ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, November 30, 2013

በእዚህ ዘመን ካሉት ከአዋቂዎቹ ይልቅታዳጊ ህፃናቱ የኪነጥበብ ባለሙያዎች የተሻለ የሀገር ፍቅር ያንፀባርቃሉ(ቪድዮ)

በእዚህ ዘመን አርቲስቶቻችን በእራሳቸው ምህዋር ውስጥ እየዞሩ ሀገራቸውን ባብዛኛው የዘነጉበት፣ለሙያ፣ለእውነት እና ለሕዝብ ፍቅር ከሚሰሩ ስራዎች ይልቅ ብዙ ብር የሚያስገኙ ስራዎች የተወደዱበት እና በሕዝብ ከመወደድ ይልቅ ከሚሊንየሮች ጋር ሸራተን መታየት የበለጠባቸው ዘመን እየሆነ ነው።እርግጥ ነው እንደ እነ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) አይነቶች በባትሪ ተፈልገው የተገኙ አልጠፉም።ኢትዮጵያ ግን የጥበብ ስራዋ በእዚህ አይነት ደረጃ ህዝብን እና ብሔራዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ስራዎች የወደቁበት ወቅት አሁን ነው።

እዚህ ላይ የኢትዮጵያ የኪ-ነጥበብ   እድገት እና ውድቀት ትንተና ላይ አይደለሁም።ሕዝብን፣ሃገርን የተመለከቱ ያለፈውን እና መጪውን የሚያማትሩ ስራዎች ግን በፈጣን ገንዘብ አስገኚ ስራዎች ተተክተዋል።ፊልሞች ወጣቶችን በፍቅር ታሪክ በማማለል ተሳክቶላቸው ይሆናል።ወጣቶቹ ወዴት እንደሚሄዱ፣ከየት እንደመጡ፣የጋራ ሃገራዊ እሴታቸው ምን እንደሆነ ግን አይነግሩም።ይህ በጣም ጥቅል እና በወፍ በረር የታየ ሃሳብ ይሆናል።በእዚህ ዘመን ካሉት አዋቂዎቹ ታዳጊ ህፃናቱ የኪነጥበብ ባለሙያዎች የተሻለ የሀገር ፍቅር ያንፀባርቃሉ።

ለናሙን ከእዚህ በታች ያሉትን የሸገር ራድዮ ለወጣት ሴቶች በራስ መተማመን ዙርያ የሚያስተምርበት ''የኛ'' የተሰኘ ተከታታይ ተውኔት ላይ የሚሰሙ ዜማዎች ናቸው። ቀደም ብሎ የወጣው ''አቤት'' የተሰኘው ዜማ የ2005 ዓም የዓመቱ ምርጥ ዜማ ተብሎ በሕዝብ ተመርጧል።በቅርቡ በተቀረፀው ''እቴጌ'' በተሰኘው ዜማ  ላይ ደግሞ ታዳጊ ህፃናቱ አስቴር አወቀ እንድትሳተፍበት አድርገዋል።ይመልከቷቸው።





Wednesday, November 27, 2013

ሰበር ዜና በሰሜናዊ ኢትዮጵያ በሁመራ ቃፍታ ወረዳ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር የሰነዘረውን ጥቃት ከመንግስት አካል በኩል ተረጋገጠ


በሰሜናዊ ኢትዮጵያ በሁመራ ቃፍታ ወረዳ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ከጋምቤላ ሕዝብ ነፃነት ንቅናቄ ጋር በመሆን  የሰነዘረውን ጥቃት የወረዳው የፀጥታ ኃላፊ ገዛይ ዳኘው ለአካባቢው ራድዮ ማመናቸውን ቪኦኤ የአማርኛው አገልግሎት ዛሬ ህዳር 18/2006 ዓም አስታወቀ።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሽምቅ ውግያ ሂደቶች ከሰሜናዊ ኢትዮጵያ በኩል እየተሰማ ነው።''የግንቦት 7 ሕዝባዊ ኃይል'' እና ''የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር'' ያሰለጠኗቸውን ሰራዊቶች ማስመረቃቸውን በእዚሁ በያዝነው ህዳር ወር ላይ ማስታወቃቸው ይታወቃል።

በእዚሁ ወር ኢሳት ለወራት በኢህአዲግ-ወያኔ ሲቀናበር የነበረ ኤርትራ በሚገኙ  በግንቦት 7 ሕዝባዊ ኃይል አመራሮች ላይ ግድያ ለመፈፀም የተሸረበ ሴራ መጋለጡ መዘገቡ ይታወቃል።የሴራው ሂደትም ኢህአዲግ-ወያኔ በቁጥር አንድ ያስጨነቀው ጉዳይ ወደ ትጥቅ ትግል የገቡ ኃይሎች መሆናቸውን ያመላከተ አይነተኛ ማስረጃ መሆኑን ብቻ ሳይሆን የአሁኑ ሂደት ከእዚህ በፊት ከነበሩት ሁኔታዎች የተለየ ነባራዊ ሁኔታ መኖሩን ብዙዎች ይስማማሉ።

ዛሬ ቪኦኤ የመንግስት መዋቅር የትግራይ ምዕራባዊ ዞን ቃፍታ ወረዳ የፀጥታ ኃላፊ ውግያውን ማመናቸውን ለአካባቢው ራድዮ መናገራቸውን ከመግለፁም በላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር የውጭ ግንኙነት ኃላፊ አርበኛ ኑር ጀባን ቃለ መጠይቅ አድርጎላቸዋል።አርበኛ ኑር ጀባ ስለውግያው ሲናገር  በ24ኛ ክፍለ ጦር ላይ ጉዳት ማድረሱን እና በርካታ ቀላል እና ከባድ የጦር መሳርያዎችን መማርኩን ገልጧል።በነገራችን ላይ ኢሳት በትናንትናው እለት ቀደም ብሎ ዜናውን ማወጁ ይታወቃል።በውቅቱም ጦርነቱ የተደረገው ህዳር 13/2006 ዓም መሆኑ ተዘግቦ ነበር።

ከእዚሁ ጋር በተያያዘ ሰሞኑን ኢትዮጵያ ውስጥ በሌለበት ፍርድ ቤት ተከሶ የነበረው በአሁኑ ወቅት የግንቦት ሰባት ሕዝባዊ ኃይል አመራር ካሴ ዘመነ ''ከወያኔ ጋር ከአሁን በኃላ የምንገናኘው ቃሊቲ ወይም እስር ቤት ሳይሆን ጦር ሜዳ ነው እዝያው እንገኛኛለን'' ያለውም በእዚሁ በያዝነው ሳምንት ነው።

ዛሬ ግንቦት 19/2006 ዓም ዘግይቶ በወጣ ዘገባ ራድዮ ፋና በድህረገፁ ጥቃቱን አምኗል።

ጉዳያችን
ህዳር 19/2006 ዓም

Monday, November 25, 2013

ኢትዮጵያዊ ቆስሎም እንዲህ ይከበር ነበር።በኮርያ ዘመቻ ላይ ተሳትፈው ለቆሰሉ ሰላሳ የኢትዮጵያ ወታደሮች ቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ በተኙበት የጀግና ሜዳልያ ሲሸልሟቸው (ታሪካዊ ፎቶ)

ኢትዮጵያዊ ቆስሎም እንዲህ ይከበር ነበር።በኮርያ ዘመቻ ላይ ተሳትፈው ለቆሰሉ ሰላሳ የኢትዮጵያ ወታደሮች ቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ በተኙበት የጀግና ሜዳልያ ሲሸልሟቸው (ታሪካዊ ፎቶ)

በኮርያ ዘመቻ የዘመቱት የኢትዮጵያ ወታደሮች አስከሬንም ሆነ ቁስለኛ 9,252 ኪሎ ሜትሮች ተጉዞ ለሀገሩ አፈር ይበቃ ነበር። ዛሬ ዓለም በሰለጠነበት እና መገናኛ በተስፋፋበት ዘመን ሳውዲ ውስጥ ወገኖቻችን አሳራቸውን የሚያዩት በ 1,900 ኪሎሜትር ማለትም የሁለት ሰዓት ተኩል የአይሮፕላን በረራ እርቀት ላይ ሆነው ነው።


Saturday, November 23, 2013

በዓለም ላይ በሳውዳረብያ በወገኖቻችን ላይ የደረሰውን ሰቆቃ ለመቃወም ሰልፍ የከለከለች ብቸኛ ሀገር-ኢትዮጵያ ነች። ይህ እንቅልፍ ያስወስዳል?

አዲስ አበባ ፌድራል ፖሊስ የሳውዲን መንግስት ለመቃወም ሰልፍ የወጡትን ሲደበድብ 

በዓለም ላይ በሳውዳረብያ በወገኖቻችን ላይ የደረሰውን ሰቆቃ ለመቃወም ሰልፍ የከለከለች ብቸኛ ሀገር-ኢትዮጵያ ነች።
ኢትዮጵያውያን በሳውዲ አረብያ በወገኖቻችን ላይ የደረሰውን ሰቆቃ አስመልክተው

ሰሜን አሜሪካ 

 - የተለያዩ ግዛቶች

 በአውሮፓ-

በጀርመን፣

እንግሊዝ፣

ጣልያን፣

ስዊድን፣

ኖርዌይ፣

 ካናዳ-

የተለያዩ ግዛቶች 

 አውስትራሊያ


መካከለኛው ምስራቅ 

- እስራኤል፣
- ቤሩት 

አፍሪካ 

 ደቡብ አፍሪካ፣

 ዑጋንዳ ፣

እስያ 

 ደቡብ ኮርያ፣

 በሚገኙ የሳውዳረብያ ኤምባሲ ፊት ለፊት ሰልፍ አድርገዋል።በለቅሶ በቁጭት እንባ ተራጭተዋል።ኤርትራውያን ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን አብረው ተሰልፈው ተላቅሰዋል ቁጣቸውን ገልፀዋል።

ቀሪ ሰልፎች ለምሳሌ በቤልጅየም ብራስልስ እና ሌሎችም ሀገሮች ይቀጥላሉ።
በዓለም ላይ የሳውዲን መንግስት ተቃውመው ዜጎች ሰልፍ እንዳይወጡ የከለከለች ብቸኛ ሀገር የጉዳዩ ባለቤት ኢትዮጵያ ብቻ ነች።ሌላ ማንም ሀገር አልከለከለም።

ኢትዮጵያ የሳውዲን ኢ-ሰብአዊ ድርጊት ተቃውመው ሰልፍ የወጡ እንቡጥ እና ለጋ ወጣቶችን፣አረጋውያንን፣አዛውንቶችን በፖሊስ እየደበደበች ብዙዎችን አካለ ስንኩል አደረገች።የቀሩትን  ሰልፉ የተደረገበት ቀን ሳትውል ሳታድር ወደ እስር ቤት ወረወረች።ይህንን የሚቀበል እንዴት አይነት ህሊና ነው?
ኢህአዲግ-ወያኔዎች ሆይ! ይህ ጠረንጴዛችሁ ላይ ያለ ያልተመለሰ ምን ጊዜም ልንረሳው የማንችለው ግን መልስ የሚሻ አጀንዳ ነው።

ጉዳያችን 

ህዳር/ 2006 ዓም 

Friday, November 22, 2013

አስር ጊዜ ከንፈር ከመምጠጥ ኢሳትን መርዳት!


የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥን -ኢሳት ከተመሰረተ ገና ሶስት አመታትን ቢያስቆጥርም በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ፣ማህበራዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ ጉዳይ ላይ ቁጥር አንድ ተፅኖ ፈጣሪ ሆኖ ወጥቷል።ዛሬ ዛሬ ኢሳት ባይኖር ኖሮ ስንት ሕዝብ ሊሰማቸው የሚገቡ ጉዳዮች ሳይሰሙ ሊቀሩ የመቻላቸውን ሁኔታ ስንመለክት ኢሳት ወሳኝ መሆኑን እንረዳለን።

በቅርቡ ከተከሰቱት የሙስሊሞች ጥያቄ፣በቤንሻጉል የጉርዳፈርዳ ነዋሪዎች መፈናቀል፣ሰሞኑን በሳውዲ አረብያ በወገኖቻችን ላይ የተፈፀመውን ግፍ ለሕዝብ በማድረስ በኩል ሁሉ የኢሳትን ታላቅ የስራ ክንውኖች የሚገልፁ ናቸው።ኢሳትን  ኢትዮጵያን የሚወድ ሁሉ ሊደግፈው የሚገባ ነው።የመረጃ  መታፈን ቁጥር አንድ ሉዓላዊነታችንን የሚያሳጣን መሆኑን የተገነዘበው ስንት ሰው እንደሆነ አላውቅም።ይህንን ስንረዳ የመገናኛ ብዙሃንን አስፈላጊነት እንረዳዋለን።ይህንን በደንብ የተረዳ የስርዓቱ ደጋፊ ቢሆንም ኢሳትን ለመርዳት ግዴታው ነው ብዬ አስባለሁ።ዛሬ ኢሳት እና ኢቲቪ ለሕዝብ በሚያቀርቡት ይዘት ተለያዩ እንጂ ሁለቱም የህዝብ ንብረት ናቸው።

ነገን አማትረን ስናይ ግን ኢትዮጵያ መንገዷ ሲሰምርላት ትልቅ አለማቀፍ የዜና አውታር እንደሚሆኑ አንጠራጠርም።ለእዚህ ሁሉ ግን ዛሬ ላይ ሆኖ ኢሳትን ማገዝ ከኢትዮጵያውያን የሚጠበቅ ትልቅ ቁምነገር ነው።ኢሳት በውጭ ከሚኖረው ሕብረተሰብ ማግኘት የሚገባውን ያህል እያገኘ አለመሆኑ በተደጋጋሚ የተገለፀ ጉዳይ ነው።አሁንም ጥያቄው ስንቶች በወር ሻይ ሲጠጡ ጉርሻ የሚሰጡትን ሃያ ዶላር በአግባቡ ይሰጣሉ? ነው።በቀን 2 ዶላር ብንሰጥ በወር 60 ዶላር መሆኑን ሳንረሳ ማለት ነው።አሁን የተጠየቀው በትንሹ 20 ዶላር ነው።ኢሳት በመጪው እሁድ ህዳር 15/2006 ዓም (ኖቬምበር 24/2013) ''እሳት የእኔ ነው'' የተሰኘ በቀጥታ ስርጭት ልዩ መርሃግብር አዘጋጅቷል።በዝግጅቱ ላይ በቀጣይነት የሚከፍሉ አባላትን ለማፍራት አስቧል።ቢያንስ ከቤት ሆኖ ይህንን መርሃግብር መሳተፍ ትንሿ ማንም ሰው ሊያደርገው የሚችለው ሥራ ነው።አስር ጊዜ ከንፈር ከመምጠጥ ኢሳትን መርዳት።ደግሞ መርዳት አይደለም ግዴታን መወጣት ነው።

ጉዳያችን
ሕዳር/2006 ዓም







Thursday, November 21, 2013

በሳውዲ አረብያ ያሉ ወገኖቻችን ጉዳይ ብዙ እርቀት መሄድ ይፈልጋል። ገጠራማው የሳውዳረብያ ግዛት የኢትዮጵያውያንን ሰቆቃ እያስተናገደ ነው።



ሳውዲ አረብያ ያሉ ወገኖቻችን ችግር ገና አልተቀረፈም።እስካሁን ባብዛኛው የታየው በከተሞች አካባቢ ያሉት ነው።ቢጮሁ የማይሰማበት ማንም የማይሰማቸው በገጠራማ የሳውዲ ግዛቶች ያሉ ብዙ ሺህ ወገኖቻችን ድረሱልን እያሉ ነው።ከከተማ እየጠለፉ የሚወስዷቸውን እህቶቻችንን የሚደብቁባቸው ቦታዎች እነኚሁ ከከተማ ራቅ ያሉ ቦታዎች ናቸው።

በኢሳት አስተባባሪነት የተመሰረተው ዓለም አቀፍ ግብረሃይል ለሳውዲ ንጉስ፣የደህንነት እና የፖሊስ መስርያቤት ግልፅ ደብዳቤ ፅፏል።ይህ የስራው መጀመርያ ነው።ግብረ ኃይሉ ከዲፕሎማሲ ሙያ ጀምሮ የተለያየ ሙያ ያላቸው ኢትዮጵያውያንን የያዘ ለእራሳችን ችግር መፍትሄዎቹ እኛው ነን የሚለውን ብሂል በተግባር ያመላከተ ድንቅ ጅምር ነው።በቀጣይ ጊዜ ለሚኖሩ የስራ ዝርዝሮች እንደሚኖሩት ይጠበቃል። የእዚህ አይነቱ ግብረ ኃይል በተጠናከረ መልክ በቀጣይነት ሊኖር የሚገባው እና ለሌሎች ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትን ለሚገዳደሩ ተግዳሮቶች ሁሉ ምላሽ የሚሰጥ እና አቅም የሚያጎለብት እንዲሆን የሁሉም ኢትዮጵያዊ ኃላፊነት ነው።

በሌላ በኩል ወደሀገር ቤት በመንግስት እየተመለሱ መሆናቸውን ኢቲቪ እያሳየ ነው።ስደተኞቹ በሲቪል ሰርቪስ ግቢ በግዝያዊነት ያረፉ እንዳሉ ተነግሯል። ሆኖም ግን በሺህ የሚቆጠር ኢትዮጵያዊ  ስደተኛ ሃሳሩን ከሚያይባት ሳውዲ አረቢያ መንግስት እስካሁን ሀገርቤት አድርሻለሁ ያለው ቁጥር ግራ እያጋባ ነው።ለምሳሌ  የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ፣የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ትዊተር ገፅ እና ኢቲቪ የተናገሩት የተምታታ ቁጥር ነው።ለምሳሌ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አቶ ዲና  4,961 ወደ ሀገርቤት አስገብተናል ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዶ/ር ቴዎድሮስ በትዊተር ገፃቸው ላይ የተመለሱትን ቁጥር 10,707 ናቸው ብለዋል።ዛሬ ኢቲቪ ደግሞ 13,000 ሰው ተመልሷል ብሏል።በዚህን ያህል ቁጥር የአንድ መንግስት ድርጅቶች እንዴት ይለያያሉ? በቁጥር ነገር መቸም መንግስትን ማመን እንደማይቻል ብዙ ምሳሌዎችን መጥቀስ ይቻላል።

የችግሩ ግዝፈት ግን ወደ ሀገር የማስገባት ሥራ ብቻ አይደለም። በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን በገጠራማ የሳውዲ ግዛቶች ውስጥ ይኖራሉ።በአንድ የዓለም ባንክ በአለማችን ላይ በገጠራማ ቦታዎች የሚኖሩ ህዝቦች ቁጥር በሚያሳይ ዘገባው ላይ ሳውዳረብያ በ 2012 ዓም እ ኤ አ ወደ 5ሚልዮን የሚጠጋ ህዝቧ ከከተማ እርቆ ነው የሚኖረው።(http://data.worldbank.org/indicator/SP.RUR.TOTL) እንግዲህ ስንት እህቶቻችን እና ወንድሞቻችን የሚሰማቸው አጥተው በየገጠሩ ሃሳራቸውን እያዩ ነው? ምን ያህል ኢትዮጵያውያን በሳውዳረብያ እንደሚኖሩ የኢትዮጵያ ኢምባሲ የጠራ መረጃ የለውም። አሁን ብዙዎቻችን ትኩረት የሰጠነው እና ስለችግሩ እየሰማን ያለነው በሪያድ እና ጅዳ አካባቢ ነው።በሌሎቹ አካባቢ ያሉት ወገኖች ጋር ለመድረስ ግን ምናልባት ጥቂት ሳምንታት ብሎም ወራት ልፈልግ ይቻላል።

 በሳውዲ መንግስት ላይ አስፈላጊው ዓለም አቀፍ ተፅኖ ለማድረግ ከተቻለ እና ተከታታይ እረፍት የለሽ ወቀሳዎች ከተሰነዘሩ ሳውዳረብያ ወደመሰላቸቱ ብቻ ሳይሆን በሃገሯ ካለባት ውስጣዊ ችግሮች አንፃር ለችግሩ መፍትሄ የማትሰጥበት ምክንያት የለም።ዓለም አቀፉ የኢትዮጵያውያን ግብረ ኃይል ግን ተከታታይ የስራ ሪፖርቶቹን ለሕዝብ እየገለፀ የራሱ የሆነ በጎ ተፅኖ መፍጠሩ አይቀርም። ከእዚህ በዘለለ በሌሎች የአረብ ሃገራት ላሉት ወገኖችም አንድ አይነት ማዕከልን የጠበቀ እርዳታ ለማድረግም ሆነ መብታቸውን እዲያስከብሩ ገንቢ ሃሳቦችን የማቅረብ ብሎም በየሀገራቱ የሚከራከርላቸው አካል ለመመስረት ይችላል።

ከእዚህ በታች የተለጠፈው የሩስያ ቲቪ (RT) ሳውዲን የተመለከተ ልዩ ዘገባ ሀገሪቱ ያለባትን የውስጥ ችግር ያመላክታል።የሀገሪቱን ኢ-ሰብአዊ አያያዝ ብቻ ሳይሆን የመንግስት መዋቅር ጭምር  ወጣቱ ንጉሳዊው ቤተሰብ የነቀፉበት አግባብን ዘገባው ይጠቁማል።



ጉዳያችን GUDAYACHNgetachewb221@gmail.com

Tuesday, November 19, 2013

Monday, November 18, 2013

ከሰሞኑ ጉዳይ መነሻነት ኢትዮጵያውያን ያላከናወናቸው ሁለት አበይት ተግባራት




ኢትዮጵያውያን ሰሞኑን በሳውዲ እየደረሰ ያለውን ችግር መፍትሄ እንዲኖረው  በአውሮፓ እና በአሜሪካ ከተሞች እንዲሁም ትናንት አርብ በአዲስ አበባ (በግፍ በእስር እና በድብደባ እስኪቆም ድረስ) በመሰለፍ ተቃውሟቸውን ገልፀዋል። ከእዚህ ሁሉ ሂደት የነጠሩ እና ወደፊት ሊነጥሩ የሚችሉ ነገሮችን ማውሳት ተገቢ መሰለኝ።

 በቅድምያ ግን ከሂደቱ የተረዳነው ጉዳይ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ችግሮች በተለይ ኢትዮጵያዊ ያልሆነ መንግስትን ከመደገፍ እና አይዞህ ባይነት ጋር በተያያዘ በቀጥታ እጃቸውን ያስገቡ መንግሥታት መኖራቸው ከምንጊዜውም በላይ ግልፅ ሆኗል።ኢሕአዲግ-ወያኔም ገንዘብ እና ድጋፍ ለሰጡት ሁሉ መታዘዙን እና ከስልጣኑ በላይ ምንም የሚያስቀድመው ነገር እንደሌለ በድጋሚ አስመስክሯል።ለእዚህም የማይካድ ሀቅ ሆኖ የወጣው የሳውዳረብያ መንግስት ምን ያህል በሀገራችን የፖለቲካ እና ምጣኔ ሀብት ጉዳይ ገብቶ እየፈተፈተ እና እያዘዘ መሆኑ በትናንትናው እለት በአዲስ አበባ በሰልፈኞች ላይ የደረሰው ድብደባ እና እስር ጥሩ ማሳያ ነው።

ከሰሞኑ ሰልፎች ጋር ተያይዞ ኢትዮጵያውያን ልናከናውናቸው የሚገቡ ሁለት አበይት ተግባራት


1/ በውጭ የሚኖረው ሕብረተሰብ አደረጃጀት ተፅኖ ፈጣሪ ማድረግ 


በውጭ የሚኖረው ሕበረተሰብ አሁን ካለበት አደረጃጀት በተሻለ እና ዓለማቀፋዊ መልክ በያዘ፣ በህብረተሰቡ ውስጥ ያሉ በትምህርትም ሆነ በገንዘብ አቅም የደረጁትን ብሎም አዳዲስ ሃሳብ የሚያፈልቁትን በማሰባሰብ አሁን ባለው የኢትዮጵያ ችግርም ሆነ ዘመን ተሻግሮ (ከለውጥ በኃላም) ኢትዮጵያን ለማንሳት ወሳኝ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው። በውጭ የሚኖረው ሕብረተሰብ አሁን አንዳንድ ችግሮች ሲፈጠሩ በተቃውሞ ሰልፍ ከመግለፅ ባለፈ ተፅኖ የመፍጠር አቅሙ በበለጠ መደራጀት አለበት።

ለምሳሌ በየሀገራቱ ያሉት የኢትዮጵያ ማህበረሰቦች (Communities) ለምን በዓለም አቀፍ ወይንም በአህጉር አቀፍ ደረጃ የመተዳደርያ ደንብ ቀርፀው የጋራ ሃገራዊ ራዕይ ቀርፀው በአጭር ጊዜ አይደራጁም? ይህ መደራጀት በፖለቲካ፣በኢኮኖሚ ማለት በውጭ ባሉ የንግድ ስራዎች እና በማህበራዊው በተለይ ባህላዊ እና ታሪካዊ እሴቶቻችንን በመጠበቅ እና ለቀሪው ዓለም በማሳወቅ ብሎም ባህሉ ለውጭው ዓለም ባህል እንዲሆን በመጣር ብዙ ተፅኖ የመፍጠርያ መንገዶችን ለመቀየስ ይቻላል። እናም ይህንን ሥራ በአፋጣኝ መስራት ሁሉም በውጭ ያለ ማሕበረሰብ  አባል እንዲሆን ማድረግ ይቻላል።

እዚህ ላይ የፖለቲካ እና የዘር አስተሳሰብ ችግሮች ያደናቅፉታል የሚሉ አስተሳሰቦች እንደሚኖሩ አስባለሁ። እነኝህ ችግሮች ግን በመተዳደርያ ሕጉ ሃገራዊ እና ኢትዮጵያዊ ራዕይ ላይ ከተመሰረተ ብዙ አንድ የሚያደርጉን ነጥቦችን ብቻ ለማጉላት ይረዳል።''ኢትዮጵያዊ አይደለሁም ወደፊትም አላስብም'' ያለ ወደ ኢትዮጵያዊነት እስኪመጣ ኢትዮጵያውያን ሥራ አይሰሩም ማለት አይቻልም እስከ ዕለተ ምፃትም ድረስ ሁሉ አንድ አይነት አስተሳሰብ እንብድኖረው እና ሃሳብ እንዲያመነጭ አይጠበቅም።ዛሬ ችግሩን የተረዳው ሥራ መስራት ይጀምራል ሌላው ይቀጥላል።

2/ ቀድመው ለሚጠብቁን የተቀነባበሩ የስነ-ልቦና ዘመቻዎች አለመጋለጥ 


ሰሞኑን ኢትዮጵያውያን ያደረጉትን የተቃውሞ ሰልፍ በማስመልከት ምን ሊደረግ እንደሚችል ቀድሞ መረዳት ተገቢ ነው።እንደ ጣኦት የሚመልኩት የሳውዲ ንጉሳውያን እና ልዑላን ምንም ማለት እንዳልሆኑ ኢትዮጵያውያን በተቃውሞ ሲናገሩ ማየት ለእራሳቸው ንጉሳውያን ቤተሰብ ብቻ ሳይሆን ለሚንቀጠቀጥላቸው  ሕዝብ ማስደንገጡ እና ማናደዱ አይቀርም።ይህ ማለት ሳውዲ አረብያ ባላት መንገድ እና መዋቅር ሁሉ ከወዳጆቿ ጋር ሆና ስሟን ለማደስ ከምትጠቀምበት መንገድ አንዱ ''ኢትዮጵያውያን በየሄዱበት ሕግ አያከብሩም'' ለማስባል እዚህም እዝያም ኢትዮጵያውያንን ስም ለማጉደፍ የሚሰሩ ቀላል የሚመስሉ ግን በዓለም አቀፉ ሕብረተሰብ ዘንድ በጊዜ ብዛት ተፅኖ የሚኖራቸው ተግባራት ሊኖሩ እንደሚችሉ መጠርጠሩ አይከፋም።ለምሳሌ በእየሃገራቱ ጋዜጦች ላይ አርቲክሎች የሚፅፉ ማዘጋጀት፣የቆዩ ቁርሾዎችን ማጉላት፣ኢህአዲግ- ወያኔን ትክክል እንደሆነ ለመሳል መሞከር ወዘተ ሊሆኑ ይችላሉ።

ለእዚህ ተግባር ደግሞ የሚተባበሩ የኢትዮጵያ ስም ሲጎድፍ የእነርሱ የሚተልቅ የሚመስላቸው ከቅርብም ሆነ ከሩቅ አይጠፉም። እዚህ ላይ እራሱ ኢህአዲግ-ወያኔም ተባባሪ እንደሚሆን ማረጋገጥ ይቻላል።በውጭ የሚኖረውን ሕብረተሰብ እንደ ጦር የሚፈራው እና የምጠላው ወያኔ-ኢህአዲግ ለምሳሌ ከሳውዲ መንግስት ጋር ሲነጋገር- ''ይህንን አመፅ የፈጠሩት በመሳርያ ኃይል ያስወገድኩት  የነፍጠኛ፣አክራሪ ክርስትያኖች፣ ፀረ አረብ አመለካከት ያላቸው ናቸው። የእነርሱ ወደ ስልጣን መምጣት ፀረ አረብ ስልጣን ያዘ ማለት ነው'' የሚል የሐሰት ገበያ ሊያደራ ይችላል።

ባጠቃላይ 


በመሆኑም ኢትዮጵያውያን በያሉበት ያሉትን የህዝብ ለሕዝብ ግንኙነት፣ጨዋነት፣ስነ-ምግባር እና ሌላውን የመረዳት ባህላችንን በጥንቃቄ ከመቸውም በበለጠ መልክ መያዝ ይገባናል።ከእዚህ በበለጠ ደግሞ ወደፊት የሚቀነባበሩልንን የስነ-ልቦና ዘመቻዎች ሰለባ ላለመሆን ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል።የስነ-ልቦና ዘመቻዎቹ እንደለመደብን ''ኢትዮጵያዊ በመሆኔ አፈርኩ'' የሚሉ ቃላትን ደጋግመን እንድንናገር ያደርገን እና መጨረሻው አደገኛ ወደ ሆነ  ትንታኔ ይወስደናል።ኢትዮጵያ ዛሬም እጅግ ሃብታም በተፈጥሮ የበለፀገች ሀገር ነች።ይህንን አሁንም ልንጠራጠር አይገባንም።ይህ ሕዝብ ታላቅ ሕዝብ ነው። የቀረን እና መከናወን ያለበት በዘር እና በጎሳ ከፋፍሎ እና ከባዕዳን ጋር ተባብሮ ወደ መጨረሻው ፈተና የሚገፋትን ስርዓት አንስቶ  በአፈራችን ላይ የመኖር መብታችንን ማስከበር ነው።ለእዚህም ኢትዮጵያዊ የፖለቲካ ራዕይ ማስቀመጥ እና ከወዲሁ ማዳበር ዛሬ  ጠንካራ የሆነ እንደ ''አለማቀፍ የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ'' ሁሉን አቀፍ ድርጅት መመስረት እና የፖለቲካ ፓርቲዎችን አቅጣጫ በማህበረሰቡ ፍላጎት እና ራዕይ ላይ ተመስርቶ አቅጣጫ መስጠት፣የሚ ታገዙትን ማገዝ አስፈላጊ የሆንበት ወቅት ላይ ነን። ለእዚህ ሁሉ ተግባራት ደግሞ ዘመኑ እራሱ አጋዥ ነው።ተግባሩን ለማከናወንም ሆነ ለማፋጠን የመገናኛ ቴክኖሎጂዎች ብዙ ፋይዳ አላቸው።

ጉዳያችን
ህዳር 7/2006

Sunday, November 17, 2013

በዛሬውም ሆነ በመጪው ትውልድ የሚጠየቁ ሁለት ''ለምኖች''



1/ ለምን አንድ 


ኢትዮጵያውያን  በሳውዲ ባሉ ወገኖቻችን ችግር  ላይ ከዋሽግተን እስከ አውስትራሊያ ሰልፍ ሲሰለፉ ለምንድነው በየሀገሩ ያሉ  የኢትዮጵያ ኢምባሲዎች በሰልፉ ላይ ያልተገኙት? ወይንም  ለምሳሌ የዛሬውን የዋሽግተን ሰልፍ አስመልክቶ  ቪኦኤ  ለዋሽግተን ኢትዮጵያ ኢምባሲ ቢደውልም ምላሽ አላገኘሁም ብሏል። ይህ የሀገራችን ጉዳይ አይደለም እንዴ? ሰልፉ የሳውዲ ኤምባሲን  ያስከፋው እንጂ የኢትዮጵያን ኢምባሲ ከሰልፉ ጋር እንዳይተባበር የሚያደርገው ምን አይነት ሐረካት ነው?

2/ ለምን ሁለት 


አሁንም በሺህ የሚቆጠር ኢትዮጵያዊ ሲሰለፍ ሳውዲ አረብያን ሲቃወም የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እና ራድዮ አንዲት እንዳይተነፍስ ያስገደደው ጉዳይ ምንድነው? ለቅሶው ለወገን፣እንባ መራጨቱ ለወገን፣ኢትዮጵይ ቴሌቭዥን ይህንን እነ ቢቢሲ፣ሲ ኤን ኤን፣ዋሽግተን ፖስት  የዘገቡትን የኢትዮጵያውያን የሳውዲ መንግስትን ተቃውሞ ለምን አላሳየም? ለምን? አዲስ አበባ ያለው የሳውዲ ኤምባሲ ሰራተኞች የአረብ ሻሂ ፉት እያሉ ስሙን የሳውዲ ቲቪ መባል እሩብ ጉዳይ የቀረውን ኢቲቪ ሲያደንቁት አይታያችሁም? ግን ለምን? ሼም  ኦን ኢቲቪ! ካለ ምንም ማጋነን ኢቲቪ ወቅታዊ አብሽቅ ነው።

እስኪ ደግሞ መጪውን ትውልድ እናስብ የዛሬ 30 ዓመት አንድ ኢትዮጵያዊ እንበል የዩንቨርስቲ ተመራቂ የመመረቅያ ፅሁፉን ''በኢትዮጵያ እና ሳውዳረብያ ግንኙነት ላይ''ሊሰራ ቢያስብ እና የሰሞኑን ሰልፎች ከቢቢሲ እና ሲ ኤን ኤን ላይ ወስዶ ከጠቀሰ በኃላ ኢቲቪ ስለሰልፎቹ  ምንም አለማለቱን ሲመለከት መደምደምያው ላይ ምን ብሎ ይፅፋል? ''ኢቲቪን የሳውዲ ገንዘብ ተቆጣጥሮት ነበር'' ብሎ? እስኪ አስቡት የት ነን? ማነው የሚገዛን? ያለቀስኩት- ከባዕድ ቆንስላ ፊት። የወቀስኩት- የውጭ መንግስትን። ኢቲቪ ምን ቤት ነው ድምፄን የሚያፍነው? ሳስበው ሳስበው ውስጤን እሬት እሬት አለኝ።

ጉዳያችን
ህዳር 9/2006 ዓም

Friday, November 15, 2013

የኢትዮጵያይውያን ተቃውሞ በ ኦስሎ፣ኖርዌይ ህዳር 5/2006 ዓም (ቪድዮ )

Ethiopians residing in Norway Demonstration against inhuman treatment of Saudi Arabia and EPRDF poor diplomatic enforcement November 14/2013 Oslo




ጉዳያችን GUDAYACHNgetachewb221@gmail.com

ለፋሺሽት ግራዝያኒ ዘብ የቆመው ወያኔ-ኢህአዲግ ወገኖቻችንን በግፍ ለገደለው ለሳውዲ መንግስት ታማኝነቱን በተግባር አሳየ።ወያኔ ገበናው ከምንጊዜም በላይ ፈጦ ወጥቷል።ጥያቄው ኢትዮጵያዊነት ወይንም ሞት!ነው።


አዲስ አበባ ሳውዲ አረብያ ኢምባሲ ፊት ለፊት በሰማያዊ ፓርቲ ዛሬ የተጠራው ሰልፍ በከፊል 

ቀደም ብሎ በጣልያን አፍሌ ግዛት ሊሰራ የነበረውን የሮዶልፍ ግራዝያኒ ሐውልትን በመቃወም ኢትዮጵያውያን አዲስ አበባ ላይ ያደረጉትን ሰልፍ የወያኔ-ኢህአዲግ ፖሊሶች ሰልፈኞቹን መደብደባቸው እና ለእስር መዳረጋቸው ይታወሳል።
(ለኢትዮጵያ ማን ይናገርላት? ጉዳያችን GUDAYACHN http://gudayachn.blogspot.no/2012/11/blog-post.html)

ዛሬ ህዳር 6/2006 ዓም የሰማያዊ ፓርቲ በሳውዲ የሚገኙ ወገኖቻችን ላይ የሚደርሰውን ግፍ በመቃወም አዲስ አበባ በሚገኘው የሳውዲ አረብያ ኤምባሲ ፊት ለፊት የጠራው ሰልፍ በፖሊስ ከመቆሙም በላይ በርካታ ወጣቶች እና አዛውንቶች በፖሊስ ተደብድበዋል የሰማያዊ ፓርቲ አመራርን ጨምሮ በርካታ ሰልፈኞች መስቀል ፍላወር አካባቢ እና አራት ኪሎ አካባቢ የሚገኙት ፖሊስ ጣቢያዎች ታስረዋል።''ጠላትማ ምንጊዜም ጠላት ነው አስቀድሞ ማለት አሾክሿኪውን ነው''።ወያኔ ገበናው ከምንጊዜም በላይ ፈጦ ወጥቷል።ለነፃነት የሚደረገው ትግል ለማደናቀፍ የቆሙት ኃይላትንም ከምንጊዜውም በላይ እየታወቁ መምጣታቸው ሌላው ክስተት ሆኗል።
ጥያቄው ኢትዮጵያዊነት ወይንም ሞት! ሆኗል።

የኢሳት ጋዜጠኛ መሳይ መኮንን ከጥቂት ሰዓታት በፊት በፌስ ቡክ ገፁ ላይ የለጠፈው እንዲህ የሚል ነበር-

'' በአዲስ አበባ ወሎ ሰፈር ሳኡዲ አረቢያ ኤምባሲ አከባቢ ከፍተኛ ድብደባ እየተፈጸመ ነው። አሁን በስልክ ያገኘኋቸው የሰማያዊ ፓርቲ ሌሎች አመራሮች በእንባ ታጅበው ሲቃ ይዟቸው ''የኢትዮጵያ አምላክ ይፋረደን'' ሲሉ ለኢትዮጵያ ህዝብ መልእክት አስተላልፈዋል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች ወጣት ይድነቃቸው ከበደ እና ወጣት ሀና ዋለልኝ ከፍተኛ ድብደባ ተፈጽሞባቸዋል። ወደ 50 የሚጠጉ የፓርቲው አባላትና የሰልፉ ታዳሚ ወደ እስርቤት ተወስደዋል። ''በህግ አምላክ! እያለን እየጮህን በፌደራል ፖሊስ ተቀጠቀጥን" አለ ወጣት ይድነቃቸው። ''ወገን አለቀ ሳኡዲ አረቢያ ከሚገደሉት ከሚቀጠቀጡት ባልተናነሰ እኛም በሀገራችን ግፍ ተፈጸመብን'' ብላለች ወጣት ሃና። ''ኢትዮጵያዊ መንግስት ከወዴት ነው ያለኧው?'' የዛሬው ከፍ ብሎ የሚሰማው ጩኧት!''

የሰማያዊ ፓርቲም ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ባወጣው መግለጫ እንዲህ ብሏል።


''በሳውዲ አረቢያ በሚገኙ ዜጎቻችን ላይ እየደረሰ ያለው በደል እና ስቃይ መጠኑ ከመጨመር አልፎ ሕይወትን እስከማሳጣት መድረሱ የሚታወቅ ነው፡፡ ይህን በደል እና ስቃይ ለመቃወም እና ሀዘናችንን ለመግለፅ በዛሬው ዕለት ማለትም ህድር 6 ቀን 2006 ዓ.ም አዲስ አበባ በሚገኘው በሳውዲ አረቢያ ኢምባሲ ፊት ለፊት ሰላማዊ ሰልፍ የተጠራ ቢሆንም በመንግሥት ታጣቂዎች በተወሰደ በአሰቃቂ እርምጃ ሰልፉ ሊካሄድ አልቻለም፡፡
እኛ ኢትዮጵያን በውጭ በሚገኙ ዜጐቻችን ላይ የሚደርሰው በደልና ግፍ እንዲቆም፣ ይህንንም ድርጊት የፈፀሙት ለሕግ እንዲቀርቡና የተጐዱ ዜጐች ተገቢውን ካሳ እንዲያገኙ፤ የኢትዮጵያ መንግሥትም በዜጐቹ ላይ ያሳየውን ቸልተኝነት በአስቸኳይ በማቆም ተገቢ የሆነውን የመንግሥት ኃላፊነት እንዲወጣ ቢጠየቅም፤ ሰልፉ በተቃራኒው በመንግሥት ታጣቂዎች በተወሰደ አሰቃቂ እርምጃ ተጠናቋል፡፡
በሳውዲ እየተፈፀመ ያለውን በደል በመቃወም በዓለም አቀፍ ደረጃ ኢትዮጵያዊያን ድምፃቸውን በማሰማት ላይ ቢሆኑም እኛ ኢትዮጵያዊያን ግን በገዛ ሀገራችን ድምፃችንን እንኳን እንዳናሰማ ታፍነናል፡፡ በዚህም እንቅስቃሴ ላይ የተሳተፉ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች፣ አባላት፣ ደጋፊዎችና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች ከፍተኛ ድብደባ፣ እንግልትና እስር ተፈፅሞባቸዋል፡፡
የመንግሥት ፖሊሶች የራሳቸውን ዜጋ በመደብደብና በማሰቃየት ብሎም በማሰር በሳውዲ በሚገኙ ኢትዮጵያዊ ወገኖቻችን ላይ የተፈፀመውን በደል ሀገር ውስጥ በሚገኙ ንፁሐን ወገኖቻቸው ላይ ደግመውታል፡፡
ይህ በውሸት ዲሞክራሲ ስም የተደበቀው አምባገነን መንግሥት ሕዝብን ለማሸማቀቅ የወሰደውን እርምጃ ወደ ጐን በመተው የኢትዮጵያ ሕዝብ ቅድም አያቶቹን በማስታወስ ያስረከቡትን ክብር ከማስመለስ ወደ ኋላ እንደማይል እርግጠኛ መሆናችንን እንገልፃለን፡፡
ፓርቲያችን እንዲህ አይነቱን የለየለት የመንግሥት ሕገ ወጥ ተግባር ትኩረት ሰጥቶ የሚመለከተው መሆኑን እየገለፅን፤ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከጐናችን እንዲቆም በአፅንኦት ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

ህዳር 6 ቀን 2006 ዓ.ም''




/////////////////////////////////።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።//////////////////////////////።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።

 -






Thursday, November 14, 2013

የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ በኖርዌይ (Ethiopian Community in Norway) በሳውዲ አረብያ የሚኖሩ ወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ላለው ሰቆቃ ያዘጋጀው ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ


የኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ በኖርዌይ (Ethiopian Community in Norway) ዛሬ ህዳር 5/2006 ዓም በሳውዲ አረብያ የሚኖሩ ወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ላለው ሰቆቃ ያዘጋጀው ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ቁጥሩ  ከፍተኛ የሆነ ሕዝብ በተገኘበት በኖርዌይ ዋና ከተማ በኦስሎ በሚገኘው የሳውዲ አረብያ ኢምባሲ ፊት ለፊት ተካሄደ።


ከቀትር በኃላ  በ10 ሰዓት የተጀመረው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ  በርካታ ወጣቶች፣ በእድሜ የገፉ አረጋውያን እና እድሜያቸው  ከአንድ ዓመት ያልዘለሉ ሕፃንትን የያዙ እናቶች ሁሉ የታደሙበት ነበር።እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት ድረስ በቆየው የተቃውሞ ሰልፍ ላይ -

- የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች ተወካዮች እና ሲቪክ ማህበራት ተወካዮች አጫጭር ንግግሮች አድርገዋል፣

- የሳውዲ አረብያ መንግስት በሀገሩ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ የሚያደርሰውን በደል የሚያጋልጡ በማህበራዊ ድህረ ገፆች የተለቀቁት ፎቶዎች በትልቁ ታትመው እንዲታዩ ተደርገዋል፣

- የተለያዩ መፈክሮች ተሰምተዋል፣

-  ለሳውዲ አረብያ ኢምባሲ የተዘጋጀው የተቃውሞ ደብዳቤ ተሰጥቷል፣

-  የሳውዲ አረብያ መንግስት ንጉሳውያን ቤተሰቦች የያዘ ፎቶግራፍን  እንዲቃጠል በማድረግ ሰልፈኛው ተቃውሞውን ከመግለጡም በላይ የኢትዮጵያ መንግስት ጉዳዩን በቸልታ እና ተገቢውን የዲፕሎማቲክ ግንኙነትን ያልጠበቀ አያይዝ ኢትዮጵያውያኑን በእጅጉ አስቆጥቷቸዋል። በሰልፉ ላይ ከተነገሩት ንግግሮች ውስጥ የኢህአዲግ ወያኔ መንግስት ለዜጎቹ የሚሰጠው ዋጋ በእጅጉ ያነሰ መሆኑ በተደጋጋሚ ከመወሳቱም በላይ አንድ ተናጋሪ '' ዛሬ ወገኖቻችን ሥራ ፍለጋ በእየ አረብ ሃገራቱ የሚሰደዱት ከ 40 ቢልዮን ብር በላይ በመዘረፉ መሆኑን መዘንጋት የለብንም ለእዚህም ተጠያቂው እራሱ ወያኔ ነው'' በማለት በምሬት ተናግረዋል።

በመጨረሻም  በሰሞኑ የሳውዲ ፖሊስ እና ወጣቶች  ተግባር የተጎዱ ኢትዮጵያውያንን  ፎቶ ሰልፈኛው ''ስራቸውን ይመልከቱት በማለት ኢምባሲው አጥር ላይ እንዲቀመጥ ከተደረገ በኃላ የሰልፉ ስነ ስርዓት ፍፃሜ ሆኗል።

የሰልፉን ገፅታ በከፊል የሚያሳየውን ፎቶ ከእዚህ በታች ይመልከቱ።














Tuesday, November 12, 2013

ሁሉም ሊደግፈው የሚገባ ታላቅ የተቃውሞ ሰልፍ በኦስሎ- ኖርዌይ Etiopiske Foreningen i Norge kaller en fredelig protest infront av Saudi Arabian Embasy i Norge.


ሐሙስ ህዳር 5/2006 ዓም 16:00 ሰአት በሳውዲ አረብያ በወገኖቻችን ላይ እየደረሠ ያለዉን እንግልት እና ግፍ ኦስሎ ከሚገኘው የሳውዲ አረብያ ኤምባሲ ፊትለፊት እንግለፅ!

Etiopiske Foreningen i Norge kaller en fredelig protest infront av Saudi Arabian Embasy i Norge, torsdag 14 november 2013 starter på 16:00 pm. Ulike Ethiooian Politiske organisasjoner, frivillige organisasjoner og religionsvitenskap institusjon vil bli med oss ​​på protesten.

Ethiopian Community in Norway call a peaceful Protest infront of the Saudi Arabian Embasy in Norway, Thursday November 14, 2013 starting at 16:00 pm. Different Ethiooian Political organizations, Civic Organizations and Religion institution will join us on the protest.

'ኢሕአዴጎች' ኢትዮጵያን የምታህል ታላቅ ሀገር ለማስተዳደር አቅሙም ብቃቱም የላችሁም!



ስራችሁን እያየን ጣልያን ለማታውቀው በባህር ሰምጠው ለሞቱት አፍሪካውያን ቀብር ባንዲራ ዝቅ አድርጋ መቅበሯን ማመስገን አለብን እንዴ?
እኛ የሞቱት፣የሚደበደቡት እና የሚደፈሩት እህቶቻችን አያሳዝኑንም?
ኢትዮጵያዊነት በእዚህ ደረጃ መዋረድ አለበት?
ኢቲቪ ከትናንት ጀምሮ ዛሬ ቀን ድረስ ስለጉዳዩ ምንም አላወራም።ስለተገደሉት፣ስለሞቱት እና ስለተደፈሩት ሴቶች የሚጠይቅ መንግስት የለንም።ከእንግዲህ ወዲህም መንግስት አለ ብለን እናወራለን?

ለመሆኑ የትኛው መንግስት ነው ከጠቅላይ ሚኒስትሩ  እስከ ደህነነቱ ድረስ ሌባ ሆኖ ዘብጥያ የወረደው?
የትኛው መንግስት ነው ዜጋው በሲቃ ላይ እያለ ሸራተን ሆቴል  የሚንደላቀቀው?
ድሮም በሙስና የተጨማለቀ መንግስት ሕዝቡን አይደለም እራሱንም ይሸጣል።የተበላ ብር ያሸማቅቀዋል።
ሊባኖስ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ በር ላይ ከእዚህ በፊት የሞተችው የእህታችን ዓለም ደቻሳን ጉዳይ እንደዋዛ ያለፈ መንግስት ዛሬም በብዛት ኢትዮጵያውያን ደም እንደጎርፍ ሲፈስ ቅንጣት ታህል አልተሰማውም። እኛም ያው ሆነናል።ሁላችንም ማውራት ማውራት አሁንም ማውራት ብቻ ሆኗል ዜማችን።ፓልቶኩ ማውራት ፌስ ቡኩ ማውራት።

ጥያቄው የትኛው የፖለቲካ ፓርቲ ምን አለ አይደለም እኔ ምን አልኩ?፣ እኔ ምን አደረኩ?፣እኔ ምን ላድርግ? ነው ወሳኙ ሥራ።
የእራስን ኃላፊነት መወጣት ነው ቁም ነገሩ።
ይህ ስሜታዊነት አይደለም።የማስተዋል ይልቁንም የእርጋታ ውጤት ነው።

እንደሰው ማሰብ ለቻለ ሰው ሁለት ነገሮች የኢህአዲግ መንግስትን ማንነት በትክክል ይገልጡለታል።
አንዱ ባለፈው ለግራዚያኒ ሊሰራ የነበረውን ዓለም የተቃወመውን የሀውልት ግንባታ በመቃወም ሰልፍ የወጡትን የገታበት ፋሽሽታዊ ቅኔ ሲሆን ሁለተኛው የሳውዲ አረብያውን ጉዳይ የያዘበት ዲፕሎማሲ ነው።ሌላው መንግስት ነኝ ተብዬው በየስርቻው የሚሰራውን ቤት ይቁጠረው።እነኚህ ስራዎች ብቻ በቂ ናቸው።

በአፄ ምኒልክ ዘመን የተሰራ ሐዲድ መስመር በ 21ኛው ክ/ዘመን ባቡር አስገባሁ እያለ የሚመፃደቁ ጉዶችን  ይዘን ድሮስ የት ይደረሳል? የዛሬ 100 ዓመት በፊት እኮ ከ 700 ኪሎ ሜትር በላይ ሐዲድ ኢትዮጵያ የዘረጋችው።ዛሬ እድሜ ለመንግሥታችን ከቆመ ሁለት አስርት አመታትን አስቆጠረ እንጂ።

ያን ጊዜ ሐዲዱ ሲዘረጋ ከአውሬ ጋር እየተጋፉ ሰው እየሞተ፣ውህ ጥም እየተቃጠለ ነው። ዛሬ በካቶ እያንጠለጠሉ ማስቀመጥን ''ጥሩ'' ከሚል ባለፈ ጧት ማታ እንድንዘምር እና የነፃነታችን ልዋጭ ልታደርጉት ትደፋፈራላችሁ።አሳዛኞች ምስኪኖች ናችሁ።ፖለቲካ እና ሰብአዊ አስተሳሰብን ለመለየት ያልታደለ ሰው ድሮስ ምን ሊሰራ ይችላል?

ጣልያን ከሽፍታ መንግስት በምን ይለያል? የሚሻልበትን ማንሳት ይበቃል።ጣልያን ኢትዮጵያን በወረራው ጊዜ ኢትዮጵያን በተባበሩት መንግሥታት ስር እንዲወክል አልጠብቅም።ግን በአንዲት ነገር እንደሚበልጣችሁ ልንገራችሁ።ምንያህል ስራችሁ  ኢትዮጵያዊ እንዳልሆነ ግልፅ አድርጎ ያሳያል።ጣልያን ኢትዮጵያውያንን ከአዲስ አበባ ከፒያሳ አካባቢ ስያፈናቅል መጀመርያ የጭቃ ቤት መርካቶ አካባቢ ገንብቶ ከጨረሰ በኃላ ነበር።እናንተ የአዲስ አበባን ሕዝብ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ እየነቀላችሁ ስታባርሩ ለኪራይ ይሁንህ እያላችሁ አልቤርጎ የማያሳድር ገንዘብ እየሰጣችሁ ነው ያባረራችሁት።

እናንተ ሕፃናትን በውጭ ምንዛሬ ገንዘብ እየተቀበላችሁ ከእናት አባት ሲነጠሉ ፈቃድ ይሰጥ የነበረው አሁንም የሚሰጠው የሰራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ነው።ከካቢኔ አባላችሁ አንዱ ሕፃናትን የሚሸጥ ሌላው ሴት እህቶቻችንን የማለፍያ ቪዛ የሚመታ የተቀረው በሕፃናቱ እና ሴት እህቶቻችን የተሰበሰበ የደም ዋጋ ወደ ካዝና የሚያስገባ ነው።ኢትዮጵያዊቷ ወጣት ለአረብ ሀገር ስትሸጥ እንደመንግስት ኃላፊነት አልተሰማችሁም።ዛሬ ተሸጠው ካለቁ በኃላ ወደ አረብ ሀገር መሄድ ተከለከል መሰል ዘፈን ሳትዘፍኑ በፊት ግን በአረብ ሀገር ኢምባሲ የሚሰሩ ሰራተኞቻችሁ በኢምባሲው ስልክ የአሰሪና ሰራተኛ አገናኝ ኢጀንሲ ሥራ ይሰሩ ነበር።

ዛሬ የሳውዲው ጉድ አፍጥጦ የመጣው እና ወገኖቼን የሚደበድበው በእናንተ የስልጣን ዘመን ሀገሬን የሚያውቃት ''ሽባብ'' የተሰኘው ወጣት ነው።ዛሬ እህቶቻችንን በየመንገዱ የሚደፍረው እናንተ ኢምባሲ ብላችሁ በምትጠሩት ቤት ውስጥ የበለጠ ደፋሪ እንዳለ የሚያውቅ ውስጥ አዋቂ ነው።

ከሁሉም በላይ የሚገርመው ደጋፊ ተብየዎቻችሁ ናቸው።አይናቸውን በጨው ሳይሆን በአሲድ ያጠቡ የዘመኑ ብልጣ ብልጦች 'አባይ ግድብ እና ባቡር ዝርጋታው ፖለቲካ አደለም ልማት ነው' ሲሉ ከርመው በሳውዲው ጉዳይ ላይ ግን የመንግስታቸውን ጉግ ማንጉግ በጨርቃቸው ለመሸፈን ፖለቲካ ነው መንግስትን ለማጥላላት ነው ለማለት  ይራወጣሉ።ቀድሞ ነገር ኢትዮጵያን የምታህል ታላቅ ሀገር ለማስተዳደር አቅሙም ብቃቱም የላችሁም።

ጉዳያችን
ህዳር 3/2006 ዓም


ከተቃውሞ ሰልፎቹ ጋር በተያያዘ ጠቃሚ መረጃ ..... የተባበሩት መንግሥታት ምን እያደረገ ነው?

Voting takes place in the General Assembly to elect 14 members of Human Rights Council. UN Photo/Evan Schneider

አስገራሚው የተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብት ምክርቤት ሳውዲ አረብያን የ 14ቱ የሰብአዊ መብት ምክርቤቱ አባል አድርጎ መምረጡን የተባበሩት መንግሥታት የዜና አገልግሎት ህዳር 3/2006 ዓም (Nov.12/2013) ገልጧል።

ይህ በጣም አሳፋሪ ሥራ ነው።በኒውዮርክ እና ጀኔቫ ተቃውሞ የምታደርጉ ይህንን ጉዳይ ታሳቢ ያደረገ ተቃሞ ማድረግ አለባችሁ።ለምሳሌ በእነኚህ ከተሞች የሚደረጉ ተቃውሞዎች ከፎቶግራፍ እና ፊልም ማስረጃዎች ጋር ተቃውሞው ለእራሱ ለተባበሩት መንግሥታት ማቅረቡ ፋይዳ ይኖረዋል።በተለይ የሳውዲ አረብያ መመረጥ በድርጅቱ በእርሱ ውስጥ በነበሩ ዲፕሎማቶች ዘንድ አከራካሪ ሁኔታ ፈጥሮ የነበረ መሆኑን ዘገባዎች ያወሳሉ።

United Nations News Centre
with breaking news from the UN News Service

http://www.un.org/apps/news/story.asp?NewsID=46476&Cr=human+rights&Cr1=#.UoOIlhaxNFI 
12 November 2013 – 
The General Assembly today elected 14 countries to serve on the United Nations Human Rights Council (HRC) for a period of three years beginning on 1 January 2014.

Algeria, China, Cuba, France Maldives, Mexico, Morocco, Namibia, Saudi Arabia, South Africa, the former Yugoslav Republic of Macedonia, Viet Nam, Russia, and United Kingdom, were elected by secret ballot today at UN Headquarters in New York.

Members of the Council serve for a period of three years and are not eligible for immediate re-election after serving two consecutive terms.

The Council, composed of 47 members, is an inter-governmental body within the UN system responsible for strengthening the promotion and protection of human rights around the globe and for addressing situations of human rights violations and make recommendations on them.

All of its members are elected by the world body’s General Assembly, and it has the ability to discuss all thematic human rights issues and situations that require its attention throughout the year. It meets at the UN Office at Geneva.

The Council’s membership is based on equitable geographical distribution and seats are distributed as follows:

13 seats for African States,
13 seats for Asian States,
8 seats for Latin American and Caribbean States,
7 seats for Western European and other States,
and 6 seats for Eastern European States.
The other members of the Council and the end of their terms are as follows:
Argentina (2015), Austria (2014),
Benin (2014), Botswana (2014), Brazil (2015), Burkina Faso (2014),
Chile (2014), Congo (2014), Costa Rica (2014), Côte d’Ivoire (2015), Czech Republic (2014),
Estonia (2015), Ethiopia (2015),
Gabon (2015), Germany (2015),
India (2014), Indonesia (2014), Ireland (2015), Italy (2014),
Japan (2015),
Kazakhstan (2015), Kenya (2015), Kuwait (2014),
Montenegro (2015),
Pakistan (2015), Peru (2014), Philippines (2014),
Republic of Korea (2015), Romania (2014),
Sierra Leone (2015),
United Arab Emirates (2015), United States (2015),
and Venezuela (2015).

መንግስት በሳውዲ አረብያ ጉዳይ ''የግብር ይውጣ'' በሚመስል መልክ ለመያዙ ማሳያ የሆኑት አምስት ነጥቦች፣ምን ይደረግ?....በአዲስ አበባ ያለው የሳውዲ አምባሳደር መልስ እስካሁን አልሰጡም




በሳውዲ አረቢያ ያሉ ወገኖቻችን ላይ የሳውዲ ፖሊስ እና ''ሸባብ'' የተሰኙ ወጣቶች እያደረሱ ያሉት ግፍ ካለፈው አርብ ወዲህም መሻሻል አላሳየም። ኢቲቪ በሰኞ 02/03/2006 ዓም ምሽት  የዜና እወጃው ላይ ስለ ሳውዲ ጉዳይ ምንም አለማለቱ እውነት ይህንን ያህል ታፍነናል እንዴ? የሚያስብል ነው።ዓለም የሚያወራውን ጉዳይ ጉዳይ የሀገራችን ብሔራዊ ቴሌቭዥን አንድ ምሽት ዘግቶት አለፈ ማለት ምን ትርጉም ይሰጥ ይሆን?

በአንፃሩ መንግስት እየወሰደ ያለው እርምጃ እጅግ አስገራሚ፣አሳዛኝ እና ''የግብር ይውጣ'' ያህል በሚባል ደረጃ  ነው።።ለእዚህ ማስረጃ የሚሆኑትን የሚከተሉትን ነጥቦች ብቻ ማንሳቱ ይበቃል።


1/ አምባሳደሩ የፅሁፍም ሆነ የቃል መልስ እስካሁን አልሰጡም 

 መንግስት እስካሁን ድረስ በአዲስ አበባ ያለውን የሳውዲ ምክትል አምባሳደር በፅሁፍ እና በቃል ማብራርያ እንዲሰጡን ጠይቀናል ይበል እንጂ አምባሳደሩም ሆኑ ኢምባሲው እስከ ሰኞ ማታ ድረስ ምላሽ አለመስጠታቸውን ለማወቅ ተችሏል።ስለ ጉዳዩ ሸገር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ጠይቆ እንደተረዳው እስከ ሰኞ ምሽት ድረስ መልስ አልሰጡም።ይህ በዲፕሎማሲ አነጋገር ንቀት ብቻ ሳይሆን ተጨማሪ እርምጃ መንግስት መውሰድ እንደሚገባው የፖለቲካ ሳይንሱ እራሱ ያዘዋል።እርምጃው አምባሳደሩን ከሀገር እስከማስወጣት ድረስ ያደርሳል።በእዚህ ምክንያት ሳውድ ያሉ ወገኖችን ጉዳይ ወደ አለማቀፍ መድረክ ማምጣት ይቻላል።ይህ ማለት ሌሎች አካላትም ሆኑ አለማቀፍ ድርጅቶች በጉዳዩ እንዲገቡ ይጋብዛል።መንግስት ግን ይህንን ያህሉን ውርደት ተሸክሞ  ሀገርንም አሸክሞ ተቀምጧል።

 2/ መንግስት መግለጫውን በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ደረጃ ዝቅ አድርጎታል።

 እስከ ሰኞ ምሽት ድረስ ለውጭም ሆነ ለሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ስለጉዳዩ  መግለጫ እየተሰጠ ያለው በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ብቻ ነው።የእዚህ አይነቱ በሺህ የሚቆጠሩ ዜጎች በምድር ላይ ምናልባት በናዚ ዘመን የተፈፀመ ግፍ ጋር የተስተካከለ ግፍ ተሰርቶ፣ጉዳዩ በቀጥታ ከብሄራዊ ሉዓላዊነት አደጋ ጋር የተያያዘ ትልቅ ጉዳይ መሆኑ እየታወቀ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩም ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አንዳች መግለጫ አልሰጡም። ይህ ህዝብን መናቅ ነው። አቶ ሃይለማርያም እና ዶ/ር ቴዎድሮስ ከማን ይበልጣሉ? አሜሪካ ሕፃናት መዋያ ላይ ለተፈፀሙ 3 እና 4 ሰው ለሞተበት አደጋ ፕሬዝዳንቷ ለመላው ሕዝብ መግለጫ ይሰጣሉ።እኛ በሺህ የሚቆጠሩ ዜጎቻችን የዜግነት መብታቸው ተገፎ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ማብራርያ መሰል ነገር ይወረወርልናል።

3/ ሌሎች የኢትዮጵያ ወዳጆች  እና አካላት ጉዳዩን እንዲመለከቱ አላደረግም 

መንግስት ጉዳዩን ጉዳዬ ብሎ ይዞት ቢሆን ኖሮ ቢያንስ የሳውዲ አረብያን መንግስትን ከፍተኛ ባለሥልጣጥናት ማነጋገር በጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ያደርግ ነበር።ይህ ባይሳካ በአፍሪካ ህብረት፣በአረብ ሊግ በኩል ባሉት ወዳጆቹ ለምሳሌ በኩዌት በኩል ሌሎች አካላት ጣልቃ እንዲገቡ የማድረግ ሥራ አልተርሰራም።ይህ ደግሞ የሕይወት አድን ጉዳይ ስለሆነ ከማጣደፍ ጋር ቢሆንም ለሀገራቱ እንግዳ ሥራ ሊሆን አይችልም ነበር። የአፍሪካ ህብረት ለዓለም አቀፉ ፍርድቤትን ለመወንጀል ያንን ያክል የመሪዎች ስብሰባ የጠራ መንግስት በዜጎቹ ጉዳይ ምነው ዳተኛ ሆነ?

በተለይ ኩዌት የኢትዮጵያ የእረጅም ጊዜ ወዳጅ  ነች።በባህረ ሰላጤው ውግያ (በኢራቅ ወረራ ጊዜ) ኢትዮጵያ ከጎኗ በመቆሟ የተገነባ ጥሩ ግንኙነት መኖሩ ይታወቃል።የቦሌ አየርመንገድን በአዲስ መልክ የመስራት ሥራ የገንዘብ ድጋፍ ያደረገችም ኩዌት መሆኗ ይታወቃል።ይህንን ግንኙነት ዛሬ ኢህአዲግ ጠብቆታል ወይስ አበላሽቶታል? እራሱን የቻለ ጥያቄ ነው።የሆነው ሆኖ መንግስት በሳውዲ አረብያ መንግስት ላይ ዜጎች ከእነ ክብራቸው ወደሀገራቸው እንዲገቡ ተፅኖ ለመፍጠር አልሞከረም።

4/ አረብኛ የማይችሉ ሰራተኞች በአረባዊቷ ሀገር መመደብ 

 ሳውዲ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ በራሱ ብዙ ችግር ያለበት መሆኑ እየተወሳ ነው።ከችግሮቹ አንዱ በፓርቲ አባልነት የተመደቡት ሰራተኞች አረብኛ መናገር ቀርቶ አማርኛ በአግባቡ የማይናገሩ መሆናቸውን በሳውዲ የሚኖሩ ዜጎች እየተናገሩ ነው።የዲፕሎማሲ  የመጀመርያው መሳርያ የተመደበበትን ሀገር  ቋንቋ የሚናገር የሰው ኃይል መመደብ ነው። ሳውድ አረብያ ያለው ኢምባሲ ግን ይህንን ያሟላ አይደለም።ስለዚህ ከሀገሪቱ መንግሥታት የተለያዩ ቢሮዎች ጋር ተነጋግረው የሚያሳምኑ ሰራተኞች አለመኖር በራሱ የመንግስትን ፓርቲ-ተኮር የስራ ምደባ የሚያመጣውን ክስረት የሚያመላክት ነው።ይህ ደግሞ ዛሬ በይድረስ ይድረስ የሚመደብ ሳይሆን በሀገሩ ቆይተው ወዳጅነት ሊያጠነክር የሚችል የሰው ኃይል ማዘጋጀት ያስፈልግ ነበር።

5/  የኢጀንሲ ድርጅት ባለቤቶች የኢምባሲ ሰራተኞች? 

የመጨረሻው አሁንም ውጭ ጉዳይም ሆነ መንግስት ከእዚህ በፊት'' የህገወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመግታት እየሰራሁ ነው'' ሲል የነበረውን ሁሉ የሚያፈርስ ጉዳይ ሰሞኑን ለማወቅ ተችሏል።ይሄውም በሳውዲ አረብያ  የኢትዮጵያ ኢምባሲ እና የኮምኒት  አንዳንድ ሰራተኞች ከኢትዮጵያ ወደ መካከለኛው ምስራቅ ወጣቶችን በቅጥር መልክ የሚደልሉ ኤጀንሲ ድርጅቶች ባለቤት መሆናቸው እና ብሮአቸውም በሳውዲ አረብያ መኖሩ መገለጡ ጉዳዩን አጀብ የሚያሰኝ ነው።በኢትዮጵያ የሲቪል ሰርቪስ ሕግ አንድ ሰው ከሚሰራበት መስርያቤትን ሥራ የሚቃረን ሥራ መስራት በራሱ እንደሚያስቀጣ ይገልፃል።በኢምባሲ ደረጃ የተመደበ ሰራተኛ በእንደዚህ አይነት እርካሽ ሥራ ተሰማርቷል መባሉ በራሱ ትልቅ የሀገር ውድቀት ነው።

ምን ይደረግ?

ባጠቃላይ ይህንን ሁሉ ጉድ የያዘው የመንግስት ድርጅት ምን እንዲሰራ ይጠበቃል? የችግራችን ስሩ እረጅም ነው።መንግስት እንደትልቅ ሥራ አድርጎ ሊያሳየን የሚሞክረው እስካሁን መልስ ያልሰጡት ምክትል አምባሳደርን አናገርኩ እና ልዑክ ልክያለሁ ብቻ ነው።ከችግሩ ግዝፈት አንፃር ይህ ፌዝ እና ቀልድ ብሎም ''የግብር ይውጣ''  ሥራ ነው።

እዚህ ላይ ኢትዮጵያውያን በእዚህ ደረጃ መከራ ሲደርስባቸው ለምን የውጭ አካላት አይናገሩም? የሚሉ አሉ።ሆኖም ግን የውጭ ኃይሎች በራሳቸው የተደመሙበት ጉዳይ የመንግስት የዲፕሎማሲ አካሂያድ ነው።ከመንግስት ሳይጠየቁ ምንም ለማለት አይችሉም።ቢያንስ ለአንዲት ቃል መነሻ ቃል ያስፈልጋል። ያንን መነሻ ቃል ሊሰጥ የሚችለው መንግስት ነበር። ግን አልሆነም።

አሁን በውጭ የሚኖሩም  ሆኑ በሀገር ቤት ያሉ ኢትዮጵያን ብቻ ናቸው መፍትሄውን ማምጣት ያለባቸው።የሳውዲው ጉዳይ አስተማሪ ሆኖ በተገቢ መልኩ ካልታረመ ሌሎች አካባቢ ያሉ ወገኖቻችን ላይ ተመሳሳይ ችግር ወደፊት የመፈጠር እድሉን ያሰፋዋል።በመሆኑም ኢትዮጵያውያን ከሀገር ቤት እስከ ውጭ ሃገራት ያለን ሁሉ  አስተማሪ የሆነ ሥራ መስራት ይገባል።ለእራሳችን መቆም ያለብን እራሳችን ብቻ ነን።በውጭ ያለው ሕብረተሰብ ትልቅ የ አድቭኬት ሥራ መስራት ይጠበቅበታል።

ለእዚህም እንዲረዳ በሳውድ ያሉ ወገኖች ጋር ግንኙነት ያላችሁ ወገኖች ከአሳዛኝ ፎቶ ባለፈ ወጥ የሆነ በተለይ በህፃናት እና በሴቶች ላይ የደረሰውን ግፍ ባለታርኮቹ ሲናገሩት የሚያሳዩ ደረጃቸውን የጠበቁ ፊልሞች በእየሃገራቱ ቋንቋ እየተርጎሙ ለየሀገራቱ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች መስጠት እና በጋዜጦች ላይ እንዲወጣ አርቲክሎችን መፃፍ ያስፈልጋል።በተለይ በህፃናት እና በሴቶች ላይ የተሰሩ ፊልሞችን ደረጃውን በጠበቀ መልክ ማዘጋጀት የምዕራቡን ዓለም በእጅጉ የሚስብ እና ጉዳዩን ለዓለም ሕዝብ የሚያጋልጥ ከመሆኑም በላይ ጉዱን እያወቀ ጥቅም ላወረው ዓለም ምክንያት ይሆነዋል።የሲ ኤን ኤን ''የነፃነት ዘመቻ'' የተሰኘውን ፕሮጀክት ፕሮግራሞች ይዘት መረዳቱ ብቻ ከላይ ለተቀስኩት ሕፃናት እና ሴቶች ላይ ያተኮሩ ፊልሞችን ውጤታማነት አመላካች ነው።

ከእዚህ ሁሉ ባለፈ ደግሞ በውጭ የሚገኙ የእስልምና ማኅበረሰብ መሪዎች በኢትዮጵያዊነት የሳውዲ አረብያን መንግስት እና  አረብ ሊግ ዙርያ የሚሰሩ ስራዎችን እንዲሰሩ ማድረግ በተጨማሪም  በአረብ ሃገራት እና በእራሷ በሳውድ አረብያ ያሉ ጋዜጦች ላይ ጉዳዩን ማሳወቅ እና ትኩረት መሳብ በአጭር ጊዜ የሚሰሩ ስራዎች መሆን ይገባቸዋል። ከእዚህ ሁሉ በፊት ግን የሳውዲ ኢምባሲን ከአዲስ አበባ እስከ ውጭ ሀገር ባሉት ሁሉ ላይ ተቃውሞ ማሰማት ይገባል።ለእዚህም የፖለቲካ ፓርቲዎችም ሆኑ የኢትዮጵያ ኮሚኒቲዎች ሊያንቀሳቅሱት የሚገባ አፋጣኝ ሥራ ነው።

ጉዳያችን
ጥቅምት/2006 ዓም

Sunday, November 10, 2013

''እኛ መንግስት የለንም! የሌላው ሀገር መንግስት ሕዝቡን አስከብሯል አንድ የሌላ ሀገር ሰው ጨርቁ አልተነካም 'አበሽ ነህ? ኢትዮጵያዊ ነህ ?' እየተባለ ነው የሚቀጠቀጠው''


እሁድ ህዳር 1/2006 ዓም በአረብኛ የሚታተም የሳውዲ ጋዜጣ ኢትዮጵያውያን እጃቸው ታስረው የሚያሳየው ፎቶ 

የዛሬ አርባ ዓመት በ 1965 ዓም ኢትዮጵያ በመላው ዓለም የታወቁ እና የተመዘገቡ ስደተኞች ቁጥር 2 ብቻ ነበር።ዛሬ ከሁለት ነጥብ አምስት ሚልዮን በላይ ደርሷል። የተከበረች የታፈረች ሀገር ዛሬ በእዚህ ደረጃ መዋረዷ ያሳዝናል።ቆም ብሎ ማሰብ አይገባም ወይ? ኢትዮጵያዊነት ከተዋረደበት ደረጃ መነሳት የለበትም ወይ? ክምንጊዜውም በላይ ህብረት እና አንድነታችንን ማጠንከር የሚገባን ወሳኝ ጊዜ  ላይ አይደለንም ወይ?

ሳውዲ አረብያ ያሉ ወገኖቻችን በቀጥታ በስልክ ዛሬ እሁድ ህዳር 1/2006 ዓም ከተናገሩት -


''እኛ መንግስት የለንም! የሌላው ሀገር መንግስት ሕዝቡን አስከብሯል አንድ የሌላ ሀገር  ሰው ጨርቁ አልተነካም 'አበሽ ነህ? ኢትዮጵያዊ ነህ ?' እየተባለ ነው የሚቀጠቀጠው''

''ወገን ይስማን!! ወገን ይድረስልን!!! ''

''እዚህ ሀገር ብዙ ሺዎች  የሚሆኑ የሌላ ሀገር ዜጎች እቃቸውን ይዘው አደባባይ ወጥተዋል ግን አንድ ሰው አልተነካም።እነሱ ኢምባሲ አላቸው።እኛ ማንም ዘወር ብሎ የሚያየን የለም።''

''ወንዶቹን ደብድበው ሴቶቹን ለ 7 እና ለ 8 እየሆኑ 'ሽባብ' የተባሉት የአረብ ወጣቶች ይደፍሯቸዋል''

'' ፖሊሶቹ ሆን ብለው ከዘራፊ እና ከሚደፍሩ ወጣቶች ጋር ይመጣሉ ሊያዘርፉን እና ሊደፍሩን''

''ንብረት የለፋንበትን በሙሉ ነው የነጠቁን መንገድ ላይ ወርቅ ያደረገች ሴት አልቀረችም በወጣቶቹ ተዘረፉ''

''ወንዱን እየጫኑ እየወሰዱ ሴቶቹን 'ሸባብ' ለተባሉ ወጣቶች እንዲደፈሩ ትተዋቸዋል።''

''ኢትዮጵያ ያለውን የሳዑድ አረቢያ ኢምባሲ ለምንድነው ሀገርቤት ያለው ሕዝብ  ወጥቶ የማይቃወመው ?ከየቤቱ አንድ ወይ ሁለት ሰው ወደ አረብ ሀገር ያልላከ ማን ነው? ለምንድነው ህዝቡ ዝም የሚለው?''

''የኢትዮጵያ ሕዝብ እባካችሁ ስሙን አንድ ነገር አድርጉልን አሁን በራችንን እስኪሰብሩ እና እስኪመጡ እየጠበቅን ነው።''

''ነገ እኔን አህትህን ላታገኘኝ ትችላለህ ወይ ለ አራት እና ለአምስት ተጫውተውብኝ አይምሮዬን ላጣ እችላለሁ።''

Saturday, November 9, 2013

በሳውዳረቢያ ያሉ ወገኖች ሁኔታ እጅጉን ተባብሷል....ሶስት ደረጃ ያላቸው መፍትሄዎች ይታዩኛል። የአዲስ አበባ ሕዝብ እና በውጭ የምንኖር ዜጎች በቀጣዮቹ ጥቂት ሰዓታት መስራት ያለብን ።


በማህበራዊ መገናኛ ከተለጠፈ የድረሱልን ጥሪ ቅዳሜ ጥቅምት 30/2006 ዓም 

በሳውዲ አረብያ ያሉ ወገኖቻችን ሁኔታ ከሶስት ቀናት በፊት ከነበረበት ሁኔታ እጅግ ወደ ባሰ ሁኔታ እየተሸጋገረ ይመስላል።ባለፉት 48 ሰዓታት ውስጥ የተከሰተው አዲስ ነገር ኢትዮጵያውያን መከራ ሲበዛባቸው እራሳቸውን ወደመከላከሉ ሲ ያዘነብሉ የሳውዲ ወጣቶችም አበሻውን እየመረጡ ማጥቃት ጀምረዋል።ሁኔታው በእዚሁ ከቀጠለ ከእዚህ በኃላ ተይዘው እስር ቤት የሚገቡት ኢትዮጵያውያን በእስር ቤት ከገቡ በኃላ ምንም አይነት የሚድያ ሽፋን በማታገኘው ሳውዲ አረብያ ታላቅ መከራ ይወድቅባቸዋል።

መንግስት ምክትል አምባሳደሩን አነጋገርኩ፣ ዜጎችን የማስወጣት ሥራ ልጀምር ነው ወዘተ የሚሉ የማረጋግያ ንግግሮችን ቢያሰማም ሁኔታውን ግን ከእዚህ በላይ የሚሄድበት አይመስልም።እንደ እውነቱ ከሆነ የእዚህ አይነቶቹ ሁኔታዎች በመንግስት ቀደም ብለው መታየት የነበረባቸው ሁኔታዎች ነበሩ።ለምሳሌ የዜጎች በሳውዲ አረብያ የሚሄዱበት ሁኔታ እና ነገሩ ከቁጥጥር ውጭ ከመውጣቱ በፊት የዜጎችን ችግር ለመፍታት በተጠና መንገድ አለመታሰቡ ዛሬ ለገጠመን ችግር የእራሱ የሆነ አሉታዊ ተፅኖ አምጥቷል።

አሁን ያንን ማውራቱ ሞት በራቸው ላይ ለቆመባቸው ወገኖቻችን አንዳች ነገር አይፈይድም።ከሳውዲ አረብያ ውጭ ያለን ኢትዮጵያውያን (ማለትም በሀገር ቤት እና ባህር ማዶ ያለነው) ማድረግ ያለብን አንድ ነገር ያለ ይመስለኛል።በመጀመርያ ደረጃ መንግስት ኢትዮጵያውያኑን አወጣለሁ ያለውን ወደተግባር ለመቀየር በቅርብ ይችላል ብሎ ማለት አይቻልም።ምክንያቱም ፓስፖርት የሌላቸውን በሺህ የሚቆጠሩትን ይለፍ መስጠት(ዜግነታቸውን ማረጋገጥ)፣ነፃ የትራንስፖርት ወጪ መመደብ እና ሀገር ቤት ወደየቀያቸው እስኪመለሱ  ቢያንስ ለጥቂት ቀናት የሚሆናቸው ገንዘብ ያስፈልጋል።አሁን ብዙዎች ንብረታቸውን እየተነጠቁ ናቸው።እነኝህን ስራዎች ባጭር ጊዜ የመስራት አቅሙም ሆነ የሎጀስቲኩ ዝግጅት ከመንግስት ሊገኝ ይችላል የሚል ግምት የለኝም።መንግስትን በመጠየቅ ሕይወት ስቀጠፍ ማየት በራሱ ሌላ እራስ ምታት ነው።


ስለዚህ ምን እናድርግ? 

እኔ አሁን የሚታዩኝ ሶስት ደረጃ ያላቸው ድርጊቶች ናቸው።


1/  ድርጊት አንድ 


አዲስ አበባ የሚገኘውን የሳውዲ ኤምባሲን  በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ወጥተው  በተቃውሞ ድምፃቸውን ማሰማት አለባቸው።የአዲስ አበባው ሰልፍ በውጭ ከሚኖሩት በበለጠ ትልቅ ድምፅ አለው።ሰልፉ የዓለም አቀፍ የዜና ዘጋቢዎች ሰሞኑን አዲስ አበባ ለተደረጉት ስብሰባዎች የመገኘታቸውን አጋጣሚ መጠቀም ያስፈልጋል።ሳውዲ አረብያም ከኢትዮጵያ ጋር የሚኖራትን ጥቅም እንደሚጎዳው ትረዳለች።እራሳችንን አሳንሰን አንመልከተው ከእርሻ ጀምሮ ሌሎች የንግድ ዘርፎች ላይ ሳውዳረብያ ኢትዮጵያ ውስጥ ጣፈጠም መረረም ጥቅም አላት።በሕዝብ ዘንድ የሚነሱ ተፅኖዎች በምንም መልኩ የሚናቁ አይደሉም።

2/ ድርጊት ሁለት 

 በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በማህበራዊ ድህረ-ገፆቻቸው ጉዳዩን የዓለም ሕዝብ እንዲመለከት በመግለፅ፣በየሃገራቱ የሚገኙ የሳውዲ  አረብያ ኢምባሲዎችን በስልክ፣በፋክስ፣እና በኢሜል ጥያቄውን ለሀገራቸው መንግስት እንዲያቀርቡ በማሳሰብ እና የአዲስ አበባው ሰልፍ ከተደረገ በኃላ እንደችግሩ መቀጠል በተቃውሞ ሰልፍ ጭምር ጉዳዩን ለየምንኖርበት ሃገራት መንግሥታት ማሳወቅ።

3/ድርጊት ሶስት 


 በሶስተኛ ደረጃ ሁኔታው የመረጋጋት መልክ ሲያሳይ ወደሀገራቸው የሚሄዱትን እና በድርጊቱ እጅግ የተጎዱቱን ቅድምያ ሰጥቶ በውጭ ያለው ወገን መርዳት የሚችልበትን ሁኔታ ማቀናበር የሚሉት ይሆናሉ።

አሁን ግን በቅድምያ አዲስ አበባ ያለው ሕዝብ በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ ይህንን የውርደት ድርጊት ወደ ኢምባሲው በመሄድ መቃወም የሚገባው ይመስለኛል።ይህ በመንግስት ደረጃ ምንም ያልተባለለትን ዲፕሎማሲ በፍጥነት ወደ ሕዝብ ዲፕሎማሲ  ያሳድገዋል።በተጨማሪም የሳውዲ መንግስት ነገሩን በአንክሮ እንዲያይ ያስገድደዋል እና አፋጣኝ መልስ ከህዝባችን ይጠበቃል።



።።።።።።።።።።።።።//////////።።።።።።።።።።።።።።።።።////////።።።።።።።።።።።።።።።።።።

በኢትዮጵያ ያለፉት አርባ አመታት የፖለቲካ ሂደት ስድስቱ የለውጥ መዘውር ነጥቦች(turning points)-ሰባተኛው የለውጥ መዘውር ነጥብ እየቀረበ ይሆን? (ጉዳያችን አጭር ጥንቅር)


ኢትዮጵያ የዘውድ ስርዓት ከወረደ በኃላ ባልተረጋጋ የለውጥ ማዕበል ውስጥ መናጥ ከጀመረች 40 ዓመታት እየደፈነ ነው።የየካቲት 1966 ዓም አብዮት ዘንድሮ 40 ዓመት ይሞላዋል።ከ 1966 ዓም በፊት በነበሩት ስልሳ አመታት ውስጥ  ሀገራችን ከሁለት መቶ አመታት በላይ በዘመነ መሳፍንት የእርስ በርስ ግጭት ከቀረው ዓለም ጋር የነበራት ግንኙነት በብዙ መልኩ የተለያየ እና ጠንካራ የማይባል ነበር።ከ20ኛው ክፍለ ዘመን መጀመርያ እስከ አጋምሹ ማለትም 1966 ዓም በነበሩት ዓመታት ውስጥ ሀገራችን ፍፁም ከሆነው የፊውዳል ስርዓት ወደ ዘመናዊነት ለመግባት ብዙ ነገሮች በየዘርፉ የጀመረችባቸው አመታት ነበሩ።ዘመናዊ መንግስት ስርዓት- እንደ ፓርላማ፣ዩንቨርስቲዎች፣የአየር መንገድ አገልግሎት፣የመብራት ኃይል ማስፋፋት፣በዓለም አቀፍ ግንኙነትም ሆነ በአህጉራዊ እና አካባቢያዊ ፖለቲካ ውስጥ ተፅኖ ፈጣሪነት እና የመሳሰሉት ባጭሩ ሊገለፁ የሚችሉ የዘመናቱ ስራዎች ነበሩ።

ከ1966 ዓም ወዲህ ባሉት አርባ አመታት ውስጥ ኢትዮጵያ የተረጋጋ የመንግስት ስርዓት እና ህዝብን ያማከለ አስተዳደር ቢኖራት ኖሮ ዛሬ ካለአንዳች ማጋነን ደቡብ ኮርያ ከደረሰችበት የስልጣኔ እና የእድገት ደረጃ የመድረስ ዕድል ነበራት።ይህ ግን አልሆነም።

በእነኚህ አመታት ውስጥ በተገቢው ደረጃ እንዳናድግ ያደረጉን ብዙ ምክንያቶች አሉ።ከእነኝህ ውስጥ በቀን በሚልዮን የሚቆጠር ገንዘብ የበላ ጦርነት በሰሜናዊ የሀገራችን ክፍል ለአስራ ሰባት አመታት መካሄዱ፣ የነበሩት በእውቀት ክህሎታቸው እና በልምዳቸው ለሀገራቸው አስተዋፅኦ ያደርጉ የነበሩ ምሁራን የመስራት መብታቸው መታፈኑ፣የኢትዮጵያ አለም አቀፍ ግንኙነት ብልህነት ያልተሞላበት የነበረ መሆኑ፣ካለፉት 22 አመታት ወዲህ ደግሞ ብሄርን መሰረት ያደረገ የሀገሪቱ የአስተዳደር  መዋቅር ወደባሰ አደገኛ የህዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ማምራቱ፣ብሄርን መሰረት ያደረገ አድሏዊ ስርዓት ምጣኔ ሃብቱን በተወሰኑ እና ጥቂት ሰዎች እጅ እንዲገባ ማድረጉ፣የፈጠራ ስሜት እጅጉን እንዲጎዳ መደረጉ፣ሀገሪቱ ያለወደብ ቀርታ ለባሰ የባዕዳን ጥቃት ተጋላጭ መሆኗ ወዘተ የሚሉትን መጥቀስ ይቻላል።

ከላይ በተጠቀሰው 20ኛው ክ/ዘመን (1900 -2000 ዓም) ውስጥ ኢትዮጵያ ስድስት የለውጥ መዘውሮች (turning points) ውስጥ አልፋለች።እነኝህ የለውጥ መዘውሮች (turning points) በሀገራችን የፖለቲካ መረክ ላይ ይከሰቱ እንጂ አብዛኞቹ ብሩህ ተስፋ ይዘው የመጡ የሚመስሉ ግን የከሸፉ ናቸው።የመክሸፋቸውን ምክንያት ለታሪክ ተመራማሪዎች ትቼ ክስተቶቹ ምንነት ላይ ብቻ ላተኩር።

1/ የለውጥ መዘውር ነጥብ (turning point) አንድ  - 

ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ 

ቤ 20ኛው ክ/ዘመን መጀመርያ ላይ የመጀመርያው የለውጥ መዘውር የነበረው የንግሥት ዘውዲቱ ስልጣን ወደ አልጋወራሽ ተፈሪ በኃላም በ 1923 ዓም የንግስና ማዕረግ ያገኙት የቀዳማዊ አፄ ሃይለስላሴ ወደ ስልጣን መምጣት ነው።በወቅቱ በጥቂት የተማሩ እና ''ተራማጅ'' ተብለው ይጠሩ በነበሩ ወጣቶች ይደገፉ ነበር። ቀዳማዊ አፄ ሃይለስላሴ ገና በአልጋ ወራሽነት ዘመናቸው ሳሉ አውሮፓን መጎብኘታቸው እና የአውሮፓን ስልጣኔ መመልከታቸው በኃላም የጣልያን ኢትዮጵያን መውረር እና በትምህርት እና በስልጣኔ ምን ያህል ወደኃላ እንደቀረን ግልፅ መሆኑ ቁጭት በንጉሱም ሆነ በወቅቱ በነበሩት ወጣቶች ዘንድ በሀገሪቱ ልማት ላይ ለውጥ ለማምጣት ስሜትን ኮርኩሯል።በእዚህም መሰረት ሀገራችን ከምንም ከሚባል ደረጃ በአፍሪካ እና በዓለም ተሰሚ የመሆን ደረጃ ደርሳ ነበር።

2/  የለውጥ መዘውር ነጥብ (turning point) ሁለት 

ብ/ጄ/መንግስቱ  ንዋይ (በንጉሡ ላይ መፈንቅለ መንግስት ከመሩት)

ሁለተኛው የለውጥ መዘውር መነሳሳት የተከሰተው በ 1953 ዓም የተነሳው በብ/ጄ/መንግስቱ ንዋይ  እና ገርማሜ የተመራው በንጉሡ ላይ የተሞከረው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ነው።ከ 1935 እስከ 1953 ዓም ድረስ የዓለም የፖለቲካ ሁኔታ ተለወጠ።አዲሱ ትውልድ አዳዲስ አስተሳሰብ ይዞ መጣ።ንጉሡ ምንም ለሀገሪቱ የመስራት ፍላጎታቸው እና ውጤታቸውን ቢያደንቅም መጪውን ግን በእዚህ አይነት አሰራር መቀጠል እንደማይቻል ያሰቡ መኮንኖች የመፈንቅል ሙከራ አደረጉ።ይህ መፈንቅል ተሳክቶ ቢሆን የሀገራችን የፖለቲካ ገፅታ ዛሬ ምን ይሆን ነበር? በርካታ መልሶች ይኖሩታል።

3/ ሶስተኛ የለውጥ መዘውር   ነጥብ (turning point)

1966 ዓም ሕዝባዊ አብዮት 

ሶስተኛው የለውጥ መዘውር ነጥብ አርባኛ አመቱን የሚደፍነው የየካቲቱ 1966 ዓም አብዮት ነው።ይህ አብዮት አሁን እስካለንበት ሁኔታ ድረስ ተፅኖ ፈጣሪ የሆነ እና በአሁኑ ጊዜ ያሉት ብዙዎቹ የፖለቲካ ድርጅቶች በእዚህ ወቅት ከነበረው የፖለቲካ አሰላለፍ ባንድም በሌላም ያለፉ ናቸው።

4/  የለውጥ መዘውር (turning point) አራት 

ሜ /ጄነራል ፋንታ በላይ እና ሜ/ጄነራል አምሃ ደስታ በኮ/ል መንግስቱ ላይ መፈንቅለ መንግስቱን ከመሩት መኮንኖች 

አራተኛው የለውጥ መዘውር ነጥብ በ 1981 ዓም በኮ/ል መንግስቱ ሃይለማርያም ላይ የተሞከረ የመፈንቅለ መንግስት ነው። ይህ መፈንቅለ መንግስት ቢሳካ ኖሮ ለሀገራችን ምን አዲስ ነገር ይዞ ይመጣ ነበር? አሁንም ለታሪክ ተመራማሪዎች እተወዋለሁ።የክስተቱ ተፅኖ ግን ብዙም ሳይቆይ በተለይ ከፍተኛ ልምድ የነበራቸው የሀገሪቱ የጦር መኮንኖች በኮ/ል መንግስቱ መገደላቸው የሰራዊቱን አቅም አዳክሞ ለሽምቅ ተዋጊዎች 'ሰርግና ምላሽ' ሁኔታ መፍጠሩን ብዙዎች ይስማማሉ።

5/ አምስተኛው  የለውጥ መዘውር ነጥብ 

አቶ መለስ 1983 ዓም 

አምስተኛው የለውጥ መዘውር ከ 1981 ዓም ብዙም ሳይቆይ በ 1983 ዓም ግንቦት ወር ላይ የኢህአዲግ ሰራዊት አዲስ አበባ መግባት ነው።ይህንን ተከትሎ ሀገራችን በዘመኗ አይታ የማታውቀው የብሔር ፖለቲካ እና መከለል ውስጥ የገባችበት፣ሀገሪቱ ወደብ አልባ የሆነችበት፣በክልሎች ደረጃ የድንበር ቁርሾ የተነሳበት በአስተዳደር ዘይቤ በዘመናዊው ዓለም ውስጥ የምትኖር የዘመነ መሳፍንት ውስጥ ያለች ሀገር የመሰልችበት ክስተት ተከሰተ።ይህ የለውጥ መዘውር እጅግ አደገኛ ያደረገው የህዝቡ ኩራት እና ማንነት ከሆነው ከኢትዮጵያዊነት የተጣላ ስርዓት መሆኑ ነው። ይህ ስርዓት የምጣኔ ሃብቱን፣የጦር ኃይሉን እና ፖለቲካውን እራሱን በጥቂት ሰዎች እና አካባቢ ሰዎች ስር መጣሉ የሀገራችንን መፃኢ ዕድል እጅግ አደገኛ አድርጎታል።

6/ ስድስተኛ የለውጥ መዘውር ነጥብ 

ምርጫ 1997 ዓም 

ስድስተኛው የለውጥ መዘውር ነጥብ  በ 1997 ዓም ኢትዮጵያ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ሕዝቧን ያነቃነቀ ነፃ የምርጫ ስርዓት ያየችበት እና  እንደ 1967 ዓም መፈክር ''ያለምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም'' ልንዘመር ነው ተብሎ የተናፈቀበት ወቅት ነበር።ሆኖም ግን ክስተቱ በመቶ የሚቆጠሩ ወጣቶችን ሕይወት በኢህአዲግ ሰራዊት አማካይነት አስቀጥፎ እና ብዙዎችን ለእስር እና ለስደት ዳርጎ እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ ሀገራችንን ላለፉት አርባ አመታት በነበረችበት የአምባገነንነት ስርዓት ውስጥ እንድትቀጥል ተፈረደባት።

7/ ሰባተኛው የለውጥ መዘውር ነጥብ?

ዛሬም በበሬ እያረስን ነው።ሰባተኛው የለውጥ መዘውር ቢያንስ ይህንን መለወጥ የለበትም?

ኢትዮጵያ የመጀምርያውን ሕዝባዊ አብዮት በታሪክ ካደረገች አብዮቱንም በወታደራዊ ደርግ ከተነጠቀች በኃላ፣ሰሜናዊው ህዝቧ እና መሬቷ እንዲነጠል ተደርጎ፣ወደብ አልባ ሆና ለወደብ አገልግሎት በጎረቤት ጂቡቲ ላይ ጥገኛ እንድትሆን ተደርጋ፣ሀገሪቱ በክልል ተከልላ እርስ በርስ የማይተማመን ሕዝብ ለመፍጠር ብዙ ሴራ ተስርቶባት፣በ 1965 ዓም በዓለም ላይ  ሁለት ስደተኞች ብቻ የነበሯት ሀገር ዛሬ ከሁለት ነጥብ አምስት ሚልዮን በላይ ስደተኛ በመላው ዓለም በትና እና ብዙ አስር ሺህ ሕፃናቷ በጉድፈቻነት ሸጣ ባጠቃላይ በብዙ ችግሮች ውስጥ ሆና ነው ሰባተኛውን የለውጥ መዘውር እየቀረበ መሆኑ ይሰማኛል የምለው።ሰባተኛው የለውጥ መዘውር በማን እንዴት መቼ እንደሚመጣ በእርግጠኝነት  መናገር አሁን አይቻል ይሆናል። የህዝብ ፍላጎትን እና በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ግራ መጋባትን ተመልክቶ መረዳት ግን ብዙ አዋቂነትን አይጠይቅም።

ለሰባተኛው የለውጥ መዘውር  ለማምጣት የተነሱ በሰላማዊውም ሆነ በትጥቅ ትግል ውስጥ የገቡ ኃይሎች ብቅ ብቅ እያሉ ነው።እነኝህ ኃይሎች ባብዛኛው ከስድስተኛው የለውጥ መዘውር ሙከራ ማለትም ከ 1997 ዓም ወዲህ የተነሱትንም ማካተቱ ይታወቃል።በሃገርቤት በሰላማዊ ትግል ያለችውን ቀዳዳ እየተጠቀሙ ያሉትን ጨምሮ በትጥቅ ትግል ላይ ያሉት እንደ ''ግንቦት 7'' አርበኞች ግንባር ወዘተ ያሉት ስርዓቱን በኃይል ለመጣል በሥራ ከተጠመዱት ውስጥ ናቸው።

ከአቶ መለስ ዜናዊ እረፍት ወዲህ በብዙ የውስጥ ቅራኔዎች መዋከቡ የሚነገረው ኢህአዲግ-ወያኔ እራሱን ለመሰረታዊ ለውጥ አለማዘጋጀቱ እራሱን የቻለ ችግር ሆኖ የቀጠለ ክስተት ቢሆንም ለሰባተኛው የለውጥ መዘውር በለውጥ አስፈላጊነት ላይ ከመስማማት ባለፈ የኢትዮጵያን ያለፈውን እና የመጪውን የእድገት ትልሟን የሚያመላክት ጥርት ያለ ፖለቲካዊ ፍልስፍና አሁንም አስፈላጊያችን ነው።እዚህ ላይ ከፖለቲካ ፍልስፍና ይልቅ ነፃነት መቅደም አለበት የሚሉትንም መዘንጋት አይገባም።ለሁሉም ግን እርግጠኛ የምንሆንባቸው ሁለት ነገሮች አሉ።የመጀመርያው የኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ በሃያኛው ክፍለዘመን አጋማሽ ጀምሮ የተረጋጋ የመንግስት ስርዓት ከተመለከትን 40ኛው ዓመት ላይ መሆናችንን።ሁለተኛው ደግሞ ጊዜውን አሁን መተንበይ ባንችልም ሰባተኛው የለውጥ መዘውር ምን መምሰል አለበት? ወዴት እንዴት ነው መሄድ የሚገባን?ያለፉት ስህተቶች እንዳይደገሙ ምን ይደረግ? የመሳሰሉት ጥያቄዎች ሊነሱ የሚገባበት ጊዜ ላይ መሆናችንን አለመርሳት የሚሉት ናቸው።

ጉዳያችን ጡመራ
ጥቅምት 30/2006 ዓም
ኦስሎ

Friday, November 8, 2013

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በአዲስ አበባ የሳውዲ ምክትል አምባሳደር በኢትዮጵያውያን ላይ እየደረሰ ስላለው ጉዳይ በፅሁፍ እና በቃል ማብራርያ እንዲሰጡ አደረገ።የሳውዲ አረብያ ዋናው አምባሳደር ሀገር ውስጥ አይደሉም ተብሏል።



''የኢትዮጵያዊው በሳውዲ አረብያ የፀጥታ ኃይሎች መገደል በምንም መልኩ ተቀባይነት የለውም በአዲስ አበባ የሳውዲ ምክትል አምባሳደር ስለጉዳዩ በፅሁፍም ሆነ በቃል ማብራርያ እንዲሰጡ  ጠይቀናል ጉዳዩን በቅርበት እየተከታተልን ነው'' አምባሳደር ዲና ሙፍቲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ዛሬ ምሽት የሰጡት መግለጫ።

በሌላ በኩል ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አገኘሁት ያለውን ኢዜአ ማምሻውን ባሰራጨው ዜና ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው የሚመለሱበትን ሁኔታ እየተሰራ መሆኑን እና ጉዳዩን የምያቀላጥፍ ተጨማሪ የሰው ኃይል ሳውድ አረብያ ወደሚገኘው የኢትዮጵያ ኢምባሲ መላኩን ገልጧል።

በጉዳዩ ላይ ሚዛናዊ እና በጎ አስተሳሰብ መያዝ ትተው በእየማኅበራዊ ድህረ ገፁ ከኢህአዲግ በላይ ኢህአዲግ ሆነው በጭፍን ድጋፍ ''መንግስት ምንም ማረግ አይችልም መንግስት ዝምታውም ልክ ነው'' እያሉ እራሳቸውን የመንግስት ጠበቃ የሚያደርጉ ከእዚህ ምን ትምህርት ያገኙ ይሆን? ሀገራችንን ስንወድ ወተቱን ለማጥቆር ወይንም ጥቁሩን ለማንጣት መሆን የለበትም።እንደሰው የማሰብ ፍትሃዊ አስተሳሰባችንን ለምን በጭፍን የመንግስት ድጋፍ እንደምንጋርደው አይገባኝም።

በሌላ በኩል የውጭ ጉዳይም ሆነ ሌሎች አካላት  ሃገርን እስከወከሉ ድረስ በ 21ኛው ክፍለ ዘመን መሆናቸውን መርሳት አይገባቸውም። በእየደቂቃው በሚቀያየር የዓለም ስርዓት ውስጥ ሆነን የማኅበራዊ ድህረ ገፆች ይህንን ያህል ስለ ጉዳዩ እስኪያጮሁ ድረስ  የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መጠበቅ አልነበረበትም።

በጉዳዩ ላይ የሳውድ አረብያ መንግስት የሰጠው ምላሽም ሆነ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው የሚመለሱበት ሁኔታ ምን ያህል በኢትዮጵያ ኢምባሲ በኩል ምን ያህል እየተቀላጠፈ መሆኑ ገና አልታወቀም። የተለወጠ ነገር ካለ  በሳውድ አረብያ ያላችሁ ወገኖቻችን ሁኔታውን ባገኛችሁት መንገድ አሳውቁ።

ጉዳያችን ጡመራ ጥንቅር

//////////////////////////////////---------////////////////////////////////-------------------------///////////////////////////////////////////

''የኢትዮጵያ ባንዲራ የት ሄደ?'' (ቪድዮ 1) እና አይዟችሁ ባይ የሌላቸው የኢትዮጵያ ታዳጊ ልጆች ስደት (ቪድዮ 2)

ቪድዮ 1


ቪድዮ 2

በሳውዲ ላለው የኢትዮጵያውያን አዲሱ ሰቆቃ ''የኢትዮጵያ መንግስት ምን ያድርግ?'' ለምትሉ

ህገ መንግስቱ አንቀጽ 33 ''የዜግነት መብቶች'' በሚለው አንቀፅ ስር

ተራ ቁጥር 2/ . ''ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የኢትዮጵያ ዜግነት በሕግ የሚያስገኘውን መብት ጥበቃና ጥቅም የማግኘት መብት አለው'' ይላል።ይህ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚስዮኖች ኢትዮጵያውያንን በውጭ የሚያስተናግዱበት አንዱ እና መሪ ሕግ ነው።
በሳውዲ አረብያ መንግስት ሰሞኑን በሚፈፀመው ድርጊት ዙርያ መንግስት በትንሹ ሊያደርጋቸው የሚገቡ ሶስት ትንንሽ ስራዎች ነበሩ።

1/ ስለ ጉዳዩ ዝርዝር መረጃ ከስፍራው ለኢትዮጵያ ሕዝብ መግለፅ፣

2/ በአዲስ አበባ የሚገኘው የሳውዲ አምባሣደርን ጠርቶ ማብራርያ መጠየቅ እና

3/ ልዩ ልዑክ ወደ ሳውዲ ልኮ ከከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር ተነጋግሮ ጊዝያዊ የማግባብያ ሃሳቦች አቅርቦ የዜጎቹን መብት ማክበር።አንዳቸውም አልተሰሩም።

አንድ መንግስት በሥራ ላይ ነው (functional) የሚባለው እኮ በመጀመርያ የሀገሩን ዜጎች መብት ማስከበር ሲችል ነው።ይህ የሉአላዊ ነትም ጥያቄ ነው።በጣም አሳፋሪ ነው።ማንም ሀገር ዜጋው በውጭ ሀገር በከፍተኛ ወንጀል ተከሶ ጥፋተኛነቱ ተረጋግጦም ቢሆን ፍርድ ቤትም ሄዶ አምባሳደሩ ከጎኑ ይገኛል። የሀገሮችን የዲፕሎማሲ ግንኙነት መሰረት የጣለው በፈረንጆቹ አቆጣጠር 1961 ዓም ቬና ኦስትሪያ ላይ የተፈረመው ''የቬና ኮንቬሽን'' (venna convention) ተብሎ የሚታወቀው ዓለም አቀፍ ሕግ በራሱ አንቀጽ 36 ላይ ''ማንኛውም የውጭ ሀገር ዜጋን የሌላ ሀገር ዜጋ በጥፋተኝነቱ ቢያስረው ለሀገሩ ቆንስላ ፖሊስ እራሱ የት እና ለምን እንዳሰረው ፋክስ ማድረግ አለበት'' ብሎ ያዛል።መንግስታችን ይህንን ሁሉ አሳልፎ ሰጠ ማለት ሉዓላውነቴን አላስከበረም ሥራ ላይ አይደለም ወደሚል ድምዳሜ ያደርሳል።እጅግ አሳዛኝ ሥራ እየተሰራ ነው።ያቃጥላል። የቬና ኮንቬንሽን አንቀጽ 36 የእንግሊዝኛውን ቃል ተመልከቱት Article 36. ''Foreign nationals who are arrested or detained be given notice "without delay" of their right to have their embassy or consulate notified of that arrest. If the detained foreign national so requests, the police must fax that notice to the embassy or consulate, which can then check up on the person. The notice to the consulate can be as simple as a fax, giving the person's name, the place of arrest, and, if possible, something about the reason for the arrest or detention.'' http://en.wikipedia.org/.


Thursday, November 7, 2013

የበዕውቀቱ ግጥም በአውስትራልያው ዩንቨርስቲ ሲረጋገጥ!

በቅድምያ የበዕውቀቱን ግጥም ላስቀድም በመቀጠል የአውስትራልያው ''ኩይንስ ላንድ'' ዩንቨርስቲ ኢትዮጵያን በዓለም ላይ የድብርት ስሜት (clinical depression) ካልተጠናወታቸው ጥቂት ሃገራት ተርታ መሆኗን በጥናቴ አገኘሁት ያለውን ''የዋሽግተን ፖስት'' ጥቅምት 28/2006 ዓም ያወጣውን አስከትላለሁ።

ከድብርት ስሜት የራቀ ሕዝብ መሆናችን በምጣኔ ሀብት በልፅገን ወይም የመሰረታዊ ፍላጎቶቻችን ተሟልተው አይደለም።ይህ  ፀጋ ነው።ሀገር ቤት የሚኖሩ ወገኖቼ የውጭውን ዓለም የድብርት ደረጃ እና ሰው በባቡር ውስጥ  ሲሄድም  ምን ያህል ሳይነጋገር እንደሚሄድ ካልተመለከቱት ይህንን ላይረዱት ይችላሉ።ይውጭውን ዓለም ድብርት የተመለከተ የሃገር ቤትን የድብርት መድኃንትነት ይረዳዋል።

አንድ ጊዜ አንድ የውጭ ዜጋ በኢትዮጵያውያን ደስተኛነት ምንጭ ግራ መጋባቱን ሲገልፅ እንዲህ አለ።

''አዲስ አበባ መንገድ ላይ አንድ ልጅ መጣ እና ሳንቲም ለመነኝ።እንደሌለኝ እራሴን በመወዝወዝ ገለፅኩለት።እርሱ ግን መልሶ እኔን እያየ ሳቀብኝ እየሳቀ ሄደ።እኔ ገንዘብ ያለኝ የእርሱን ያህል ደስተኛ አይደለሁም።ይህንን ልጅ መልሼ ጠራሁት እና የት እንደሚኖር ጠየቅሁት ከመንገድ ዳር እንደሚኖር ነገረኝ።ይህንን ሲነግረኝም ፈገግ ብሎ ነበር።ኢትዮጵያውያን ውስጣዊ ደስታቸው  የሚመነጨው ከእግዚአብሔር መሆን አለበት አልኩኝ።በችግር ላይ ሆነውም አይደበሩም።''ብሏል።

ሃይማኖታዊ በዓላት ሲከበሩ ሕዝብ ሁሉ በደስታ ወጥቶ የሚያከብረው የቁሳዊው ነገርስለተሟላለት አይደለም።እየከፋን ደስ እንዲለን የተሰጠን ፀጋ አለ።ሃዘናችንን የምንረሳበት የተሰጠን ልዩ ስጦታ አለ።

ወደ ገጣሚ  በእውቀቱ ስዩም ግጥም እናምራ አርስቱ ''ኢትዮጵያዊ ነኝ'' ትላለች።

''ኢትዮጵያዊ ነኝ 

      ኑሮ ቢገፋኝ የማልወድቅለት፣

                      እንደ አክሱም ድንጋይ እንደ ሮሃ አለት፣

የጊዜ ሞገድ ያላደቀቀኝ፣

 የመከራ ዶፍ ያልነቀነቀኝ፣

     ለሙሾ ሲያጩኝ  ቅኔ የምቀኝ፣

በግራ ሲሉኝ የምገኝ በቀኝ፣

ኢትዮጵያዊ! ነኝ።''



A stunning map of depression rates around the world

BY CAITLIN DEWEY
November 7/2013  at 7:00 am


Redder countries have higher depression rates. Bluer countries have lower depression rates. (Max Fisher/The Washington Post)
በካርታው ላይ እነደሚታየው የሰማያዊ ቀለም ያለባቸው ሃገራት (በጥናቱ መሰረት) የድብርት መጠናቸው ከ 4% በታች የሆኑ ናቸው።የቀይ ቀለም የሚታይባቸው ደግሞ የድብርት ደረጃቸው ከፍተኛ የሆኑ ናቸው።ለምሳሌ ኢትዮጵያ፣አውስትራልያ ከ 4%በታች ሲሆኑ ሱማልያ፣ኤርትራ ሳውዳረብያ እስከ 6% የሚሆን የድብርት መጠን ላይ መሆናቸውን ያመላክታል።የድብርት መጠኑን ጥናቱ በ 7 እና 4% መካከል ሁሉንም ሃገራት አስቀምጧል።
ምንጭ- ዋሽግተን ፖስት ጋዜጣ  http://www.washingtonpost.com/blogs/worldviews/wp/2013/11/07/a-stunning-map-of-depression-rates-around-the-world/?tid=sm_fb  

Tuesday, November 5, 2013

''የአፍሪካ ሚድያ ፎረም'' በሚል በእነ ሚሚ ስብሃቱ የሚዘጋጀው ጉባኤ በኢትዮጵያ የሚድያ ነፃነት ላይ ከመሳለቅ እኩል ሆኖብኛል።ለመሆኑ እኛ ከአፍሪካውያን ጋር ስንነፃፀር የት ላይ ነን?

አዲስ ዘመን ጋዜጣን ሳስበው ነፃነት ናፈቀኝ

ዛሬ ዛሬ ጋዜጦችን በኢንተርኔት ማንበብ የተለመደ ነው።የበለፀጉት ሃገራትን ትተን የአፍሪካዎቹ ለምሳሌ የዩጋንዳው ''ኒው ቪዥን'' የኬንያው ''ዴይሊ ኔሽን'' ዕለታዊ ጋዜጦች በሕዝቡ ዘንድ እንደ ማለዳ ቡና ከጉልት ቸርቻሪ እስከ ከፍተኛ የናጠጠ ሃብታም ነጋዴ ሳያነባቸው አይውሉም።ጋዜጦቹ ይዘዋቸው የሚወጡት እትሞች ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል የሚመለከቱ እና የመፃፍ መብትን በተሻለ ደረጃ ይንፀባረቅባቸዋል።ስርጭታቸው በታተሙበት ዕለት እስከ ታች ገጠር ከተሞች ድረስ የመድረስ አቅም አላቸው።

ለምሳሌ የኬንያው ''ዴይሊ ኔሽን'' በቀን ከእሩብ ሚልዮን ቅጂ በላይ ሸጦ ያድራል።የዩጋንዳው ዕለታዊ ጋዜጣ ''ዘ ኒው ቪዥን'' እንዲሁ እጅግ ተናፋቂ ጋዜጣ ነው።መቼ ነግቶ አንብቤው ባዩ ብዙ ነው።ጋዜጣው  በአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች  ጭምር ሳይቀር ሁል ጊዜ እንዲያነቡት እና በዕለቱ ትምህርት ቤት የሚያቀርቡት የቤት ሥራ እንዲሰሩ ይታዘዛሉ።ታድያ ማታ አባት እቤት እስኪገባ እና ጋዜጣውን ይዞ እስኪመጣ መጠበቅ የልጆች ሥራ ነው።ማታ ላይ የሚጠጣ አባት ያለው ልጁ የቤት ስራውን ባለመስራቱ ይታወቃል።''ኒው ቪዥን'' የመንግስት ድርሻ ከሃምሳ ፐርሰንት በላይ ያለበት ጋዜጣ ነው(በቅርቡ ፐርሰንቱ ለውጥ ሊኖረው ይችላል)።

እነኚህ ሁለት የቅርብ እና የሩቅ ጎረቤቶቻችን ህዝባቸው የማንበብ ባህሉ እንዲያድግ ደረጃቸውን የጠበቁ ጋዜጦች አሏቸው።

የእኔው አዲስ ዘመን 

ዕለታዊ ጋዜጣ አዲስ ዘመን በ 1935 ዓም ስራውን ሲጀምር ሃገራቱ ቅኝ ተገዢዎች ነበሩ።ዛሬ ዕለታዊ ጋዜጦቻቸው በሀገር ውስጥ የተከበሩ እና የህዝቡን የዕለት ከዕለት  ሕይወት የሚዳስሱ ብቻ ሳይሆኑ ከየትኛውም የዓለም ጥግ በኢንተርኔት በቀጥታ ይነበባሉ።የመፃፍ ነፃነት እና የጋዜጠኝነት መብት የታገተባት ሀገር ኢትዮጵያ አዲስ ዘመንን ይዘን ከአራት ኪሎ ብርሃንና ሰላም አለፍ ሲል ጨረታ እና የግምሩክ ማስታወቅያ የሚከታተሉ የመርካቶ ነጋዴዎች ያውም ሥራ እና እንጀራ ሆኖባቸው ይገዛሉ።

አዲስ ዘመን ጋዜጣ በገበያ ላይ 70 ዓመታትን አሳልፏል።ባለፉት አርባ ዓመታት ውስጥ ከሚያወጣቸው ፅሁፎች ይልቅ በንጉሡ ዘመን የሚያወጣቸው ፅሁፎች በሕዝብ ዘንድ የመነጋገርያ አጀንዳዎች የመሆን ዕድል ነበረባቸው።የሚያሳዝነው ነገር በንጉሡ ዘመን ስልጣን ጠቅልሎ መያዝ የተለመደበት እና እስከ 1960ዎቹ ድረስ የነበረ  የአገዛዝ ዘይቤ ነበር እንበል።በደርግ ዘመንም ሶሻሊስታዊ የአምባገነነት አስተዳደር የአንዳንድ የዓለማችን ክፍል ፋሽንም ነበር እንበል። ዛሬ መላው ዓለም በመረጃ መረብ በተገናኘበት፣የተነገረው ብቻ ሳይሆን የተነጠሰው በሚታወቅበት ዘመን  የሀገራችን የፕሬስ ነፃነት ይህንን ያህል የሚያሸማቅቅ መሆኑ ምን ያህል ድንቁርና በሕዝባችን ላይ እንደጣለ ያመላክተናል።

ሕዝብ የማንበብ ባህሉ እንዲዳብር እንደ አዲስ ዘመን ያሉትን ጋዜጦች በዘመናዊ መልክ ማደራጀት እና ለሕዝብ እንዲደርሱ ከመንግስት የፕሮፓጋንዳ መሳርያነት ማውጣት ብሎም የመፃፍ መብትን መልቀቅ ሲገባ ዛሬም ድረስ   በነፃ የመፃፍ መብት መነፈጋችን እጅግ ያስቆጫል።የአዲስ ዘመን ጋዜጣ  በ 1960ዎቹ ላይ ይፈለግ የነበረውን ያህል ዛሬ ከነመኖሩም እንዲረሳ መሆኑ የብዙ ችግሮቻችን አመላካች አንዱ መንገድ ነው።እርግጠኛ ነኝ እራሱ አዲስ ዘመን ጋዜጣን አሁን ባላስታውሳችሁ ብዙዎቻችሁ እረስታችሁታል።ግን ቀን ጥሎት እንጂ አዲስ ዘመን የተባለ ዕለታዊ ጋዜጣ 70ኛ ልደት በአሉን አክብሮ ወደ 71ኛው እያዘገመ ነው።

የአዲስ ዘመን ጋዜጣን ጉስቁልና ስናጤነው እና የቅርብ ጎረቤት ኬንያ እና ዩጋንዳ ያሉበትን የማንበብ ባህል መዳበር እና ለመፃፍ ነፃነታቸው ምን ያህል ዋጋ እንደሚሰጡ ስናስብ ምን ያህል በነፃነት እጦት እየማቀቅን እንደሆነ ይቆጠቁጠናል።አይደለም ጋዜጣ ብሎጎችን እኮ አሳዶ የሚዘጋ መንግስት ያለን ነን- እኛ ኢትዮጵያውያን።በእዚህ ደረጃ ህዝብ የመፃፍ እና የመናገር ነፃነት አጣ ማለት ምን ማለት ነው? አዎን!ይህ ማለት ሲመነዘር ብዙ ብዙ ይወጣዋል።

ከምንዛሬው ውስጥ ትውልድ አዲስ ነገር እንዳይፈጥር መሸበብ፣ሙስና ሕዝብ አናት ላይ ሲፈነጭ ዝም እንድንል፣በሕዝብ ስም መንግስት የተበደረው ገንዘብ እንደፈለገ ለግለሰቦች የግል ኪስ ማድለብያ ሲሆን ፈርተን እንድናቀረቅር፣የተሳሳተ የትምህርት ፖሊሲ ትውልድ ሲገድል ለመናገር እንዳይቻል ወዘተ መጥቀስ ይቻላል።በነፃነት ለመፃፍ መታገድ እንዲህ ትውልድንም ሀገርንም ይገድላል።የኢትዮጵያን አሳዛኝ የሚያደርገው መንግስት በእራስህ መንገድ ቀጥል ለሕዝባችን በገንዘባችን የሻማ ጭላንጭል እንሆናለን ብለው የተነሱ የግል ጋዜጦችን ለምሳሌ አዲስ ነገር፣ወዘተ እያዋከበ አዘጋጆቹን በዘመኑ ፋሽን ስድብ እየለጠፈ ከገበያም ከሀገርም እንዲሰደዱ ማድረጉ ነው።የመፃፍ ነፃነት ማጣት ምንዛሬው ብዙ ነው። ምንዛሬውን ዘርዝረን ስንጨርስ አስከፊው የወደቅንበት ጭቃ ያዳለጠን ዳጥ ወለል ብሎ ይታየናል። ውድ የሆነው ነፃነትም እጅግ ይናፍቀናል።አዎን አዲስ ዘመን ጋዜጣን ሳስበው ነፃነት ናፈቀኝ።

ጥቅምት 23/2006 ዓም
ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ

Saturday, November 2, 2013

ባለፉት ሶስት ዓመታት ውስጥ ብቻ በትንሹ 2,500 ኤርትራውያን ወጣቶችን በሜደትራንያን ባህር ውስጥ መስመጣቸው ታወቀ። የአቶ ኢሳያስ መንግስትም በአስተርጓሚነት ሰላዮቹን ጣልያን አስገብቷል። AFP




የብዙ አፍሪካውያን ከሊብያ ከአልጄርያ እና ከሞሮኮ ወደ ደቡባዊ አውሮፓ የሚያደርጉት ፍልሰት የመላው ዓለም መነጋገርያ ከሆነ ሰነበተ።በቅርቡ ባብዛኛው ኤርትራውያንን የያዘ ጀልባ ተሳፋሪዎቹን እንደያዘ በደቡባዊቱ የጣልያን ግዛት መስጠም ጉዳዩን በአዲስ መልክ መቀስቀሱ ይታወቃል።ባለፈው ሰሞንም የአውሮፓ ህብረት በጠራው ድንገተኛ ስብሰባ የደቡብ አውሮፓ መግብያ በሮች 'በዘመናዊ ካሜራ እና ልዩ ጥበቃ እንዲጠናከሩ' በሚል ሃሳብ ዙርያ ሃሳቦችን ተለዋውጧል።

አስገራሚው ነገር ግን አውሮፓውያንም ሆኑ የአፍሪካ መንግሥታት ችግሩን እንፍታው የሚሉት ከችግሩ ምንጭ ማለትም ከአፍሪካ አምባገነን እና ማን አለብኝ መንግሥታት ጀምረው ሳይሆን ስለ ጀልባው፣ድንበር ማጠር ወዘተ እያነሱ በጉዳዩ ላይ ከመሳለቅ ባላለፈ ዙርያውን የመዞሩ አባዜ አሁንም ለችግሩ መፍትሄ በቅርቡ እንደማይገኝለት አመላካች ነው።ለምሳሌ የኢትዮጵያውያንን እና የኤርትራውያኑ ስደት ምክንያት በሀገራቸው ካለው የኢኮኖሚ ችግር በዘለለ የአምባገነንነት እና የዘር ፖለቲካ መንሰራፋት መሆኑ እየታወቀ አውሮፓውያን የነገሩን ስረ-ምክንያት ትተው ስለ ድንበር ማጠር ማውራት ቀጥለዋል።

 ቄስ  ሙሴ ዘራይ እና ''ሀበሻ ኤጀንሲ'' የተሰኘ ድርጅታቸው  በተለይ በ ሜዴትራንያን በኩል አልፈው ለመምጣት የሚሞክሩትን ኤርትራውያንም ሆኑ ኢትዮጵያውያንን በመርዳት  ይታወቃሉ።ድርጅታቸው በስደተኞቹ ዙርያ ያደረገውን ጥናት እና ያሉትን መረጃዎች ትናንት ጥቅምት 21/2006 ዓም (Oct.31/2013) ለፈረንሳይ የዜና አገልግሎት (ኤኤፍፒ) እና ለሌሎች ዓለም አቀፍ የዜና አውታሮች መግለጫ ሰጥቷል።በመግለጫው ላይ የተተኮሩት ሁለት ነጥቦች ሲሆኑ-
የመጀመርያው  ከባህር ጉዞ የተረፉትን ስደተኞች ችግር ለጣልያን መንግስት የሚያስተረጉሙት የሻብያ መንግስት ሰላዮች መሆናቸውን እንደደረሱበት እና ጉዳዩን ከኢኮኖሚ ጋር ብቻ እያስተሳሰሩ ፖለቲካዊ ምክንያት እንዳላሰደዳቸው በመናገራቸው ችግር ከመፍጠራቸውም በላይ የስደተኞቹን መረጃዎች ለሻብያ መንግስት በሚስጥር እየላኩ ብዙ ቤተሰቦች ችግር ላይ መውደቃቸውን ገልፀዋል።
በሌላ በኩል እርሳቸው እና ድርጅታቸው ለጉዳዩ ቅርብ የመሆናቸውን ያህል እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ 2010 ወዲህ አሁን እስካለንበት 2013 ዓም በሶስት አመታት ውስጥ ብቻ ወደ አውሮፓ ለመሻገር ሲሞክሩ በሜደትራንያን ባህር ውስጥ ሰምጠው የቀሩት ኤርትራውያን ቁጥር በትንሹ  2,500 መሆኑን ተናግረዋል።ዜናውን የጀርመኑ DW ራድዮ እና የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ለመላው ዓለም አሰራጭተውታል።ባለፈው ወር ላይ ጉዳዩ በአቶ ኢሳያስ መንግስት ላይ ከፍተኛ ተቃውሞ በተለያዩ የውጭ ሃገራት በሚኖሩ ኤርትራውያን መሰማቱ ይታወቃል።

በመጨረሻም ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ዛሬ ጥቅምት 23 እና ነገ ጥቅምት  24/2006 ዓም በቫቲካን በህገወጥ የሰዎች ዝውውር ላይ የምክክር ስብሰባ ጠርታለች።ስብሰባው የድርጊት መርሃግብር ለመቅረፅም የታለመ መሆኑ የቫቲካን ድህረ ገፅ ያትታል።

Sources-Priest claims Eritrea spies hunting shipwreck survivors in Italyhttp://www.globalpost.com/dispatch/news/afp/131031/priest-claims-eritrea-spies-hunting-shipwreck-survivors-italy 



ANTI-HUMAN TRAFFICKING MEETING AT VATICAN NOV. 2-3





Text from page http://en.radiovaticana.va/news/2013/10/29/anti-human_trafficking_meeting_at_vatican_nov._2-3_/en3-741883 
of the Vatican Radio website 


Friday, November 1, 2013

የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ባለቤት ሰርካለም ፋሲል በእስር ቤት ከተገላገለችው ልጇ ጋር ከስደት ዓለም ያሰማችው ድምፅ (ኦድዮ)


የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ባለቤት ሰርካለም ፋሲል በእስር ቤት ከተገላገለችው ልጇ ጋር ከስደት ዓለም ያሰማችው ድምፅ (ኦድዮ)
ምንጭ- የኢሳት ራድዮ ያቀረበው ከ ኢትዮጵያ መወያያ መድረክ ላይ የተወሰደ

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...