ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, March 19, 2014

በኩዌት የሰሞኑ የኢትዮጵያውያን ችግር ከሳውዲው በተለየ አይን እንየው።ከሰሞኑ ክስተት ጋር በተያያዘ ምን ይደረግ?




በኩዌት አንዲት አትዮጵያዊት የአሰሪዋን ልጅ ገድላለች በሚል በኢትዮጵያውያን ላይ አንዳንድ ችግሮች እየተፈጠሩ መሆኑ እየተሰማ ነው።ሟች ኩዌታዊት ደግሞ  የዩንቨርስቲ ተማሪ መሆኗ እና በተለይ የኩዌት የስፖርት ሚኒስትር ልጅ መሆኗ ሁኔታውን አክርሮታል።

የኩዌት ጉዳይ ከሳውዲው በተለየ መልክ መታየት ያለበት ይመስለኛል። ኩዌት ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነት እንደ ሕዝብ ጠንከር ያለ ነው።ረጅም ግንኙነት ብቻ ሳይሆን በተለይ በደርግ ዘመን በኢራቅ ወረራ ሳብያ ኢትዮጵያ ከኩዌት  መቆሟ በኩዌታውያን ዘንድ ከፍ ያለ ዋጋ ተሰጥቶታል። ለእዚህም ነው ኩዌት ከ ኢራቅ እጅ እንደወጣች ልዑካንን ልካ ኢትዮጵያን ማመስገን ብቻ ሳይሆን ለቦሌ አየር ማረፍያ ተርሚናል ማስፋፍያ ከሰላሳ ሚልዮን ዶላር በላይ ያፀደቀችው በደርግ ዘመነ መንግስት ነው።ፕሮጀክቱ ደርግ ከወደቀ በኃላም እንዲከናወን ቃሏን ጠብቃለች።ኩዌት  ኢትዮጵያን የምታይበት የተሻለ አይን አላት።አሁን በኩዌት ከሰማንያ ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን እንዳሉ ይነገራል።

ከሰሞኑ ክስተት ጋር በተያያዘ ምን ይደረግ?

ከሰሞኑ ክስተት ጋር በተያያዘ መከናወን ያለባቸው ሁለት ነገሮች ይመስሉኛል -

1/ ኩዌት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በመጀመርያ  ሕይወቷ ላለፈው የኩዌት ወጣት ማዘናቸውን መግለፅ አለባቸው።ይህ ተገቢ ነገር ነው።ወጣቷ የዩንቨርስቲ ተማሪ ሕይወቷ አልፎ ስለሷ ማዘናቸውን ሳይገልፁ ስለበደል ቢወራ የሚሰሙ ኩዌታውያን አይኖሩም።እንደሚባለው ከሆነ ኢትዮጵያውያን ይባረሩ የሚል ሰልፍም በተውሰኑ ሰዎች ተዘጋጅቶ ነበር። ይህ የወጣቷ መሞት የፈጠረው የቁጣ ስሜት ነው።ለምን ተቆጡ? ማለት አይቻልም።በመሆኑም ኢትዮጵያውያን በኮሚኒቲያቸው አማካይነት ከፍተኛ የሀገሪቱን አካላት በማግኘት በሁኔታው ማዘናቸውን መግለፅ እና ገድላለች ለተባለቸው ወጣት ጠበቃ ማቆም ብሎም ነገሩ የሚድያ ሽፋን እንዲያገኝ ማድረግ ተገቢ ነው።በተለይ ኢትዮጵያውያን በሞተችው ልጅ ማዘናቸውን በሚድያ እንዲገለፅ እና ህዝቡ እንዲያውቅ ማድረግ አለባቸው።

2/ የመንግሥታት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ዞሮ ዞሮ የወሳኝነት ሚና ስለሚኖረው መንግስት ከፍተኛ ልዑክ ልኮ ኢትዮጵያውያን በግድያው ማዘናቸውን መግለፅ እና በቀሩት ኢትዮጵያውያን ላይ የሚደርሰው ከስራ መፈናቀል እንዲቆም እንዲደረግ ባልታወቁ ኩዌታውያን ተገላለች የተባለችው ኢትዮጵያዊት ጉዳይ እንዲጣራ ቢጠይቅ እና ወደሀገራቸው መመለስ የሚፈልጉ ኢትዮጵያውያንን መመለስ መጀመር አለበት ብዬ አስባለሁ።

ከእዚህ በተለየ ግን እንደ ሳውዲ አረብያ በማኅበራዊ ድረ-ገፆች ቸኩለን የኩዌትን ሕዝብ ወደመውቀሱ ባንሄድ ለእዚህ ጊዜው ገና ነው ብዬ አስባለሁ።ኩዌት ኢትዮጵያውያንን ታከብራለች።በእያንዳንዱ ጉዳዮች ላይ እንደ ሕዝብ እሰጥ አገባ መቀያየር  እንደ ሀገርም የኢትዮጵያን  ወዳጆችን ማጣት ነው። ከእዚህ ደግም ተጠቃሚ የለም።እንደዘለቄታ ግን በአረብ ሃገራት ያሉ ኢትዮጵያውያን ከሚጠቀሙት የምጎዱበት መንገድ እስከ በዛ ድረስ ያለቻቸውን እየያዙ ወደሃገራችው የሚገቡበት መንገድ መፈለግ ይገባል። በታወቀ የፖለቲካ ችግር ምክንያት መግባት የማይችሉት ደግሞ ወደሶስተኛ ሀገር እንዲገቡ የሚመቻችበትን ሁኔታ መፈለግ ሌላው መንገድ ይሆናል።እስኪ ስለ ኩዌት የበለጠ ግንዛቤ ይላችሁ ደግሞ አክሉበት።

ጉዳያችን
መጋቢት 11/2006 ዓም 

No comments: