ራሷ ትወስን ነበር የምትላቸው፡፡ ሁሌም መምህር ተማሪዎቹ ውጤታማ እንዲሆኑለት ነው የሚቀጣው እኔም እንደትቀር አልፈልግም ትል ነበር፡፡ ቤተሰቦቼ ብርታት ሆነውኝ የግዕዙን ትምህርት ልቀስም ችያለሁ፡፡

ሪፖርተር፡- ሁለቱ የግዕዝ መምህራን ካረፉ በኋላ ትምህርቱን እንዴት ቀጠላችሁ?

መምህርት ኑኃሚን፡- ግቢው ውስጥ ግእዙን እስከ 11ኛ ክፍል የተማርኩት እኔ ብቻ ነበርኩ፡፡ መምህራኑ በሞቱ በዓመቱ የግዕዝ መምህር ቅጥር ማስታወቂያ ወጣ፡፡ ለውድድሩ የቀረብነው እኔና ሰባት መሪ ጌታዎች ነበሩ፡፡ አንድ ሴት ሰባት ወንድ ማለት ነው፡፡ በየገጠሩ ከውሻ ጋር እየተባረሩ ግዕዝ ከተማሩ ሰዎች ጋር እንዴት ትወዳደሪያለሽ በሚል ፈተና ገጥሞኝ ነበር፡፡ ቦታውን ያገኛል ተብሎ የተጠበቀውም ከመሪ ጌታዎቹ ውስጥ ነበር፡፡ መጋቢ ሚስጥር ጌድዮን ገና ተማሪ እያለን ያሉኝን ያስታወሰኝ ወቅት ነበር፡፡ ቅኔ ማህሌት ውስጥ ሴት መግባት ስለማትችል ከዛ ልንቀስም የምንችለውን ዕውቀት ለማግኘት ፈተና ነበር፡፡ መምህራችን ‘ወንድ ብትሆኑ ስሜን ታስጠሩ ነበር’  ይሉን ነበር፡፡ አባቴን ሁሌም ሴት ልጅ ስም አታስጠራም እንዴ? እያልኩም እጠይቀው ነበር፡፡ ‘ዋቅጅራ ተብሎ የኔ ስም የሚጠራው የአንቺ አባት ስለሆንኩ አይደል’ ይለኛል፡፡ በፈተናው ወቅትም ከአካባቢዬ የገጠመኝ ፈተና ይኸው ነበር፡፡ ሆኖም ፈተናውን አልፌ በደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል ካቴድራል አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የግዕዝ መምህርት ሆኜ በ1994 ዓ.ም. ተቀጠርኩ፡፡ ሁለት ዓመት እንዳስተማርኩ የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ማንኛውም መምህር የመምህርነት ትምህርት ማስረጃ ከሌለው ማስተማር አይችልም የሚል መመርያ አወጣ፡፡ እዚያው እያስተማርኩ ቅድስተ ማርያም ዩኒቨርሲቲ ገብቼ በ1999 ዓ.ም. በአማርኛ፣ እንግሊዝኛ ቋንቋ ዲፕሎማ ያዝኩ፡፡ 2000 ዓ.ም. ላይ በግዕዝና በሥነ ምግባር ትምህርት ዙርያ የሌሎች ሃይማኖት ተከታዮች ላይ ተፅዕኖ ትፈጥራላችሁ በሚል የካቴድራሉን ትምህርት ቤት ለመገምገም ከትምህርት ቢሮ ባለሙያዎች መጡ፡፡ ሁለቱንም ትምህርት የማስተምረው እኔ ስለነበርኩ የመንፈሳዊ ሥነምግባር ትምህርት በፍላጐት ብቻ የሚሰጥ መሆኑን፣ የግዕዝ ትምህርቱ ደግሞ የወንበር ትምህርት ማለትም ውዳሴ ማርያም፣ ገድላት፣ ተአምራትን ያካተተና የኦርቶዶክስ ሃይማኖትን ብቻ የሚመለከት በመሆኑ የእምነቱ ተከታዮች ብቻ የሚማሩትን ሳይሆን የግዕዙን ቋንቋ ትምህርት እንደማንኛውም አንድ የኢትዮጵያ ቋንቋ እንደሚማሩት አብራራሁ፡፡ የማስተምርበትን ወርሃዊና ዓመታዊ የትምህርት ዕቅድ አሳየኋቸው፡፡ ትምህርቱ ተከፋፍሎ የሚማሩበትን የኮምፒውተር ጽሑፍም አዩ፡፡ ገምጋሚዎቹ ስለግዕዝ ትምህርት የነበራቸው ግንዛቤ ከእምነቱ ጋር ብቻ የተያያዘ፡፡ ሆኖም ግዕዝ የወንበርና የቋንቋ ተብሎ የተከፈለ ተማሪዎቹም የሚማሩት የቋንቋውን ክፍል ብቻ መሆኑን አስረዳኋቸው፡፡ ከተማሪዎቹ ያገኙት መልስም ስለግዕዝ ቋንቋ ብቻ እንደሚማሩ ነበር፡፡  

ሪፖርተር፡- ካንቺ ከተረዱ በኋላ አስተያየታቸው ምን ነበር?

መምህርት ኑኃሚን፡- ስለምንሰጠው ግዕዝ ቋንቋ ትምህርት ካስረዳኋቸው በኋላ እስከምን ድረስ ትዘልቂበታለሽ ነበር ያሉኝ፡፡ የአምላክ ፈቃድ ቢሆን የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት አገር አቀፋዊ እንዲሆን ነው የምመኘው፡፡ ግዕዝ አገር አቀፍ ቋንቋ መሆን እንደሚችል አምናለሁ፡፡ አገር አቀፍ ቋንቋ ባይሆን ኖሮ በብሔራዊ ደረጃ የግዕዝ ቋንቋ ፈተና አይሰጥም ነበር፡፡ የግዕዝ ቋንቋ የተመቻቸ የትምህርት መሠረት ቢኖረው ማንኛውም ተማሪ መማር የሚችለው ነው አልኳቸው፡፡ ገምጋሚዎቹ ሀሳቤን ሲረዱ በክፍል በክፍል ከፋፍለሽ በመማርያ መጽሐፍ መልክ ብታዘጋጀው በኢትዮጵያ ደረጃ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ በዚሁ ብትቀጥይ ጥሩ ነው አሉ፡፡ ባለሙያዎቹ አስተያየቱን ከሰጡኝ በኋላ በሒደት ከአንደኛ እስከ 10 ክፍል በየክፍሉ የተከፋፈለ የግዕዝ ቋንቋ መማርያ መጻሕፍት አዘጋጅቼ በማኅበረ ቅዱሳን አቡነ ጐርጐርዮስ ትምህርት ቤት ጥቅም ላይ እየዋለ ነው፡፡    

ሪፖርተር፡- ማኃቶተ ጥበብ ዘልሣነ ግዕዝ አንደኛ መጽሐፍ ለማዘጋጀት ያነሳሳሽ ምንድን ነው?

መምህርት ኑኃሚን፡- ሦስት መሠረታዊ ነገሮችን ይዤ ነው፡፡ ደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል ካቴድራል እያለሁ ከትምህርት ቢሮ ከመጡት ገምጋሚዎች የግዕዝ ቋንቋን በቋንቋነቱ አብዛኛው ሰው እንደማያውቀው ተረዳሁ፡፡ ስለዚህ የግዕዝ ቋንቋን ማንኛውም ሰው መማር እንደሚችል ለማሳየት በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንም ቋንቋውን በአደራ ተቀብላ እየተጠቀመችበት እንጂ የግሌ ነው ብላ እንዳልያዘችውና ማንኛውም ሰው እንደ አንድ ቋንቋ መማር እንደሚችል ለማሳወቅ ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ግዕዝ ቋንቋን ማንኛውም ሰው መማር ይችላል፡፡ መሠረታችንም የግዕዝ ፊደል ነው፡፡ ያላወቅነው እንዴት እንደምንግባባበት ነው፡፡ ፊደል የቆጠረ ሁሉ አጠቃቀሙን ካለማወቅ እንጂ ግዕዝን ተምሯል፡፡ ሆኖም ከልጅነታችን ፊደል ቆጥረን እንጂ የግዕዝ አገባቡን ስለማናውቀው ግዕዝ ሞቷል የሚሉ አሉ፡፡ ግዕዝ እንዳልሞተ የተማርነውና እየተማርነው ያለ እንዲሁም እየተጠቀምንበት መሆኑን ለመግለጽ ነው፡፡ ግዕዝ የኢትዮጵያ ቋንቋ እንደሆነ ለማሳወቅ ነው፡፡ ሦስተኛው ያጣኋቸውን መምህሬን መጋቢ ምስጢር ጌድዮን መኰን ለማሰብ ነው፡፡  

ሪፖርተር፡- መጽሐፉን ስታዘጋጂ ያጋጠሙሽን ችግሮች ብትጠቅሽልን?

መምህርት ኑኃሚን፡- ብዙ ተቸግሬያለሁ፡፡ የመጀመርያው የግዕዝ መምህሬ ሲያስተምሩን በቃል ነው፡፡ በቃል የተማርኩትን ወደ መጽሐፍ ለመቀየር መረጃ ያስፈልገዋል፡፡ ብዙ መጻሕፍት ማየት ነበረብኝ፡፡ እስከ 900 ብር አውጥቼ የኪዳነ ወልድ ክፍሌን ፅፌ ከእኔ ለተሻሉ የቤተክርስቲያን ምሁራንና አባቶች ሳስተችና ሳስገመግም ብዙዎቹ የተባበሩኝ ቢሆንም ጊዜ ወስዶብኛል፡፡ መጽሐፉ እንዲታተም ለማኅበረ ቅዱሳን የገባው በ2002 ዓ.ም. ነው፡፡ የወጣው ደግሞ 2006 ዓ.ም. ላይ ነው፡፡ መጽሐፉን ለማሳተም ስፖንሰር ለመሆን የፈቀዱ ሰዎች ሲዲውን ለማየት ከወሰዱ በኋላ ጠፍቶባቸዋል፡፡ ከማኅበረ ቅዱሳን 2003 ዓ.ም. ለመጀመርያው እትም ተብሎ የተከፈለኝም 5 ሺሕ ብር ነው፡፡ ከ1ኛ እስከ 8ኛ ክፍል ያዘጋጀሁትን የግዕዝ ቋንቋ መማርያ መጻሕፍት ያለምንም ክፍያ ነው በአቡነ ጐርጐርዮስ ትምህርት ቤት ጥቅም ላይ እየዋለ ያለው፡፡ ማበረታቻ ተብሎ ግን 4 ሺሕ ብር ተሰጥቶኛል፡፡ ሆኖም የልፋቴን ዋጋ አላገኘሁም፡፡ የ9ኛ እና የ10ኛ ክፍል የግእዝ መማርያ መጽሐፍ አዘጋጅቼም ማኅበሩ እየተጠቀመበት ነው፡፡ በሌላ በኩል በምፈልገው መጠን ሕዝቡ እጅ አልደረሰም፡፡ ከዚህ አንፃር ማኅበረ ቅዱሳን ለሕዝቡ በስፋት በሚያሠራጭበትና እኔም ተጠቃሚ የምሆንበትን መንገድ እንዲያሳውቀኝ በደብዳቤ ጠይቄያለሁ፡፡

ሪፖርተር፡- በግዕዝ ዙርያ እስከምን ድረስ ለመሄድ አስበሻል?

መምህርት ኑኃሚን፡- ግእዝ እንደ አንድ ቋንቋ መነጋገሪያ እስኪሆን ድረስ ወደኋላ አልልም፡፡ ብዙ ነገሮቻችንን ስናይ ከግዕዝ ቋንቋ ጋር የተያያዙ ናቸው፡፡ እኔ እዚህ ደርሻለሁ፡፡ ነገ የሚመጣው ትውልድ ከእኔ በተሻለ ቋንቋውን እንዲጠቀምበት እፈልጋለሁ፡፡  

ምንጭ - ሪፖርተር  ዕሁድ መጋቢት 14/2006 ዓም 

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...