ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, February 13, 2014

ጠቅላይ ሚኒስትር 25% የአዲስ አበባ ሕዝብ ውሃ አያገኝም ማለት 1,000,000 የሚጠጋ ሕዝብ ማለት መሆኑን ልብ ያሉት አልመሰለኝም።...የውሃ፣የመብራት እና የስልክ ነገር።




የመብራት ነገር 


በያዝነው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ አንድ ጋዜጠኛ የመብራት፣የውኃ እና የስልክ መስመር  ችግርን የገለፀበት አገላለፅ የችግሩን ስፋት የሚያሳይ ነበር።ጋዜጠኛው በጥያቄ መልክ ሲያቀርብ - ''መብራት በተደጋጋሚ ከመጥፋቱ የተነሳ (ብልጭ ድርግም ሲል) የአዲስ አበባ ቤቶች የናይት ክለብ የሚመስሉበት ሁኔታ ነው ያለው''

የስልክ ነገር 


ስልክን በተመለከተ ጋዜጠኛው ቀጠለ- '' ስልክ አንዳንድ ቀን እንድያውም በጠቅላል በከተማው ይጠፋል። ሰው ይታመማል አምቡላንስ መጥራት ብንፈልግ እንዴት እንሆናለን አስቡበት እንጂ?''ብሎ ሲጠይቅ አቶ ኃይለማርያም ቴክኖሎጂው ከኖርዌይ እና ዴንማርክ ጋር እኩል እንደሆነ ኮራ ብለው ነገሩት።''ችግሩ'' አሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀጥለው የቀደመውን ሲስተም በአዲስ ስንቀይር ሊቆራረጥ ይችላል'' አሉ።

ቴሌ ከእዚህ በፊት ለመስመር መቆራረጥ የሰጠው መልስ ግን የተለያየ ነበር። አንድ ጊዜ ''ኬብል እየተሰረቀ ነው።''ሌላ ጊዜ ''ህንፃዎች እየከለሉት ነው-----ህንፃ ላይ እንትከል ስንል ባለቤቶች ይከለክሉናል።'' ዛሬ ጠቅላይ ሚኒስትር ደግሞ ''በአመት 6 ቢልዮን ትታለባለች'' ያሏት ቴሌ መስመር በኖርዌይ እና ዴንማርክ የስልክ ደረጃ እየዘረጋን ስለሆነ ነው። አሉን።ሙስና፣የተማረ የሰው ኃይል ፍልሰት፣ወዘተ የሚሉትን እውነተኛ ምክንያቶች ታሽገው የሚፈታቸው ጠፋ።

ባለፈው ወር ይመስለኛል አዲስ አበባ በሚገኝ  አንድ ኤፍ ኤም መዝናኛ ፕሮግራም ላይ የስልክ ኔት ወርክ ችግርን ሲያስረዳ ጋዜጠኛው እንዲህ አለ '' አሁን አሁን ስልክ እያወራህ መስመር ሊጠፋ ስለሚችል መጀመርያ የምታወራውን ሰው ስታገኝ ''ስልኩ ከተዘጋ ቻው! ልበልህ  ትልና ነው ወደ ንግግርህ የምትገባው ስልኩ በመሃል ቢቆም ወዳጅህ ቻው! አላለኝም ብሎ አይቀየምህም'' ብሎ አስቆን ነበር።በነገራችን ላይ ባለፈውም አመት ሆነ በእዚህ አመት የአዲስ አበባ ኤፍ ኤም ራድዮኖች ካስተናገዱት የስልክ ጥሪ ውስጥ አብዛኛው መብራት እና ውሃ ሄደብን መሆኑን እራሳቸው ደጋግመው የሚያሰሙት ጉዳይ ነው።ህዝቡ መብራት እና ውሃ መስርያቤት አልሰማ ሲሉት ኤፍ ኤም ራድዮኖች ላይ እየደወለ ያለቅሳል።

የውሃ ነገር 


ሌላው ለአቶ ኃይለማርያም የቀረበው ጥያቄ የውሃ ጉዳይ ነው። ''ውሃ በከተማው የለም ሰው ቢጫ ጀሪካል ይዞ እየተንከራተተ ነው አንዳንድ ቦታዎች እስከ 15 ቀናት ያክል ውሃ አያገኙም መፍትሄው ምንድን ነው?'' ተብለው ሲጠየቁ

'' የከተማው ሕዝብ 25% ነው ውሃ በበቂ ሁኔታ የማያገኘው የቀረው 75% እያገኘ ነው።''ካሉ በኃላ የጋዜጠኛው ሰፈር ከ 25% ውስጥ ሊሆን እንደሚችል ነግረውት አረፉ።

በነገራችን ላይ ውሃ ከድሬዳዋ እስከ መቀሌ ድረስ ከፍተኛ ችግር አለ።አንድ ሕዝብ እድገት ቢቀርበት መሰረታዊ ፍላጎቶች ምግብ፣ልብስ እና መጠለያ ባይሟላለት ውሃ ግን የመኖር እና ያለመኖር ጉዳይ ነው።ቀን አይሰጠውም። አቶ ኃይለማርያም 25% የአዲስ አበባ ሕዝብ ውሃ አያገኝም ያሉት ከጠቅላላው የአዲስ አበባ ነዋሪ 1/4ኛው ማለትም  1,000,000 የሚጠጋ ሕዝብ መሆኑን ያሰቡት አልመሰለኝም።ምናልባት ቢሮ ከገቡ በኃላ ሲያሰሉት ይደነግጡ ይሆን?

ጉዳያችን
የካቲት 6/2006 ዓም


No comments: